Friday, December 20, 2013

ዓረና መድረክ ከተምቤን ኗሪዎች ጋር ለመወያየት እሁድ ህዝባዊ ስብሰባ ጠርቷል (አብርሃ ደስታ ከመቐለ/ትግራይ

ዓረና መድረክ ከተምቤን ኗሪዎች ጋር ለመወያየት እሁድ ታህሳስ 13, 2006 ዓም በዓብይ ዓዲ ከተማ (ማዘጋጃቤት አዳራሽ) ህዝባዊ ስብሰባ ጠርቷል። የዓረና አባላት ከትናንት ሐሙስ ጀምሮ በተለያዩ የተምቤን ከተሞች ቅስቀሳ እያካሄዱ ነው። እስካሁን የተምቤን ህዝብ በጥሩ መንፈስ እየተቀበላቸው ሲሆን የአከባቢው አስተዳዳሪዎች ግን እያንገራገሩ ነው። አስተዳዳሪዎች ቅስቀሳ የሚያካሂዱ የዓረና አባላትን ይሰድባሉ፣ ዕንቅፋት ይፈጥራሉ። የዓረና አባላት ቅስቀሳ በማድረጋቸው በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል። ቅስቀሳው ግን በሌሎች አባላትም ቢሆን ይቀጥላል። የማይጨው ከተማ አስተዳዳሪዎች በጥሩ መንፈስ ተቀብለውን ነበር። የተምቤኖቹ ግን ለምን አንገራገሩ? ህወሓት ምክንያት አለው።

ኢህአዴግን ሙሉ በሙሉ ለማሸነፍ በትግራይ ክልል መንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ምክንያቱም ትግራይ ክልል የህወሓት መሰረት ነው። ኢህአዴግ ያለ ህወሓት ዋጋ የለውም። ምክንያቱም ሌሎች የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በህወሓት ጠመንጃ ድጋፍ የሚኖሩ እንጂ የህዝብ ድጋፍ የላቸውም። ስለዚህ የህወሓት የትግራይ መሰረት ከተናጋ ኢህአዴግ ይናጋል።

ከትግራይ ክልል ደግሞ ሁለት ቦታዎች በደምብ መያዝ በቂ ነው፤ ተምቤንና ዓጋመ። በፖለቲካ ዘርፉ የተምቤን ህዝብ ከጎንህ ማሰለፍ ከቻልክ መለው ትግራይ መቆጣጠር ቀላል ይሆናል። (ምክንያት ሌላ ግዜ)። ሁለተኛው ቁልፍ የትግል መሰረት የዓጋመ ህዝብ ነው (በኢኮኖሚ ዘርፍ)። (ምክንያት ሌላ ግዜ)። የዓጋመ ህዝብ ከጎንህ ለማሰለፍ ግዜ ሊወስድ ይችላል። የተምቤን ግን ትንሽ ጥረት ማድረግ በቂ ነው። እናም ጉዟችን ወደ ተምቤን ነው።

ህወሓትም ይሄ የተምቤን ጉዳይ በደምብ የተረዳው ይመስላል። በተምቤን ዓብይ ዓዲ ከተማ በምናደርገው ህዝባዊ ስብሰባ ለመረበሽ የተዘጋጀ ይመስላል።

እሁድ በዓብይ ዓዲ ከተማ ማዘጋጃቤት አዳራሽ ስለሚደረገው ስብሰባ ተጨማሪ ዘገባ በወቅቱ ይቀርባል።

ተጨማሪ ማብራሪያ፡ ከህወሓት የትጥቅ ትግል ወቅት ጀምሮ በትግራይ ክልል ከሚገኙ ህዝቦች ዓቅሙ እያላቸው በህወሓት የተንኮል አገዛዝ ምክንያት ተጨቁነው (ታፍነው) የሚኖሩ ህዝቦች የተምቤንና የዓጋመ ናቸው። የተምቤን ህዝብ የፖለቲካ ዓቅም አለው። የዓጋመ ህዝብም የኢኮኖሚ ዓቅም አለው። ሁለቱም ህዝቦች (የተምቤንና ዓጋመ) መቀስቀስ ከተቻለና አብረው ከሰሩ መላው ትግራይ አንቀሳቅሰው ህወሓትን ሙሉ በሙሉ ማሸነፍ ይችላሉ። ህወሓት አሁንም የሁለቱም ህዝቦች መነሳት ያስፈራዋል። ተምቤኖች በፖለቲካ እንዳይሳተፉ ይደረጋል፤ ዓጋሜዎቹም በኢኮኖሚ እንዲዳከሙ ይደረጋል። ተምቤኖች እንቅስቃሴ ጀምረዋል። ለዚህም ነው የህወሓት አስተዳዳሪዎች በተምቤን ለሚደረግ የስብሰባ ቅስቀሳ ለመረበሽ የተነሱት (የተምቤን አስተዳዳሪዎች የተምቤን ተወላጆች አይደሉም)። ህወሓት በተምቤንና ዓጋመ ምንም ድጋፍ የለውም። በጠመንጃ ሃይል ነው የሚገዛው።

No comments:

Post a Comment