Thursday, January 30, 2014

የኢትዮጵያ መንግስት የግንቦት7 መሪዎችን ኮምፒዩተሮች በዘመናዊ የስለላ መሳሪያዎች ሲሰልል እንደተደረሰበት አንድ አለማቀፍ ተቋም አጋለጠ

ጥር ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የህዝቦችን ደህንነት ከመንግስታት ጥቃት ለመከላከል የተቋቋመው ፕራይቬሲ ኢንተርናሽናል የተባለው  ተቋም ለእንግሊዝ መንግስት የገቢዎቸና ጉምሩክ መስሪያ ቤት በጻፈው ደብዳቤ “ጋማ ኢንተርናሽናል የተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ በአለም ላይ የሰብአዊ መብቶችን በመጣስ ለሚታወቁ አገሮች ኮምፒይተሮችን፣ የሞባይልና የስካይፕ የስልክ ግንኙነቶችን እንዲሁም የኢሜል ልውውጦችን በርቀት ሆኖ ለመከታተል የሚያስችለውን ፊን ፊሸር ወይም ፊን ስፓይ በሚል ስም የሚጠራውን የመሰለያ መሳሪያ ከአውሮፓ ህብረት ውጭ ላሉ አገሮች በመሸጥ ዜጎች እንዲሰለሉና ደህንነታቸው አደጋ ላይ እንዲወድቅ በማድረጉ  ምርመራ እንዲጀመር” ሲል ጠይቋል።
የግንቦት7 ከፍተኛ አመራር በሆኑት በ ዶ/ር ታደሰ ብሩ የግል ኮምፒዩተር ላይ የመሰለያ ቫይረሱ መገኘቱን በቶሮንቶ ዩኒቨርስቲ የሙንክ ስኩል ግሎባል አፌርስ የምርምር ተቋም የሆነው ሲትዝን ላብ ማረጋገጡን ፕራይቬሲ ኢንተርናሽናል በደብዳቤው ገልጿል።
የመሰለያ መሳሪያው የሰብአዊ መብቶችን በሚጥሱ 36 አገራት ላይ መሸጡን የገለጸው ፕራይቬሲ ኢንተርናሽናል፣ በተለይም በቬትናም፣ ማሌዚያና ኢትዮጵያ የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለመሰለያነት እየዋለ ነው ብሎአል።
በኢትዮጵያ የግንቦት7 ከፍተኛ አመራር የሆኑት ዶ/ር ታደሰ ብሩ ኮምፒተራቸው ሲሰለል መቆየቱን የገለጸው ፕራይቬሲ ኢንተርናሽናል፣ በአንድ የብሃሬን የሰብአዊ መብት ተማጓች ኮምፒዩተር ላይም ተመሳሳይ የስለላ ሶፍት ዌር መገኘቱን ገልጿል።
ዶ/ር ታደሰ ብሩ ለፕራይቪሴ ኢንተርናሽናል ጠበቃ የምስክርነት ቃላቸውን መስጠታቸውን ተናግረዋል። ፕራይቪሲ ኢንተርናሽናል የስለላ ቫይረሱን የሸጠውን ጋማ ኢንተርናሽናልን የተባለውን ድርጅት ወደ ፍርድ ቤት ለመውሰድ ማቀዱን ዶ/ር ታደሰ ገልጸዋል፡
ከዶ/ር ታደሰ ጋር የተደረገው ቃለምልልስ ከዜናው በሁዋላ ይቀርባል።

Thursday, January 16, 2014

በሶማሊያ ክልል 47 ሰዎች መገደላቸውን የአገር ሽማግሌዎች ለአቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ በላኩት ደብዳቤ ገለጹ

