Friday, October 25, 2013

የአንድነት አመራር አፈና እና ድብደባ ተፈጸመባቸው

የአንድነት አመራር አፈና እና ድብደባ ተፈጸመባቸው ——————————- የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የብሄራዊ ምክር ቤት አባልና በሚሊዩኖች ድምጽ ለነጻነት ሕዝባዊ ንቅናቄ በተለያዩ ከተሞች በመንቀሳቀስ ከፍተኛ ተሳትፎ ያደረጉት መምህር አበበ አካሉ ትናንት 14/02/06 ዓ.ም የደህንነት መስሪያ ቤት አባላት ነን ባሉ ሶስት ቅጥረኞች የግድያ ሙከራና አካላዊ ጥቃት እንደደረሰባቸው ለፍኖተ ነጻነት ይፋ አድርገዋል፡፡ ሰላማዊው ታጋይ እንደተናገሩት በምሳ ሰዓት ኮተቤ መሳለሚያ አካባቢ ለስራ ጉዳይ ሲንቀሳቀሱ ህገ ወጦቹ ያካራክሯት የነበረችን ላንድክሩዘር መኪና የእግረኛ መንገድ እንድትዘጋ በማድረግ አቶ አበበን በሀይል በመኪናው በመጫን ወደማያውቁት ሰዋራ ቦታ በመውሰድ ቤቶች በሚሰሩበት አካባቢ ከመኪናዋ በማውረድ ሺሚንቶ ላይ በማስተኛት በሰላማዊ መንገድ የሚያካሂዱትን ትግል እንዲያቆሙ ይህ ካልሆነም‹‹ በሽብርተኝነት በመወንጀል መንግስትን በሀይል ለማውረድ ትሰራለህ›› በማለት እንደሚወነጅሏቸው በመንገር በቃላት ለምግለጽ በሚቸግር ሁኔታ ድብደባ እየተፈራረቁ እንዳካሄዱባቸው ተናግረዋል፡፡ መምህር አበበ ከቀኑ 6፡30 እስከ ምሽቱ 1፡00 ሰዓት ግለሰቦቹ ሽጉጥ ደግነውባቸውና የማያውቁትን የአልኮል ቃና ያለው ፈሻሽ ነገር በመጋትና ከሲሚንቶ ጋር አጣብቀው በመርገጥ የግድያ ሙከራ ካደረጉበቫቸው በኋላ ከምሽት ላይ በመኪና አውጥተው እንደጣሏቸው ለፍኖተ ነጻነት ተናግረዋል፡፡ ፍኖተ ነጻነት ፓርቲው አመራሩ በህገ ወጥ መንገድ መያዛቸውንና መደብደቡን በተመለከተ ምን እያደረገ ነው በማለት የፓርቲውን ከፍተኛ አመራሮች በመጠየቅ ከአመራሮቹ ‹‹ጉዳዩን በማጣራት ላይ እንገኛለን፡፡አውሬነት የተሞላበትን አስነዋሪ ድርጊትም በቸልታ የምናልፈው አይሆንም››የሚል ምላሽ አግኝታለች፡፡ መምህር አበበ አካሉ በአሁኑ ወቅት በመኖሪያ ቤታቸው ተኝተው ይገኛሉ፡፡ ሰላማዊው ታጋይ ባለትዳርና የሶስት ልጆች አባት ናቸው፡፡

No comments:

Post a Comment