Thursday, January 18, 2018

ለዲሞክራሲ የሚናካሂደው ትግል በምንም አይነት ጥገናዊ ለውጥ አይደናቀፍም!

የአርበኞች ግንቦት 7 ርዕስ አንቀጽ

የኢትዮጵያ ህዝብ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ከታህሳስ 3 ቀን 2010 ጀምሮ እስከ ታህሳስ 21 ቀን ሲያካሂድ በሰነበተው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ በራሱ በድርጅቱ ውስጥ ተፈጥሮአል ባላቸው ችግሮች እና የአገራችንን ግዜያዊ ሁኔታና የወደፊት አቅጣጫ አስመልክቶ ግምገማ በማድረግ ባለ 8 ነጥብ ውሳኔዎችን አሳልፎ እንደተጠናቀቀ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል ።

ኢህአዴግ አወጣሁ ያለው ይህ መግለጫ በአጭሩ ሲዳሰስ በቅርጹም ሆነ በይዘቱ ብዙ ችግሮች የሚታዩበት ፤ አደናጋሪና ወጥነት የሌለዉ፥ እርስ በርሱ በሚጣረስ ሀሳቦች የታጨቀ ከመሆኑም በላይ አገራችን የገባችበትን መሰረታዊ ችግሮች ያላገናዘበ እና ህዝባችን በተለይ ላለፉት ሶስት አመታት እያነሳቸው ያሉትን መሠረታዊ ጥያቄዎች ከግምት ዉስጥ ያላስገባ ወይም እውቅና ያልሰጠ ፤ የህወሃት የበላይነት የነገሠበትን ሥርዓት ዕድሜ ለማስቀጠል ሲባል ገዢዉ ፓርቲ እስካሁን አከናወንኩ ያላቸውን በጎ እርምጃዎች በመዘርዘር “በአመራሮቹ ድክመት ካልሆነ በቀር ምንም አይነት የፖሊሲም ሆነ የፖለቲካ እምነት ችግር የለብኝም እና ተረጋጉ” የሚል መልዕክት ያስተላለፈበት ሆኖ ተገኝቶአል። እንዲህ አይነት መግለጫ ለማውጣት የህወሃትን የበላይነት ከውስጥ ሆነው አጥብቀው በመታገል ላይ ያሉ የሌሎች አባል ድርጅቶች አመራሮችስ እንዴት ብለው ተስማሙበት የሚል ጥያቄም በማስነሳቱ ምናልባትም ስብሰባው ከተበተነ ቦኋላ እራሱ ህወሃት “አለሁ” ለማለት በግሉ ጽፎና አጽድቆ ያሰራጨው ሊሆን ይችላል የሚልም ግምት አሳድሮአል። የግምቱን ምክንያታዊነት ደግሞ የሚያረጋግጠው መግለጫው ይፋ የሆነው ስብሰባው ተጠናቀቀ ከተባለበት ዓርብ ታህሳስ 21 ቀን ቦኋላ ለ36 ሰዓታት ዘግይቶ መሆኑ ነው። መግለጫው ላይ እንዲህ አይነት ጥርጣሬ በመፈጠሩ የተነሳ በኢህአዴግ 27 አመት የሥልጣን ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የ4ቱም ድርጅቶች ሊቃነመናብርት በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት ተገደዋል። በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅትም ህብረተሰቡ ውስጥ ጥርጣሬ በፈጠሩት እና መነጋገሪያ በሆኑት ነጥቦች ላይ በሁለት ጎራ የተከፈለ አስተያያት ሲሰጥ ተስተውሎአል።