ጥር ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በቀላፎ አካባቢ የሚኖሩ የየረር ባሬ ጎሳ  የአገር ሽማግሌዎች ለጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ያስገቡትና መረጃው ለኢሳት እንዲደርስ በሚል በላኩት መረጃ ፣ የሶማሊ ክልል ፕሬዚዳንት አብዲ ሙሀመድ ኡመር እና ጄኔራል አብርሀም በቅጽል ስማቸው ኳታር የሚመራው ልዩ ሚሊሺያ እየተባለ የሚጠራው ሀይል ታህሳስ 1 እና 2 በከፈተው ተኩስ በትምህርት ላይ የነበሩ ህጻናትንና ወጣቶችን ጨምሮ 47 ሰዎችን መግደሉን የሟቾቹን ስም ዝርዝር በመጥቀስ ገልጸዋል።
ልዩ ሚሊሺያው ተማሪዎች በትምህርት ላይ እንዳሉ ተኩስ መክፈቱን የአገር ሽማግሌዎቹ በደብዳቤያቸው ላይ የገለጹ ሲሆን፣ የፌደራሉ መንግስት በአስቸኳይ ደርሶ እንዲታደጋቸውም ጠይቀዋል።
የየረር ባሬ ጎሳ አባላት የክልሉ መንግስት ጭቆና ያደርስብናል በማለት ራሳቸውን በራሳቸው ለማስተዳደር ሲጠይቁና በተደጋጋሚ እርምጃ ሲወሰድባቸው እንደነበር አውስተው ፣ በቅርቡ የተወሰደው አስከፊ እርምጃ ግን በደቡብ አፍሪካ እንሰማው የነበረ እንጅ በአገራችን ላይ የሚፈጸም ነው ብሎ ለማመን ይቸግራል ብለዋል።
ባከፍ ድር እየተባለ በሚጠራው ትምህርት ቤት ላይ እና በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ በተከፈተው ተኩስ  ኡመር ሀጂ ሙሀመድ፣ ሙኒየር አዳቢ ሙሀመድ፣ ካሊድ ሙሀመድ አብዲ፣ ሀሰን አሊ ቤላህ፣ ወ/ሮ ሀሺ ሃጅ መሀመድ፣ ማዴቦ ሞሀመድ አብዲ፣ ሀጂ ኑሩ  ሙሀመድ፣ ማዴባ ሞሀመድ አብዲ፣ መሀለም ካልየ ደውሀሊ፣ አብረሳ አደም ሞሀመድ፣ ሀጂ ኑሩ ሙሀመድ፣ ሞርየ ሞሀመድ ካር፣ ጋለው አብዲ የኑስ፣ የሱፍ ረምሳ አደም፣ ካሊባን ሳራህ ኡመርነህ፣ ኡስማን  አብደሌ፣ ጠኒ ሙሀመድ ጣር፣ መንሲን ሙሀመድ ጣር፣ ደልግ አሊ ኡመር፣ ካሊድ ሙሀመድ አብደሌ፣ ሀሰን ማሌ አብዱላሂ፣ የሱፍ የሄ፣ ጀማል ኡመር ጠባህ፣ ሙሀመድ ኡስማን ጦለቤ፣ አህመድ መሀመድ፣ አሊ ቀሲም ቀለኔ፣ ባቡል ዳሩር፣ ከሬ ባዴ፣ ማን ኦረየ ባዴ፣ ጦርየ አዊ ባዴ፣ አብዲ ሸክለሌ፣ አሊ ኡስማን ቀለሌ፣ ሊሞ አሌባዴ፣ ማዲህ አብዱልኑር፣ ዙቅ ኡር እና የሌሎች የ12 ተጨማሪ ሟቾች ስም ዝርዝር ቀርቧል።
በአካባቢው የተነሳው ውጥረቱን ተከትሎ በትናንትናው አለት ደግሞ ተጨማሪ ሀይል ወደ አካባቢው መጓዙን ሽማግሌዎች ገልጸዋል።
ክልሉን ከጀርባ ሆነው የሚያንቀሳቅሱት ጄኔራል አብርሀ በክልሉ ለሚፈጸመው የሰብአዊ መብት ጥሰት ተጠያቂ መሆናቸውን የአካባቢው ሰዎች ይገልጻሉ።
መረጃው እንደተላከልን የክልሉን ፕሬዚዳንት ለማነጋገር በተደጋጋሚ ሙከራ ብናደርግም ሊሳካልን አልቻለም። ጠ/ሚንስትሩ ለተጻፈላቸው ደብዳቤ እስካሁን መልስ አለመስጠታቸውን ሽማግሌዎቹ ገልጸዋል።
የሶማሊ ክልል በቅርቡ የብሄር ብሄረሰቦችን ቀን ማክበሩ ይታወሳል።

የኢትዮጵያን ታሪክ ጥላሸት የመቀባት አባዜ (ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም)

January 16, 2014
ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም
ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ
ጥር 7 ቀን 2006 ዓ.ም

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ያለው ገዥው አካል በ19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ንጉስ የነበሩት የዳግማዊ አጼ ምኒልክ መቶኛ የሙት ዓመት በዚህ በያዝነው ዓመት (በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር) እየተከበረ ባለበት ወቅት ሙሉ ጊዜውን በመስጠት ንጉሱ የሰሩትን ታላቅ ስራ ሁሉ በማጣጣል እና ጥላሸት በመቀባት ዘመቻ ላይ በመጠመድ ታሪክ የማጠልሸት ድራማውን በመተወን ላይ ይገኛል፡፡ የታሪክ ማጠልሸት ዘመቻው በዋናነት እየተከናወነ ያለው ለገዥው አካል ቅርበት ባላቸው ታማኝ ሎሌዎች፣ የጥቅም ተጋሪዎች እና የእራሳቸው ስብዕና በሌላቸው አሻንጉሊቶች አማካይነት ነው፡፡ ገዥው አካል ሲያስነጥሰው መሃረብ ይዘው በሚቀርቡ አጎብዳጆቹ አማካይነት የጥላቻ መርዛማ ቃላትን፣ የሚቆጠቁጡ ባዶ ዲስኮሮችን እና እርባናየለሽ ምዕናባዊ ስዕል በአዕምሮው ላይ እየፈጠረ አጼ ምኒልክ የግዛት ማስፋፋት ጥማታቸውን ለማርካት ሲሉ በዜጎች ላይ የጭካኔ ተግባራትን እንደፈጸሙ በማስመሰል ለምንም የማይጠቅሙ እርባናየለሽ እና ተራ አሉባልታዎችን በማሰራጨት ላይ ይገኛል፡፡