ሁላችንም እንደምናውቀው የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የሆኑት 3ቱም ድርጅቶች ህወሃት የራሱን የፖለቲካ አጀንዳ ለማሳካትና ጥቅሙን ለማስጠበቅ በህወሃት የተፈጠሩ ናቸው። በዚህም የተነሳ ድርጅቶቹ እስከ ቅርብ ግዜ ድረስ ከአገርና ከወገን ጥቅም በላይ በአካል ለፈጠራቸው ህወሃት ታማኝ ሆነው ሲያገለግሉ ኖረዋል። ይህ ሃቅ መሆኑ እየታወቀ አንዳንዶች ከዚህ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ በጎ ውጤት በመጠበቅ አገዛዙ እስካሁን በተከተላቸው የተሳሳቱ ፖሊሲዎች እና በፈጸማቸው ህገወጥ ተግባሮች ምክንያት አገራችን ከገባችበት ዘርፈ ብዙ ችግሮች የምትወጣበትንና ከተጋረጠባት የህልውና አደጋ የምትታደግበትን ሥርነቀል እርምጃዎች ለመውሰድ የሚያስችሉ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ብለው ጓጉተው ነበር። ህወሃት/ ኢህአዴግ በእስከዛሬ ተሞክሮው ምንም አይነት ለአገርና ለወገን የሚጠቅም እርምጃዎችን ከራሱ ጠባብ አላማ አስበልጦ እንደማያውቅ እየታወቀ እንዲህ አይነት ጉጉት ያደረባቸው ወገኖች ተስፋ ያደረጉት እንዲያው በድፍኑ አልነበረም። ምክንያቱም መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም በሞት ከተለየ ወዲህ ህወሃት ውስጥ የተፈጠረው የሥልጣን ክፍፍል የህወሃትን የበላይነት ተቀብለው በኖሩ አባል ድርጅቶች በተለይም በኦህዴድና በብአዴን ዘንድ“እንደከዚህ በፊቱ ታዛዥ ሆነን አንኖርም” የሚል አመጽ እና የእኩልነት ጥያቄ ቀስቅሶአል። በሌላ በኩል ደግሞ በአብዛኛው የአገራችን ክፍል የሚኖረው ህዝባችን አገዛዙ አሠልጥኖ ካዘመተበት የአጋዚ ጦር ጋር እየተፋጠጠ ለመብቱና ለክብሩ በማካሄድ ላይ የሚገኘው ሁለገብ ትግል ከግዜ ወደ ጊዜ እየተጠናከረና አድማሱን እያሰፋ እንጂ ወደ ኋላ እየተመለሰ ስላልሆነ በራሱ በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውስጥ በተለያየ የሥልጣን እርከኖች ላይ ባሉ አመራሮች ዘንድ ግንዛቤና ድጋፍ እያገኘ የመጣበት ሁኔታም አለ። ከዚህ በተጨማሪ ህወሃት በገጠመው ንቅዘትና በህዝብ ዘንድ ባጣው ተቀባይነት ምክንያት ከከፍተኛ አመራሩ ጋር ተሻርከው በሃብት ዘረፋ የተሰለፉ ነባር የኦህዴድና የብአዴን አመራሮችን በሙስናና በመልካም አስተዳደር ጉድለት ስም እያባረረ በወታደራዊና የስቪል ደህንነት ተቋሞቹ ውስጥ ተኮትኩተው ያደጉ ወጣት አመራሮችን ወደ ሥልጣን እንዲመጡ ሁኔታዎችን አመቻችታል። በተለይም በኦህዴድ ውስጥ። እነዚህ አዳዲሶቹ አመራሮች ደግሞ እንደቀደሞዎቹ ነባር አመራሮች ህሊናቸውን ሽጠው ለሚከፈላቸው ደመወዝ የሚገዙ አልሆኑም። እንዲያውም እንወክለዋለን የሚሉት ማህበረሰብ የሚያሰማውን የዘመናት ብሶትና የመብት ጥያቄ ከመደገፍ አልፈው ወገናዊነታቸውን በተለያየ መንገድ መግለጽ ጀምረዋል። ከነዚህ ሁሉ ምክንያቶች በመነሳት ህወሃት እንደ እስከዛሬው የኦህዴድንና የብአዴንን ሙሉ ድጋፍና ትብብር ሳያገኝ ብቻውን እየገደለ፤ እያሰረ ፤ እየገረፈና እያፈናቀለ ለመዝለቅ እንደማይችል ሥለሚረዳ አጋጣሚውን በመጠቀም እራሱን ለህዝብ ጥያቄ ለማስገዛት ሥርነቀል ውሳኔ ለማስተላለፍ ይችል የሆናል የሚል ተስፋ ይዘው ነበር።

ብዙዎችን ተስፋ ያስቆረጠው ይህ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች አንዳንዶች ጠብቀውት እንደነበረው ሥርነቀል ለውጥ ለማምጣት አስተዋጽዖ የሚያደርግ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ከማናችንም በላይ ተጠቃሚው እራሱ ህወሃት ይሆን እንደነበር ግልጽ ነው። ምክንያቱም ላለፉት 27 አመታት ሥልጣንን ከለላ በማድረግ በአገር ሃብት ዘረፋ እጅግ የከበሩ፤ የሥልጣን ዕድሜያቸውን ለማራዘም በፈጸሙት አፈና በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን በግፍ ያስጨፈጨፉ ፤ ያሠሩ ፤ ያስገረፉ ፤ ያፈናቀሉና ለስደት የዳረጉ እነርሱ ስለሆኑ አገራችን ውስጥ የሚደረገው ማንኛውም አይነት ሠላማዊ የሥልጣን ሽግግር ይዞት የሚመጣው ብሄራዊ እርቅ በአብዛኛው ተጠቃሚ የሚያደርገው በወንጀል የተጨማለቀውን የህወሃት አመራርን ነበር። ዛሬ የአጋዚ ጦር የሚፈጽምበትን አፈናና ግድያ ተቋቁሞ ነጻነቱን ለማስመለስ በመፋለም ላይ ያለው ህዝባችን በምንም ተዓምር መብቱንና ክብሩን ሳያስመልስ ወደ ቤት እንደማይገባ ከምንግዜውም በላይ ግልጽ ሆኖአል። በህወሃት ገታራነትና ትዕቢት ህዝባችን ለዚህ ትግል የሚከፍለው መስዋዕትነት እየከበደና እየገዘፈ ከሄደ ለህወሃት የእስካሁኑ ወንጀሎች የሚኖረው የይቅርታ ልብ እየተመናመነና እየደነደነ በስተመጨረሻው የሚያስከፍለውም ዕዳ እየከፋ ይሄዳል። ይህ በሞራልም በህግም የተረጋገጠ ነው።

አርበኞች ግንቦት 7 አገራችን ውስጥ እየተካሄደ ያለው ትግል የዲሞክራሲ ሥርዓት ለማምጣት የሚካሄድ የሞት ሽረት ትግል ስለሆነ ህወሃት በሚያስበው ማንኛውም አይነት የጥገና ለውጥ እንደማይሰናከል አጥብቆ ያምናል።በዚህም ምክንያት ህዝባችን የጀመረው ትግል ግቡን እንዲመታ ያለውን ሃይል በሙሉ አስተባብሮ እስከመጨረሻው በጽናት ይታገላል።

ህወሃት በድል አድራጊነትና በአይነኬነት እስከዛሬ የአገራችንን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ምህዳር በበላይነት ተቆጣጠሮ ለመዝለቅ የቻለው ህዝባችንን በቋንቋና በሃይማኖት የመከፋፈል ሴራው ስለተሳካለት ነበር። ያስኬት ዳግም ላያንሰራራ እየሞተ ነው። የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ “መርህ አልባ ግንኙነት “ በማለት የኮነነው የሁለቱ ትላልቅ ማህበረሰቦች ግንኙነት የህይወት እስትንፋስ ሆኖ ህወሃትን ላለፉት 26 አመታት ሥልጣን ላይ ያቆየውን የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ አፈር ከድሜ አብልቶታል። ህወሃት ምን ያስከትል ይሆን ብሎ ሳያስብ “መርህ አልባ ግንኙነት” ብሎ የኮነነው የአማራና የኦሮሞ ህዝብ ግንኙነት የበለጠ የህዝብ ቁጣ ቀስቅሶበት ከተለመደው አሰራር ውጪ በቡድን ጋዜጣዊ መግለጫ እንዲሰጥ አስገድዶታል። “ ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ ” እንዲሉ መልዕክቱ ዒላማውን ከመታ ቦኋላ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጠ አልተሰጠ ልዩነት የለውም።“እሳትና ጭድ የሆኑት ሁለቱ ማህበረሰቦች መቀራረብ የጀመሩት በኛ ሥራ አለመሥራት ነው” ተብለንስ የለ? በቃል አቀባዩ ጌታቸው ረዳ? ሌላው ማዘናጊያና ጊዜ መግዣ ደግሞ በስብሰባው ውሳኔ ላይ ያልተጻፈና ከጋዜጣዊ መግለጫው የሰማነው የፖለቲካ እስረኞች የመፈታት ዜና ነው።

ወያኔን ማፍረስ አገራችንን ከመፍረስ መታደግ ነው! – የአርበኞች ግንቦት 7 መግለጫ

የወያኔው ጦር በጨለንቆ በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ ባደረሰው የጅምላ ጭፍጨፋና እንዲሁም በምዕራብ ሃረርጌ ሃዊ ጉዲና እና ዳሮ ወረዳዎች ውስጥ በኢትዮጵያ ሶማሊ ወገኖች ላይ በደረሰው እልቂት ንቅናቄያችን አርበኞች ግንቦት7 የተሰማውን ከፍተኛ ሃዘን ለመግለጽ ይወዳል። ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ህይወት ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውና ለዜጎች የህይወት ዋስትናና ነጻነት እውን መሆን ሌት ተቀን የሚታገለው ድርጅታችን፣ እንዲህ አይነት የጅምላ ጭፍጨፋ መርዶዎችን ሰምቶ በዝምታ ለማለፍ የሚያስችለው ትዕግስት የለውም።

የአለም ህዝብ አገራችንን በድህነቷ ይወቃት እንጅ፣ ድህነት ያልበታተነው የህዝብ አንድነትና ፍቅር ያላት አገር መሆኗንም ጠንቅቆ ያውቃል። ይህ በዘመናት የተገነባው ፍቅርና አንድነት የውዷ አገራችን ልዩ መለያ እሴቷ ነው። ይሁን እንጅ ይህ እንቁ እሴት ካለፉት 26 ዓመታት ወዲህ፣ በተለይም ደግሞ በቅርቡ እየተራከሰና ዋጋ እያጣ በመምጣቱ በአገራችን ህልውና፣ በህዝባችን ሰላምና ደህንነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ይዞ መጥቷል። ይህ የአንድነትና የፍቅር ማተባችን እየተበጠሰ ያለው በማንኛውም የውጭ ሃይል ወይም በየትኛውም ድርጅት ሳይሆን፣ ስልጣኑን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮ በሚገኘው የወያኔ ቡድን መሆኑ ስጋታችንን አባብሶታል። በየትኛውም አገር የመንግስት ታሪክ የመንግስት የመጨረሻውና ቀላሉ ስራ የዜጎችን ደህንነትና ህልውና ማስጠበቅ ነው። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ለዘመናት የተገነባ ፍቅርና አንድነት ባለባቸው አገሮች የሚገዙ መንግስታት፣ የዜጎቻቸውን ደህንነትና ሰላም ማስጠበቅ ካለባቸው ሃላፊነቶች ሁሉ እጅግ ቀላሉ መሆኑን ከታሪክ መማር ይቻላል። ዜጎች ለዘመናት የገነቡትን ፍቅርና አንድነት ከትውልድ ትውልድ እያሸጋገሩ ህልውናቸውንና ደህንነታቸውን አስጠብቀው እንዲጓዙ፣ ፍትሃዊ አስተዳደር መመስረት ግድ ነው። እንደ ጣሊያን የመሳሰሉ የውጭ ወራሪዎች አገራችንን በቅኝ ግዛት ለመያዝ ያልቻሉት ይህን ዘመን የማይሽረውን የአንድነትና የፍቅር ማተብ ለመበጠስ ባለመቻላቸው መሆኑ የሚታወቅ ነው። ወያኔ ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድነት ይነሳብኛል በሚል ፍርሃት፣ ህዝባችንን እርስ በርስ በማጋጨት በየቦታው የዜጎች እልቂት እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑ ፣ በአለም የመንግስታት ታሪክ ልዩ ያደርገዋል። ይህ ህዝብን እርስ በርስ እያጨፋጨፉ ለመግዛት የሚደረግ ሙከራ፣ ዛሬ ሆድን ሞልቶ ለማደር የጠቀመ ቢመስልም፣ የሁዋላ ሁዋላ ግን “መሬት ተከፍታ በዋጠችኝ” የሚያስብል አደጋ በገዢዎች ላይ ይዞ መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ከሊቢያው መሪ ጋዳፊ እና ከየመኑ አህመድ ሳላህ የቅርብ ጊዜ ታሪክ መማር ይቻላል።