የገዥው አካል ድንጉላ አገልጋዮች በማናቸውም የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች በመሰማራት ታሪካዊ ቅጥፈቶችን፣ አሳሳች ዘገባዎችን፣ የሀሰት ታሪክ ፈጠራዎችን፣ ሆን ተብሎ በሀሰት ላይ የተመሰረቱ መረጃዎችን እና ነጭ ውሸቶችን እንደ በቀቀን እየደጋገሙ በማሰራጨት ላይ ይገኛሉ፡፡ የዕኩይ ዓላማው አራማጆች በታላቁ የኢትዮጵያ መሪ ላይ ግነታዊ ኩምክና በመስራት፣ በማዋረድ እና እውነተኛውን ስብዕናቸውን ጥላሸት በመቀባት የስሜት ፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ውስጥ በመዘፈቅ ጌቶቻቸውን ለማስደሰት በታለመ ዕኩይ ምግባር ላይ ተጠምደው ይገኛሉ፡፡ የታላቁ መሪ ነብስ ከስጋቸው ከተለየች ከአንድ መቶ ዓመታት የጊዜ ቆይታ በኋላ የተቀበረን ጉዳይ በማንሳት ታላቁን መሪ ሰይጣናዊ ስብዕና እንደነበራቸው ለማስመሰል በማሰብ የዕኩይ ምግባር ጎተራዎቹ የቻሉትን ያህል ጥረት ለማድረግ ሞክረዋል፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ በህይወት ከተለዩ ሁለት ዓመታት እንኳን ሳይሞላቸው የዕኩይ ምግባራት ቋቶቹ የኢትዮጵያ አዳኝ መልዓክ ሊያደርጓቸው ይፈልጋሉ፡፡

በአሁኑ ጊዜ በዳግማዊ አጼ ምኒልክ ላይ በተከፈተው የገፍ ወይም የኃይል የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ወይም ደግሞ የአጼ ምኒልክን የሙት መንፈስ ደጋግመው በማንሳት ፍጹም ጥላቻ እና የጥላቻ አመለካከት እንዲንሰራፋ በገዥው አካል ስልታዊ እና የተቀነባበረ ዘመቻ የማካሄድ አመክንዮ ለማንም ቢሆን ሊደንቅ አይገባም፡፡ ሀቁ አንድ እና አንድ ብቻ ነው፡፡ የኸውም የምኒልክን ስም ጥላሸት በመቀባት (ሰይጣናዊ ስብዕና በመስጠት) በሚሽከረከር ጉዳይ ላይ ብቻ የሚቆም ጉዳይ አይደለም፡፡ ነገር ግን በቅርቡ በህይወት የተለዩትን የገዥውን አካል የአለቆች ሁሉ አለቃ (Capo di tutti capi) አቶ መለስ ዜናዊን በመላዕክነት ቀብቶ ለማቅረብ የታቀደ ዕኩይ ምግባር ነው፡፡

Tuesday, January 14, 2014

አንዱዋለም ግንቦት ሰባት ከተባለ እኔም ግንቦት ሰባት ነኝ – ግርማ ካሳ

«በሕገ መንግስቱ የመደራጀት መብታቸው የተጠበቀላቸው ፓርቲዎችን አልከሰስንም።ፓርቲዎችን ግን ሽፋን አድርገዉ ስርዓቱን ወይንም ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለመናድ እንቀሳቀሳለን የሚሉ ኃይሎችን ግን ዛሬም ፣ ነገም ፣ ሕጉን የማስከበር ግዴታና ሃላፊነት ስላለብን ከመከሰስ አያመልጡም ማለት ነዉ።»

ኢቲቪ በቅርቡ በ«ሽብርተኝነት» ላይ፣ በቅርቡ ባቀረበዉ አሳዛኝ ዶኩሜንተሪ ላይ ፣ የፌደራል መንግስት አቃቤ ሕግ፣ አቶ ብርሃኑ ወንድማገኝ የተናገሩት ነበር።

እኝህ የሕግ ባለሞያ እየደጋገሙ ሕግን ስለማክበርና ስለ ሕገ መንግስቱ ነግረዉናል። ስለሕገ መንግስት ካነሳን አይቀር አንድ ነገር ጣል ላድርግ። የሕገ መንግስቱ አንቀጽ 29 ንኡስ አንቀጽ 4 «በመንግስት ገንዘብ የሚካሄድ ወይንም በመንግስት ቁጥጥር ሥር ያለ መገናኛ ብዙሃን የተለያዩ አስተያየቶችን ለማስተናገድ በሚያስችለው ሁኔታ እንዲመራ ይደረጋል» የሚል ድንጋጌ ያካትታል። ኢቲቪ በሕዝብ ገንዘብ የሚተዳደር እንደመሆኑ ይህ የሕገ መንግስት አንቀጽ ይመለከተዋል። ነገር ግን ኢቲቪ በቀጥታ፣ ሕግ መንግስቱን ሲንድ፣ ገለልተኛነት በጎደለው መልኩ የአንድ ድርጅትን የፖለቲክ ፕሮፖጋንዳ መጠቀሚያ ሲሆን ነው እያየን ያለነዉ። እነ አንዱዋለም አራጌ ላይ፣ ኢቲቪ የአንድ ወገንን አቋም የያዘ፣ የስም ማጥፋት ዘመቻ ሲያዥጎደጉድ፣ ቢያንስ ቢያንስ ጥቂት ሰኮንዶች፣ የአንዷለምን ጠበቃዎች፣ ወይንም ቤተሰብ፣ አሊያም የትግል አጋሮቹ የሆኑት የአንድነት አመራር አባላትን ለማነጋገር አልተሞከረም። እንግዲህ ከዚህ የምንረዳዉ፣ ሕግን በማክበር አኳያ፣ ሕወሃት/ኢሕአዴጎችና ኢቲቪ፣ አንድ ጣታቸዉን ወደሌሎች ሲጠቁሙ፣ አራቱ ጣቶቻቸው ወደ እነርሱ መዞራቸውን፣ ሕገ መንግስቱን እየጣሱ ያሉ እነርሱ መሆናቸውን ነዉ።