በሃዊ ጉዲናና ዳሮ ወረዳዎችም ይሁን በጨለንቆ፣ ከዚያ በፊትም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተካሄዱ እና አሁንም በመካሄድ ላይ ያሉ ጭፍጨፋዎችና ግጭቶች በህዝብ መካከል የሚካሄዱ ሳይሆኑ ወያኔ የስልጣን እድሜውን ለማራዘም ሲል የሚለኩሳቸውና የሚያራግባቸው መሆኑን ህዝባችን የሚያውቀው ሃቅ ቢሆንም፣ ዛሬም ይህን ሃቅ ልናስታውስ እንወዳለን። ወያኔ በስልጣን ላይ እንዲቀጥል እስከፈቀድንለት ድረስ በዘመናት የተገነባው የፍቅርና የአንድነት ማተባችን ተበጣጥሶ አሁን ከሚታዬውም በላይ እጅግ አስከፊ ወደሆነ የእርስ በርስ ጦርነት እንደሚከተን የታወቀ ነው። ስለዚህ ይህን የአገር ጠላት ከስር መሰረቱ ነቅሎ በመጣል የአንድነታችንንና የፍቅር ማተባችንን መልሶ በማሰር የዜጎቻችንን ህልውና እና ደህንነት ማስጠበቅ ከእያንዳንዱ አገር ወዳድ ዜጋ ሁሉ የሚጠበቅ ነው። ወያኔ እያንዳንዷን ቀን በስልጣን ላይ በቆዬ ቁጥር በህዝባችን ላይ የሚደርሰው አደጋም በተመሳሳይ መንገድ እየጨመረ የሚሄድ በመሆኑ ዳር ቆመን የምንመለከትብት ጊዜ እንዳበቃ ማወቅ አለብን።

አርበኞች ግንቦት7 ወያኔ በህዝባችን ላይ ያደረሰውን እልቂት ሲያወግዝ፣ የእልቂቶች ሁሉ ምንጭ የሆነውን የወያኔ አገዛዝ እንድናስወገድ የተለመደ ጥሪውን በማቅረብ ነው።

ድል ለኢዮጵያ ሕዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ለዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ

Wednesday, August 23, 2017

ወያኔ እስካልተወገደ ድረስ ህዝባችን እረፍት አይኖረውም!!!

ባለፉት 26 ዓመታት በወያኔ ዘረኛ፣ ከፋፋይ፣ አፋኝና ገዳይ ፖሊሲ ስቃይ ያልደረሰበት ዜጋ አለ ከተባለ ያ ግለሰብ የአገዛዙ አባል መሆን አለበት። በወያኔ ፖሊሲ ህዝባችን ተገድሏል፤ አካለ ጎደሎ ሆኗል፣ ታስሯል፤ ተገርፏል፤ ተሰዷል። ህዝባችን በምድር ላይ ያለውን ስቃይና መከራ ሁሉ ተቀብሏል። ከዛሬ ነገ ይሻሻል ብሎ ተስፋ ሲያደርግ፣ ስቃዩ እየጨመረ፣ የህዝቡ የመኖር ህልውና አደጋ ውስጥ እየወደቀ፣ እንደ ህዝብ በጅምላ የሚጠፋበት ደረጃ ላይ ደርሷል። ጥቂቶች የህወሃት ሽፍቶችና ግብረአበሮቹ፣ የማይጠረቃውን ቋታቸውን ለመሙላት ሲሉ ህዝቡን በአጥንቱ አስቀርተው አገሩን ሁሉ ለመውረስ ላይ እና ታች እያሉ ነው።

የመንግስት ሰራተኛው በአንድ ለአምስት ተጠርንፎ በኑሮ ውድነት ሲጠበስ ቆይቶ አሁን ግን የአልሞት ባይ ተጋዳይነት ትግል ማድረግ ጀምሯል። አርሶአደሩ ሞፈሩንና ቀንበሩን እየሰቀለ፣ ጎተራውን አራቁቶ፣ ጥሪቱን አሟጦ ረሱን ለመከላከል እየተጋደለ ነው። “በብልጽግና ላይ ብልጽግናን አጎናጸፍነው” እየተባለ በእየለቱ የሚዘመርለት አብዛኛው ነጋዴ ደግሞ፣ ጥቂቶች ለበሉት እሱ እዳ እንዲከፍል በመታዘዙ ፣ “ በቃኝ” ብሎ ትግሉን ለኩሷል። ወያኔ አስፈራርቶ ለመግዛት ያወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወደ ጎን በመተው፣ ህዝባችን ከአቅጣጫው ትግሉን ማቀጣጠሉ ለወያኔ ያለውን ንቀት ብቻ ሳይሆን፣ ከእንግዲህ ወያኔንና ሰንኮፉን በአገራችን ምድር ለማየት እንደማይፈልግ ማሳያ ሆኖአል። ኩሩውና ጀግናው ህዝባችን ለወያኔ ያለውን ንቀት፣ የወያኔን የተጣመመ ህግ አልቀበልም ብሎ በማደም ብቻ ሳይሆን፣ የወያኔን የጥይት ጥቃት በመመከት ጭምር እያሳየ ነው። ጥይትና አፈና የማያንበረክከው ህዝባችን፣ ወያኔን ስልታዊ በሆነ ትግሉ ወደ ማይመለስበት መቃብር እየከተተው ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ህዝባችን እየተገበራቸው ያለው የትግል ስልቶች፣ ነጻነት ወዳዱን ህዝብ ሁሉ የሚያኮራ፣ ገዳዮችን የወያኔ ጀሌዎች ደግሞ የሚያስበረግግ ነው።

ወያኔ በአምሳሉ የፈጠረው የአየር ሃይል ሲፈተሽ

አየር ሃይል ለአንዲት አገር መከላከያ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ እጅግ የላቀ ነው። በዚህም አገራችን ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ የራሷን የአቪየሽን ተቋም በመመስረት ግንባር ቀደምት ነች።ወይንም ነበረች ሳይሻል አይቀርም።ያኔ የአፍሪካ አገራት በቅኝ ግዛት ቀንበር ስር ወድቀው በሚማቅቁበት ዘመን ኢትዮጵያ የራሷ ጠንካራ የአየር ሃይል ተቋም ነበራት።በኢትዮጵያ የአቪየሽን ታሪክ የሚጀምረው በ1921 ዓ/ም እንደጀመረ ታሪክ ይነግረናል።የኢትዮጲያን አየር ሃይል በዘመናዊ መልኩ ማደራጀት የተጀመረው ደግሞ በ1936 ዓ/ም ከፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ በኋላ ነው። አየር ሃይሉ ከሌሎች የሃገሪቱ መከላከያ ተቋማት ጋር በመጣመር የሃገሪቱን ዳር ድንበርና ሉአላዊነትን ለማስከበር በተደረጉ ተጋድሎዎች  እስከደርግ ወድቀት ድረስ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል። በተለይም የኢትዮጵያን የአየር ክልል በማስከበር ረገድ የማይተካ ሚና ነበረው።

በ1969 ዓ/ም የሱማሊያው መሪ ጀነራል ዚያድ ባሬ የኦጋዴንን መሬት በመጠቅለል ታላቋን ሶማሊያ ለመመስረት ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት የኢትዮጵያ የአየር ሃይል የዚያድባሬን ህልም ወደቅዠት በመቀየር አኩሪ ታራክ በመስራት ረገድ የፊታውራሪውን ድርሻ ወስዷል።እናም በታጠቀው ዘመናዊ መሳሪያ እጅግ የሚልቀውን የሱማሊያውን የአየር ሃይል ተቋም ለምን ጉድ ባሰኘ መልኩ ድባቅ መትቶቷል።በወቅቱ ኢትዮጵያ ለጦርነቱ በዋናነት ያሰለፈቻቸው F 5E የተባሉ የአየር ላየር ተዋጊ ጀቶች  በቁጥር ከ8 የማይበልጡ ሲሆኑ እንዲሁም ቁጥራቸው ከ—– የማይበልጡ F 5A ቦምብ ጣይ ጀቶች ብቻ ነበሯት።የዚያድ ባሬው የሱማሊያ አየር ሃይል በበኩሉ በመቶዎች በሚቆጠሩ በጊዜው እጅግ ዘመናዊ በሆኑ ሶቪያት ሰራሽ MIG 19 እና MG-21 በተባሉ ተዋጊና ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖች እስከ አፍንጫው የታጠቀ ነበር።ኢትዮጲያ ለጦርነቱ ካሰለፈቻቸው የጦር ጀቶች አንጻር ሲመዘን የሶማሊያው አየር ሃይል በዘመናዊነቱም ሆነ በቴክኖሎጂ ጥራቱ የነበረው ብልጫ እጅግ የላቀና ለውድድርም የማይቀርብ ነበረ። ታዲያ በወቅቱ እንዴት የኢትዮጵያው የአየር ሃይል እጅግ የሚልቀውን የሱማሌውን የአየር ሃይል ተቋም  በልጦ ተገኘ? ጥያቄው ይሄ ነው።