«አንዱዋለም አራጌን በተመለከተ፣ የግንቦት ሰባትን ተእልኮ ለማስፈጸም አገር ዉስጥ በሕቡእ (ስዉር) ይንቀሳቀሳል በሰላማዊ ትግል እንታገላለን የሚሉ የፓርቲዎችን ሽፋን አድርጎ ሲንቀሳቀስ የነበረ በመሆኑ በቂ ማስረጃ አቅርበናል» ሲሉ ነበር የፌደራል አቃቤ ሕጉ ለኢቲቪ አክለው የገለጹት። ምን አይነት መረጃ እንዳቀረቡ ግን አልነገሩንም። ለምን ቢባል ምንም ስለሌለ።

Monday, January 13, 2014

ኢህአዴግ ከምርጫ 2007 በሁዋላ ረብሻ ሊነሳ ይችላል አለ

ጥር ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ኢትዮጵያን ላለፉት 23 ዓመታት የገዛው ኢህአዴግ መጪውን ምርጫ ተከትሎ
በአዲስ አበባና በዋና ዋና የአገሪቱ ከተሞች ረብሻዎች ሊነሱ እንደሚችሉ ፓርቲው ድምዳሜ ላኢ መድረሱን አስታውቋል።
የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት በኢትዮጵያ መንግስት አሸባሪ ተብለው የተፈረጁት በተለይ ግንቦት7 እና ኦነግ ምርጫውን ተከትሎ በምርጫ 97 የታየውን አይነት የህዝብ አመጽ ለማስነሳት እየሰሩ ነው የሚል ድምዳሜ ላይ የደረሰው ኢህአዴግ፣ ከአሁኑ ጀምሮ በአንድ ለአምስት አደረጃጀትና የከተሞችን ነዋሪዎች ስለ አሸባሪዎች አላማ እና ግብ በማስረዳት ህዝቡ በአመጹ ተሳታፊ እንዳይሆን እንደሚያስተምር አስታውቋል።

Sunday, January 12, 2014

አቶ ሽፈራው ጃርሶ ባጋጠማቸው የመኪና አደጋ እስካሁን በህክምና ላይ ይገኛሉ ተባለ

(ዘ-ሐበሻ) በሚኒስትር ማዕረግ የስኳር ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሽፈራው ጃርሶ ከ2 ሳምንት በፊት ባጋጠማቸው ከባድ የመኪና አደጋ የተነሳ እስካሁን በህክምና ላይ እንደሚገኙ የውስጥ አዋቂ ምንጮች ገለጹ።


ከ2 ሳምንታት በፊት በደቡብ ኦሞ አካባቢ እየተገነባ የሚገኝን የስኳር ፕሮጀክትን ለመጎብኘት ጠ/ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ በርካታ የመንግስት ባለስልጣናት ወደ ዛው አምርተው እንደነበር የገለጹት ምንጮች በአቶ ሽፈራው ጃርሶ መኪና ላይ በደረሰ አደጋ ባለስልጣኑ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ለማወቅ ተችሏል።

አቶ ሽፈራው ላይ አደጋው የደረሰው በወላይታ አካባቢ እንደሆነ ያስታወቁት ምንጮቹ እንደ አደጋው አሰቃቂነት ሕይወታቸው መትረፉ በራሱ ትልቅ እድል ነው። በአካባቢው ሄሊኮፕተር ተልኮ ወዲያውኑ ወደ ጦር ሃይሎች ሆስፒታል እንደመጡና ህክምናቸውን በዛው እየተከታተሉ እንደሚገኙ ምንጮቹ ጠቅሰው ባለስልጣኑ እስካለፉት 2 ቀናት ድረስ በጦር ኃይሎች ሆስፒታል ህክምና ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። ካለፉት 2 ቀናት ወዲህ ያለውን የአቶ ሽፈራው ጃርሶን ሁኔታ ዘ-ሐበሻ ለማጣራት ሞክራ አልተሳካላትም።
ዘ-ሐበሻ ድረገጽ ላይ የሚከተለው ግጥም የዋልድባ የመታረስ ዜና የተዘገበ ሰሞን ወጥቶ ነበር። ግጥሙን ከትውስታ እዚህ አምጥተነዋል።

ስኳር ገዳም ገባ

እያንገራገረ ህዝቡ እያባባ
አበው እያዘኑ ወጣት እያነባ
እየተቃወሙ እየጮሁ እነ አባ
ዜናው በዓለም ዓቀፍ እየተስተጋባ
ድንገት ሳይታሰብ ስኳር ገዳም ገባ
ከፍ ከፍ ብሎ ለዚያውም ዋልድባ
ሲጠፋ ሲሰወር ሲደበቅ ቆይቶ
በአቋሙ ጠንክሮ በአቋሙ ጸንቶ
አመክሮ ሳይዝ ድንገት ገዳም ገብቶ
ጣፋጭ የነበረው ሊመር ነው ከቶ
ለሱ የሚስማማ ስንት ቦታ ሞልቶ
ስኳር እሳት ሆኖ ከገበያ ጠፍቶ
ሊቀመጥ ነው አሉ መቃብር ቤት ገብቶ
ምን ይውጥሽ ይሆን ከእንግዲህ መርካቶ
አባቶ ች ምን አሉ በዋልድባ ያሉ
በአባቶች አጽም ላይ ሸንኮራን ሲተክሉ
ከተቀበረበት እየፈነቀሉ
በደም የበቀለ ሸንኮራ ሊበሉ
በውሳኔ ጸንቶ
ኸረ እግዚኦ በሉ!
ይሄስ ጥሩ አይደለም
ከአቅም በላይ ሆኖ ህዝቡ ቢበደለም
አባቶች ዝም በሉ ይረሱት ግድ የለም
ዋልድባ በጾሙ ምነው ተፈተነ
በገዳሙ ልማድ ትንሽ ከታዘነ
ጸሎቱ እንደወጉ ከተከናወነ
ውሎ አድሮ ይሟሟል ስኳር ስለሆነ
4/3/12 voa radio
ከአዜብ ሮባ