ትልቁ ሰውዬና የጅጅጋ ሕዝብ ሰቆቃ

ከሙክታር ኦማር የእንግሊዝኛ መጣጥፍ በግርድፉ የተተረጎመ

በድህረ ቅኝ ግዛት ዘመኗ አፍሪካ የገባችበትን የአስተዳደር ብልሹነትና የፖለቲካ ቀውስ አስመልክቶ  እንደ ካሜሩናዊው የማህበረሰብ ጥናት ተመራማሪ አቺሌ ሜምቤ  በትክክል የተረዳና የጻፈ ምሁር  ጥቂት ነው። ” የብልግና ውበት” በተባለው ድንቅ ጥናታዊ ጽሁፉ የነጮቹን ጌቶቻቸውን ቦታ ተረክበው አፍሪካን እየተጫወቱባት ያሉት “ጌቶቹ አምባገነን መሪዎቻችንና ባለስልጣናቱ” የፈጠሩት ስርዓት ጥቂቶቹን ጨቋኞችና ብዙሃኑን ተጨቋኝ ህዝብ በአንድ ላይ ጠፍንጎና አቆላልፎ አስከፊ ወደሆነ የስብዓና ዝቅጠትና ሕይወት አልባ ወደሆነ የደመ ነፍስ ጉዞ እንደሚጎትታቸው በሚያስደንቅ ብዕሩ ገልጾታል።

ገደብ አልባ በሆነ የስልጣን ኮርቻ ላይ ለዕድሜ ልክ የተፈናጠጡት ትላልቆቹ አምባገነኖች በመንፈሳቸው የበሰበሱና ፍቅርና ሰላም አልባ ውስጣዊ ማንነታቸው ከውጭ በሚታየው አካላዊ ቅርጻቸው ላይ ይነበባል ይላል አቺሌ ሜምቤ። እነኚህ የቁም ሙታኖች፣ ቦርጫቸው አለቅጥ ተንዘርጥጦ፣ ፊታቸው ጤናማ ባልሆነ ውፍረት ተነፍቶና ላባቸው አለማቋረጥ ሲወርድ፣ ቅርጽ የለሽ ደረታቸውና ሆዳቸው በጸጉር ተወርሮ ለሚያያቸው ለዓይን የሚቀፉ ሰው መሰል አውሬዎች ያስመስላቸዋል። ይህ ጸያፍ የሆነውን አካላዊ ቅርጻቸውን እዚህ ደረጃ ላይ ያደረሰው ደግሞ ስርዓትና ገደብ የሌለው የአመጋገብ ባህላቸው ነው። ከሆዳቸው ፍቅር በተጨማሪም ለዚህ እንስሳዊ ማንነት የዳረጋቸው ስልጣናቸውን ተገን አድርገው የሚፈጽሙት የዜጎች ላይ ጥቃትና ግድያ፣ ለከት የሌለው የወሲብ ፍላጎትና ነውረኛ እርካታ፣ የእርስ በርስ የመጠላለፍ ሴራ፣ አጠቃላይ የምግባረ ብልሹነትና ነፍስን ለስጋ ፍጹም አሳልፎ የመሸጥ ክፉ ውጤት ነው ይላል አቺሌ ሜምቤ።

Thursday, July 6, 2017

የሰኔ አንድ ሰማዕታት አደራ በትግላችን እውን ይሆናል!

ሰኔ አንድ በኢትዮጵያ የሰማዕታት ታሪክ ልዩ ስፍራ የሚሰጠው ነው። ሰኔ 1 ቀን 1997 ዓም እንደ የካቲት 12 ቀን 1929 ዓም ሁሉ ፣ መብታቸውን የጠየቁ፣ በባርነት፣ በጭቆና እና በዘር መድሎ አንኖርም ያሉ ኢትዮጵያውያን በመለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ደማቸው እንደ ጎርፍ እንዲፈስ የተደረገበት ዕለት ነው። በየካቲት 12 እና በሰኔ 1 መካከል ልዩነት ቢኖር፣ የገዳዮች ማንነት ነው። የካቲት 12 ቀን 2009 ዓም የአገራቸውን በጣሊያን መወረር የተቃወሙ የቁርጥ ቀን ልጆች በፈጸሙት ታሪካዊ የአልገዛም ባይነት ተጋድሎ ፣ በአረመኔው ግራዚያኒ ትእዛዝ ተጨፍጭፈዋል። ሰኔ 1 ቀን 1997 ዓም ደግሞ የጭቆናን ቀንበር ሰብረው ለመውጣት ትግል ያደረጉ፣ በአገራቸው ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ተገንብቶ ማየት የሚሹ፣ በግንቦት 7 1997 ዓም ምርጫ ወላጆቻቸው የሰጡት ድምጽ እንዲከበርላቸው የጠየቁ እንቦቀቅላዎች፣ አገር በቀል በሆነው የግራዚያኒ የመንፈስ ልጅ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ፣ ከ40 በላይ ወጣቶች በአደባባይ የተጨፈጨፉበት፣ ብዙዎች ለአካል ጉዳትና ለእስር የተዳረጉበት ነው።

እነዚህ ሰማዕታት የህይወትና የአካል መስዋትነት ሲከፍሉ በህይወት ላለነው ታላቅ አደራ አስቀምጠውልን ማለፋቸውን ምንጊዜውም ልብ ልንል ይገባል። ሰማዕታቱ “ኢትዮጵያችን ዘረኝነትን፣ ጭቆናንና አፈናን አሸንፋ፣ በዲሞክራሲ፣ በፍትህና በነጻነት የምትመራ አገር እስከምትሆን ድረስ ትግላችሁን ቀጥሎ፣ ያን ጊዜ የእኛ ደም ከንቱ ሆኖ አየቀርም” የሚል አደራ አስቀምጠውልን አልፈዋል። ይህ ታሪካዊ አደራ ዛሬ ዛሬ እየተደረገ ላለው የሞት ሸረት ትግል የማንቂያ ደወል ሆኖ እያገለገለ ነው። ዛሬ በመላ አገራችን የተቀጣጠለ የመጣው የነጻነት ትግል ለእነዚህ ሰማዕታት ትልቅ ርካታን የሚሰጥ ነው። በእያንዳንዱ ቀን በምናደረገው ትግል ውስጥ ሰማዕታቱ አብረው ይዘከራሉ።

የሰኔ 1 ሰማዕታትን አደራ ጠብቀው የተጓዙ በርካታ ወጣቶች የህይወት መስዋትነት ከፍለዋል፣ እየከፈሉም ይገኛሉ። ከሰኔ 1 ቀን 1997 ዓም ወዲህ በማላ አገሪቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ለነጻነታቸው የህይወት መስዋትነት ከፍለው። በአወዳይ፣ አምቦ፣ ሃሮማያ፣ አርሲ፣ ጎንደር፣ ጎጃም እና በሌሎች በርካታ የአገሪቱ ክፍሎች በተካሄዱ የነጻነት ትግሎች በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ብቻ ከ2 ሺ ያላነሱ ሰዎች በአረመኔው አገዛዝ በግፍ ተገድለዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። በየእስር ቤቱ እየማቀቁ የሚገኙትንማ ቤት ይቁጠረው። የሰኔ ሰማዕታት የለኮሱት ትግል ፣ አደራቸውን በተቀበሉ ወጣቶች እየጎመራ ሲሄድ ስንመለከት ፣ የሰማዕታቱ ደም ከንቱ አለመሆኑን ብቻ ሳይሆን፣ አደራውን በተቀበሉ ወጣቶችም እንድንኮራ አድርጎናል።

ትግል እንደ ዱላ ቅብብሎሽ አንዱ ለሌላው እያስረከበው የሚሄድ ነገር ነው። አንድን ትግል አንድ ግለሰብ ወይም የአንድ ትውልድ አባላት ብቻ ከዳር ያደርሱታል ብሎ ማመን ስህተት ነው። የሰኔ ሰማዓታቱ የትግሉ ሻማ ለዚህ ትውልድ አስረክበዋል፣ ይህ ትውልድ ደግሞ ሻመው እንዳይጠፋ ብቻ ሳይሆን ይበልጥ እንዲቀጣጠል አድርጎ ለሚመጣው ትውልድ ያስረክባል፣ የሚመጣው ትውልድም ለቀጣዩ ትውልድ እያስረከበ ይሄዳል። የህወሃትን ዘረኛና አምባገነን አገዛዝ ማስወገድ ከትግሉ ግቦች ውስጥ አንዱ ቢሆንም፣ በዚህ አገዛዝ ቦታ ላይ የሚተካውን ዲሞክራሲያዊ ስርዓት መፍጠር ፣ የተፈጠረው ስርዓት በጠንካራ አለት ላይ እንዲቀመጥና ቁመናውንና ጥንካሬውን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ እንዲሄድ ማድረግ የትውልዶች ስራ ነው። የዚህ ትውልድ የቤት ስራ የህወሃትን አገዛዝ አስወግዶ በምትኩ የዲሞክራሲያዊ ስርዓትን መሰረት መጣል ነው ብሎ ድርጅታችን አርበኞች ግንቦት7 በጽኑ ያምናል። ለዚህ ስርዓት መመስረትም አስፈላጊውን መስዋትነት እየከፈለ ይገኛል፤ ይህ ስርዓት እውን እስኪሆንም መከፈል ያለበትን መስዋትነት ሁሉ ይከፍላል። አርበኞች ግንቦት7 የሰኔ ሰማዕታት ያስረከቡትን አደራ ምንጊዜም ጠብቆ አደራቸውን ዳር ለማድረስ የሚተጋ ድርጅት ነው። ሰኔ 1 በአርበኞች ግንቦት7 ታጋዮች ዘንድ ልዩ ስፍራ የሚይዝ ቀን እንደመሆኑ፣ በዚህ ቀን ሁሉም ታጋይ የትግሉን ቃል ኪዳን ያድሳል። ሰማዕታቱንም ይዘክራል።