ሰማያዊ ፓርቲ ሀሳቡን በኢሳት ላይ ለመግለጽ የማንንም ይሁንታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ

ታህሳስ ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ፓርቲው ” የምንናገርበትን የመገናኛ ብዙሃን ማንም እንዲመርጥልን ወይም እንዲወስንልን አንፈቅድም” በሚል ርእስ ባወጣው የአቋም መግለጫ፣ ” ሰማያዊ ፓርቲ መልዕክቱን የሚያስተላልፍበትን መገናኛ ብዙሃን ማንም አካል እንዲመርጥለት ወይም እንዲወስንለት የማይፈልግ መሆኑን ግልፅ ” አድርጓል።
“በሕገ መንግስቱ የተረጋገጠውን ማንም ሰው በመረጠው መንገድ ሃሳቡን የማስተላለፍ መብቱን በመጠቀም በኢሳትም ሆነ እድሉን ካገኘ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አቋሙንና እምነቱን ማስተላለፍ የሚቀጥል መሆኑን ማረጋገጥ ይወዳል” በማለት ፓርቲው በኢሳት ላይ ቀርቦ አቋሙን ከመግለጽ እንደማይገታ ግልጽ አድርጓል።
ሰማያዊ ፓርቲ ታህሳስ 25 ቀን 2006 ዓም በኢቲቪ የተላላፈውን ዶክመንታሪ ፊልም “የእብሪት መልዕክት” ያዘለና እና “ከተራ ርካሽ ፕሮፓጋንዳነት የማያልፍ የሕግና የዲሞክራሲያዊ መብት ገደብን ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ነው” ሲል አጣጥሎታል።
“የብሔራዊ ደህንነት መረጃ እና የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል  በተደጋጋሚ ጊዜ በሽብር ወንጀል ጠርጥሬአቸዋለሁ የሚላቸውን ሁሉ በመክሰስ ወደ እስር ቤት እንዲወርዱ እያደረገ ጉዳያቸው የፍርድ ቤት ውሳኔ ሳያገኝ እንደፈለገ በሚቆጣጠረው ወይም በሚያዘው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት አማካኝነት የፈለገውን ዓይነት ፍረጃና ሥም ማጥፋት ሲያካሒድባቸው” መቆየቱን ያስታወሰው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ይህ ራሱን ከሕግ በላይ የሰቀለ አካል ያለምንም ገደብ ከሚሰራቸው ተግባራት እንዲታቀብ በሕግ የሚያስቆመው በመጥፋቱ እስካሁን የፈፀማቸውን የማንአለብኝነት ተግባራት እንደጥፋት ሳይሆን እንደ መልካም ሥራ ቆጥሯቸው በተመሳሳይ የሥም ማጥፋትና የፍረጃ ተግባሩ እንዲገፋበት አድርጎታል” ብሎአል።
“ኢሳት” የተባለ የመገናኛ ብዙሃን በኢትዮጵያ መንግስት በሽብርተኝነት ከተፈረጀ ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ እንደተደረገለትና በሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች በተለይም ሰማያዊ ፓርቲ በዚህ የመገናኛ ብዙሃን እንዳይጠቀም የማስጠንቀቂያ ዛቻ ተላልፎለታል” ሲል ያስታወሰው ሰማያዊ ፓርቲ፣  ይህ አስፈራሪ አካል ራሱን ሕግ አውጭና ሕግ ተርጓሚ በማድረግ የዚህች ሐገር ዜጎች ሃሳባቸውን የሚገልጹበትንና የማይገልጹበትን የመገናኛ ብዙሃን እየወሰነላቸውና እየመረጠላቸው ይገኛል፣ ብሎአል ።
የገዥው ቡድን ሰዎች ሀሳብን በሃሳብ ማሸነፍ እንደማይችሉ ስለሚያውቁት የቀራቸው አማራጭ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ሃሳባቸውን የሚያሰራጩባቸውን መንገዶች መዝጋት ብቻ መሆኑን ፓርቲያችን ይገነዘባል ያለው ሰማያዊ ፓርቲ፣  ማንም አካል በሕግም ሆነ በሞራል ተጠያቂ የሚሆነው የሚያስተላልፈው መልዕክት ይዘት የሌሎችን ዲሞክራሲያዊና ሞራላዊ መብት የሚጋፋ መሆን አለመሆኑ እንጂ ገዥው ቡድን በጠላው ወይም በወደደው የመገናኛ ብዙሃን መልዕክቱን ማስተላለፉ አይደለም” ሲል አቋሙን ግልጽ አድርጓል፡፡ መልዕክትን የገዥው ቡድን ሰዎች በጠሉት የመገናኛ ብዙሃን ማስተላለፍ በራሱ ወንጀለኛ ወይም ሽብርተኛ ለማድረግ የሚያበቃ ምንም ዓይነት የሕግ መሰረት እንደሌለውም ገልጿል፡፡
ፓርቲው በመጨረሻም ” ሰማያዊ ፓርቲ መልዕክቱን የሚያስተላልፍበትን መገናኛ ብዙሃን ማንም አካል እንዲመርጥለት ወይም በዚሁ አጋጣሚም የፓርቲያችንን መልካም ስም በሃሰት ለማጉደፍ የተሰነዘሩ ቃላትን በቀላሉ የማንመለከታቸው መሆኑን ሕግ ባለበት ሐገር ራስን ከሕግ በላይ በማስቀመጥ ማንንም አካል መፈረጅና ስም ማጉደፍ በሕግ የሚያስጠይቅ መሆኑን የዘጋቢ ፊልሙ ባለቤቶች እንዲያውቁትና ወደፊትም ተመሳሳይ ድርጊት ከመፈፀም እንዲቆጠቡ እናሳስባለን፡፡” ብሎአል።
በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱት ሰማያዊ ፓርቲ እና አንድነት ፓርቲ በኢሳት ላይ ቀርበው አቋማቸውን እንዳይገልጹ መንግስት ሰሞኑን ምክር አዘል ማስጠንቀቂያና ማስፈራሪያ በኢቲቪ አማካኝነት መስጠቱ ይታወሳል።
ከመጪው ምርጫ ጋር ተያይዞ ኢሳት ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ፕሮግራሞቻቸውንና መልእክቶቻቸውን በነጻ እና ያለገደብ የሚያስተላልፉበትን አሰራር በመቀየስ ላይ ነው።

የቀደምቶቹን ወንጀል ለማጋለጥ መቃብር ሲምስ የኖረው ወያኔ በራሱ ጦር ካምፕ ውስጥ የተገኘውን አስከሬን መደበቅ ለምን አሰፈለገው?

አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ፈረንሳይ ለጋሲዮን በሚገኘው የክብርዘበኛ ጦር ካምፕ ውስጥ ማንነታቸው ያልታወቁ የ6 ዜጎች አስከሬን ለመንገድ ሥራ በተሠማሩ ቆፋሪዎች አማካኝነት መገኘቱ የሰሞኑ አሳዛኝ ዜና ነው።

አንድ አይነት ቀለም ባላቸው ብርድ ልብሶች ተጠቅልለው ከተገኙ 6 አስከሬኖች የመጀመሪያዎቹ ሁለት ሰለባዎች ታስረውበት የነበረው የእጅ ሰንሰለታቸው እንኳ እንዳልወለቀና ከተቀሩት የአንዱ እጆች ደግሞ የፍጥኝ ወደ ኋላ እንደታሰሩ መገኘታችው ግድያው በቅርብ እንደተፈፀም አንዱ አስረጂ ነው።

በእንዲህ አይነት ጭካኔ የተገደሉ ዜጎች አስከሬን መገኘት በመንግሥት ተብየው አካል ካለመገለጹም በላይ ግቢውን በማስተዳደር ላይ የሚገኘው 3ኛ ክፈለ ጦርም ሆነ በግብር ከፋይ ገንዘብ የሚተዳደሩ መገናኛ ብዙሃን እስከዛሬ አንድም ቃል መተንፈስ አለመፈለጋቸው ጉዳዩን እጅግ የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን የሚያስገርምም አድርጎታል። ይባስ ተብሎም በመንገድ ሥራ ቁፋሮው የበለጠ አስከሬን ሊወጣ ይችላል በሚል ስጋት አካባቢው በፖሊስ እንዲታጠር ከተደረገ በኋላ ሥራውም እንዲቋረጥ ተደርጓል።

Saturday, January 4, 2014

የማይመስል ነገር ለሚስትህ አትንገር! ኢቲቪ ስለ ኢሳት

January 4, 2014
ቢታኒያ አለማየሁ፣ አዲስ አበባ

ዶክመንታሪ ብሎ ዝም! አስቡት እስኪ ኢሃዲግን በሚያክል አፋኝ መንግስት በኢቲቪ ኢሳት ሲብጠለጠል፣’ኢሳት ማለት የኢትዮጵያ ህይዝብ እውነተኛ የመረጃ ወፍጮ ነው!’Ethiopian Satellite Television (ESAT)

ለምን ግን በዚህ ሰአት ስለ ኢሳት ዶክመንታሪ መስራት አስፈለገ?

-ኢሳት ከተመሰረተ አንስቶ እስካሁን ድረስ በእውነተኛ መረጃ ምንጭነት በመላው የኢትዮጵያ አንጀት ውስጥ ተደላድሎ
መቀመጡን ስልሚያውቁ!

-ይከስማል ይጠፋል አቅሙ ይዳከማል ሲሉት እንደ ወይን ጠጅ ከለት እለት እየበሰለና እየጎመራ መምጣቱን ስላዩ!

-በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙ ተምልካቾች ለኢሳት በመደወል በሚሰጡት አስተያየት ህዝቡ በሚገባ እየተከታተለው መሆኑን ስላረጋገጡ!

-ከዚህ ቀደም ከሰባት ጊዜ በላይ ጃም በማደርግ እና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ኢሳት ወደ ኢትዮጵያ የሚያደርገውን ስርጭት ቢያቛርጡም ኢሳት ግን የተለያዩ የሳተላይት አማራጮችን በመጠቀም ከአንድ አመት በላይ(እስካሁን) ያለ ምንም ችግር ወደ ኢትዮጵያ ማሰራጨ ስለቻለና አሁን ካለው የኢኮኖሚ ሁኔታ አንጻር ጃም ማድረግ ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቅ!