የሰኔ ሰማዕታት አደራውን ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ያስረከቡት በመሆኑ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በዚህ አደራ ዙሪያ ታቅፎ ትግሉን ማካሄድ አለበት። የህወሃትን ዘረኛና ጨፍጫፊ አገዛዝ ለማስወገድ ብቻ ሳይሆን፣ በተነቀለው ጉቶ ላይ የዲሞክራሲያንና የነጻነትን ችግኝ ለመትከልና ለማሳደግ የመላው ኢትዮጵያዊን ርብርብ የሚጠይቅ በመሆኑ፣ ሁላችንም የሰኔ ሰማዕታትን አደራ እያስታወስን እጅ ለእጅ ተያይዘን ትግላችንን አጠናክረን እንድንቀጥል ዛሬም አገራዊ ጥሪ እናቀርባለን።
ክብር ለሰኔ አንድ ሰማዕታት! ድል ለኢትዮጵያ ነጻነት ወዳዶች ሁሉ!

Monday, February 20, 2017

የህወሓት ተላላኪ ሆኖ በርካታ በደሎችን በህዝብ ላይ ሲፈፅም የነበረው ደረጄ መከታው የተባለው ግለሰብ በአርበኞች ግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች እርምጃ የተወሰደበት መሆኑ ታወቀ፡፡

(የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ ሬድዮ)
የህወሓት ተላላኪ ሆኖ በርካታ በደሎችን በህዝብ ላይ ሲፈፅም የነበረው ደረጄ መከታው የተባለው ግለሰብ በአርበኞች ግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች እርምጃ የተወሰደበት መሆኑ ታወቀ፡፡

ሰሞኑን በአርበኞች ግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች የተገደለው ደረጄ መከታው የተባለው ግለሰብ ከዚህ በፊት የቀድሞው የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር አባል የነበረና በድርጅቱም ግዳጅ በመላክ ወደ ኢትዮጵያ ሲሄድ አብሮት ሲሄድ የነበረውን የትግል ጓዱንና ድርጅቱን በመካድ የጠላት ተባባሪ በመሆን በታጠቀው የድርጅቱ መሳሪያ ጓዱን በመግደል ለወያኔ ስርዓት እጁን በመስጠት ተቀላቅሏል፡፡ ከአገዛዙ ተቀላቅሎ በመኖር ላይ እያለም ከአንድ የስርዓቱ አገልጋይ ጓደኛው ጋር በመሆን የትጥቅ ትግሉን ይደግፋሉ እንዲሁም በገዢው ቡድን ላይ ህዝብን ያሳምፃሉ ብለው የሚፈርጇቸውን ሰዎች እንዲሰልሉ በአገዛዙ ተቀጥረው ሲሰሩ የነበረ ቢሆንም ከእለታ አንድ ቀን ሰው በመግደል ታስረው የቆዩ ሲሆን ባልታወቀ ምክንያትም ብዙም ሳይቆዩ ከእስራት ተፈተዋል፡፡ ይኸው ደረጄ መከታው የተባለው ግለሰብ ከእስራት ከተለቀቀ በኋላም ከወያኔ ደህንነት ጋር በመሆን በአሳቻ ሰዓትና በማታ ንፁሃን ዜጎችን በማደን ሲያሳስርና ሲያስደበድብ በተጨማሪም ሲያስገድል መቆየቱን የአካባቢው ህዝብ የአይን ምስክሮች ናቸው ፡፡

በመሆኑም ይህን የህዝብ ሰቆቃ ሰምቶ መታገስ ህሊናቸው ያልፈቀደላቸው በአርበኞች ግንት 7 ስር በሃገር ቤት የሚንቀሳቀሱ የውስጥ አርበኞች በዚሁ ደረጄ መከታው በተባለው ግለሰብ ህዝብ የሚደርስበትን በደልና ይኸው ግለሰብ ለወያኔ መላላክን ምርጫው ያደረገ በንፁሃን ዜጋ ሞት የሚደሰት መሆኑን በመመልከታቸው የአርበኞች ግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች ተከታትለው ሊገድሉት ችለዋል ፡፡

አሁንም በዚህ ተግባር ላይ ተሰማርተው የሚገኙ ከህዝብ ጎን መቆም ሲገባቸው ለጥቅም ያደሩ ግለሰቦች መለስ ብለው መሳሳታቸውን አምነው ከህዝብ ጎን ካልተሰለፉና የህዝቡን ትግል ካልደገፉ ወይም ከቀደመው እኩይ ተግባራቸው ተቆጥበው ማሳሰራቸውንና ማስደብደባቸውን እስካላቆሙ ድረስ በሰላም መኖር እንደማይችሉና የእነርሱም እጣ ፈንታ እንደ ደረጄ መከታው እንደሚሆን የአርበኞች ግንቦት 7 የውስጥ አርበኞች ከሃገር ቤት ባደረሱን መረጃ አስታውቀዋል ፡፡