-ህዝብን አደንቁሮ በኢቲቪ ፕሮፓጋንዳ ብቻ የህዝብን አምሮ ለማደደብ በሚደርገው ጥረት ኢሳት ነጻ ሃሳብ በማነሸራሸር እንቅፋት ስለሆነ!
ባጠቃላይ ኢሳት ለህዝብ እውነትን በመግለጽ ለስረአቱ የእግር እሳት መሆኑ ስለታመነበት:- የኢሳትን ይዘት ተንትኖ እና እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ ኢሳት ግን እንዲህ ይላል በሚል አመክኖዋዊ አስተሳሰብ ከመሞገት ይልቅ፣ ግንቦት ሰባት አሸባሪነው ኢሳት ደግሞ የግንቦት ሰባት ነው ስለዚህ ኢሳት አሸባሪ ነው ብለው ከደመደሙ በኋላ ህዝቡ አሳትን መከታተል እንደ ሽብርትኛነት አድርጎ ቆጥሮት መከታተሉን እንዲያቆም ለማግባባት ቀጥሎም ለማስገደድ ያመች ዘንድ የተሰራ ድራማ ነው! የዘፈን ዳር ዳሩ እስክሳ ነው ትል ነበር አያቴ! የሚገርመው ግን አቶ ሃይለማሪያም እንዳሉት “ግንቦት ሰባት በቅዠትላይ የተመሰረተ ድርጅት” ከሆነ ይህን ያክል ተከታታይ ድራማዎች በመስራት ምን አደከማቸው? በራሱ ጊዜ ከእንቅሉ ይባንንላቸው የለም እንዴ?

እናንት አሸባሪ ኢሳቶች ሆይ ህዝብን እልል እያስባላችሁ አንባገነኖችን እያሸበራችሁ ነውና በርቱ! በርቱ! በርቱ!

ቢታኒያ አለማየሁ

Friday, January 3, 2014

ቴዲ አፍሮና የቢራው ፖለቲካ

በጋዜጠኛ ስህተት የወጣች አንዲት ጽሁፍ ምክንያት 18 ሺህ ፊርማ በኢንተርኔት መሰበሰቡን ሰማን። ጽሁፉን ያሳተመው መጽሄት ስህተቱን አረመ። ይቅርታም ጠየቀ። ዘመቻው ግን እንደቀጠለ ነው። ቴዲ አፍሮ ይንን እንዳልተናገረ መግለጫ ቢሰጥም ጉዳዩ እልባት ሊያገኝ አልቻለም። ከቶውንም አንድነታችንን የማይፈልጉ ምእራባውያን ጭምር ይህችን ምክንያት በመያዝ ጉዳዩን ማረገብ ጀመሩ። አንድ የዳች ጋዜጣ አጼ ምኒሊክን ከሂትለር ጋር አመሳስሎ በመጻፍ ጋዜጣውን በዚህ ሳምንት አሰራጭቷል! ያለ አንዳች መረጃ። “ለነጮች እጄን አልሰጥም!” ብሎ አድዋ ላይ ስላዋረዳቸው ምኒሊክን ለማንቋሸሽ ምንም መረጃ አያስፈልጋቸውም።

እልፍነሽ ቀኖ የተባለች የኦሮምኛ ሙዚቃ አቀንቃኝ በአንድ ወቅት በለቀቀችው ነጠላ ዜማ ምክንያት ማእከላዊ እስር ቤት ታስራ ነበር። ምርመራውን የሚያካሂዱት ሰዎች በመጀመርያ የዘፈኑ ግጥም ወደ አማርኛ እንዲተረጎም አደረጉ። በግጥሙ ምንም አይነት የወንጀል ነገር ሲያጡ ግጥሙ “የህግ ትርጉም ይደረግለት” ሲሉ አዘዙ። የህግ ትርጉሙም ብዙ ስላላስኬዳቸው ለግጥሙ የፖለቲካ ትርጉም እንዲሰጠው አደረጉና ሙዚቀኛዋን “ጥፋተኛ ነሽ” ሲሉ ከሰሱ።  የፖለቲካ ትርጉሙ “ይህን ያለችው እንዲህ ለማለት ነው…”  ከማለት ተነስቶ አቀንቃኝዋ በልቧ አስባው ይሆናል የሚለውንም ያካተተ ነበር። በኢትዮጵያ “የፍትህ ሰዎች” የምናስበውንም ያውቁ ኖሯል።

የበደሌ ቢራ አድማ ጠሪዎች ቴዲ አፍሮ በልቡ ያሰበውን የማንበብ ሃይል እንዳላቸው አናውቅም። እሱ ግን የተባለውን ነገር እንዳልተናገረ ገልጾላቸዋል።

አጼ ምኒሊክ ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ ያከሄዱት ጦርነት “ቅዱስ ጦርነት ነው” ወይንም “አይደለም” የሚለውን ሙግት ለግዜው ወደጎን እንተወው። ምክንያቱም የዚህ ውይይት ውጤጥ የኦሮሞ ህዝብ አሁን ላለበት ችግር የሚፈይደው አንዳች ነገር የለም። የህሊና አይኖቹን ክፍት አድርጎ ለሚመለከት ሁሉ፤ የዛሬው የኦሮሞ ህዝብ ችግር የበዴሌ ቢራን ከመጠጣት እና ካለመጠጣት የላቀ ነው። ለነገሩ እንጂ 90 በመቶ የሚሆነው የኦሮሞ ህዝብ የሚተዳደረው በግብርና፤ ኑሮውም ከእጅ ወደ አፍ በመሆኑ የበደሌ ቢራን የመጠጣት አቅሙም ሆነ እድሉ የለውም። የዚህ ዘመቻ መሪ ተዋንያን የሆነው ጃዋር መሃመድ እንደነገረን ከሆነ ደግሞ 90 በመቶው የኦሮሞ ህዝብ የሙስሊም እምነት ተከታይ ነው። በሙስሊም አልኮል “ሃራም” ነው።

“እስር ቤቱ ሁሉ ኦሮምኛን ይናገራል!” ያለው ማን ነበር? አዎ! የስርዓቱ ቁንጮ የነበረው ስዬ አብርሃ ነው። ስዬ ስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት ከርቸሌ ታስረን የነበርን ጋዜጠኞች የእነ ኦቦ ባይራን ጉዳይ እያነሳን በኦነግ ስም በግፍ ለታሰሩት ስንጮህ የዝሆን ጆሮ ነበር የሰጠን።  አቶ ስዬ አብርሃ አይኑ የተከፈተውና ጆሮው ኦሮምኛን መስማት የጀመረው እጆቹ  የኋሊት ታስረው ቃሊቲ ሲወርድ ነበር። በእርግጥ ማየት ማመን ነው። ያየውንና የሰማውን በመመስከሩ ሊመሰገን ይገባዋል። ልብ በሉ። እስረኛው ሳይሆን እስር ቤቱ ነው ኦሮምኛ እየተናገረ ያለው።

ሂዩማን ራይትስ ዋች ሰሞኑን በለቀቀው ዘገባ፤ በኦሮሞ ወገናችን ላይ እየተፈጸመ ያለውን አስከፊ ስቃይ በድምጽና በምስል ጭምር አሰራጭቷል። ይህንን ስቃይ ለማስቆም የፌስቡክ ታጋዮቹ ስንት ሺህ ፊርማ እንዳሰባሰቡ አልነገሩንም። የበዴሌ ቢራን የኦሮሞ ህዝብ እንዳይጠጣ በ24 ሰዓታት ውስጥ 18 ሺ ፊርማ ተሰብስቧል ብለውናል።

እርግጥ ነው። “ሰብአዊ መብት ይከበር!” የሚል ዘመቻ ከመጀመር ይልቅ “ቢራ አትጠጡ!” ማለቱ ቀላል ሊሆን ይችላል።  በምእራቡ አለም የሚመረተውን ሄነከን ቢራ ራሳቸው እየተጎነጩ  ይህንን ቀጭን ትእዛዝ ሲያስተላልፉ ግን በዚያ ትልቅ ህዝብ ላይ እያሾፉበት መሆኑን የዘነጉት ይመስላል።

የኦሮሞ ልሂቃን ግራ ያጋቡኛል። ይህን ስል ያለምክንያት አይደለም።  በአባ ጅፋር ግዛት ተወልጄ በኦሮሞ ባህል ታንጼ ነው ያደግኩት።  በደሙ ብቻ ‘ኦሮሞ ነኝ’  እያለ ከሚመጻደቀው ይልቅ የኦሮሞን ህዝብ ማንነት ጠንቅቄ አውቀዋለሁ። ቋንቋው፣ ባህሉና ስነልቦናው ውስጡ ሰርጎ ሳይገባ በደሙ ብቻ ራሱን እየለካ ከህልም እና ከቅዠት አለም ውስጥ ገብቶ የኋሊት ከሚራመደው በተሻለ መንገድ።  …    እናም አንድ የኦሮሞ ህዝብ አውቃለሁ።  በቋንቋው፣ በባህሉና በታሪኩ የሚኮራ ህዝብ።  ታታሪና ሰራተኛ ህዝብ።  ከሌላው ጋር ተዋልዶና ተከባብሮ በፍቅር አብሮ የሚኖር ህዝብ።   የኦሮሞ ህዝብ  ከሌላው ወገኑ ጋር በደም ተሳስሯል። ሃቁ ይህ ነው። ግና ፖለቲከኞቹ ከዚህ ህዝብ በሁለት ሺህ ማይልስ ርቀው በምእራቡ አለም በሚሰሩት ስራ ይህንን ትልቅ ህዝብ እጅግ ትንሽ የሚያደርግ መሆኑን ያስተዋሉት አይመስለኝም።

በቅርቡ ሳውዲ አረቢያ በወገኖቻችን ላይ የጸመችውን ግፍ ለመቃወም በአለም ዙርያ ያለ ኢትዮጵያዊ በጋራ በሚጮህበት ወቅት አንድ እንግዳ ክስተት በኢንተርኔት ላይ ወጥቶ አየን። “ሳውዲ አረቢያ ኦሮሞን አትግደሉ፣ ኦሮሞ ኢትዮጵያዊ አይደለም፣ ኦሮሞ ወንጀለኛ አይደለም።” የሚል መፈክር የሚያሰሙ ሰዎች ለብቻቸው ሰልፍ ወጡ። እነዚህ ሰዎች የተሰለፉት “ኦሮሞን አትንኩ። ሌሎቹ ግን ወንጀለኞች ስለሆኑ ይገባቸዋል” የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ነበር።  መቼም ከማንም ሰብአዊ ፍጡር እንዲህ አይነት ኢ-ሰብአዊ አባባል አይጠበቅም። ድርጊታቸው ያሳፍራል። አንገትም ያስደፋል። ይህ አሳፋሪ ድርጊት እኔን እንዲህ ካሸማቀቀኝ፤  አፈር ስንፈጭ ያደግነው በኢትዮጵያዊነታቸው የሚኮሮ የኦሮሞ ልጆች ቢያዩት ምን ሊሉ እንደሚችሉ በምናቤ እስል ነበር።  በዚያ ትልቅ ሕዝብ ስም አደባባይ ወጥተው፣ ተግባራቸው ግን ማስተዋል የተሳነው ትንሽ ህዝብ ነበር።  ያንን ኩሩ ህዝብ እንዲህ … እንዲህ እያሉ ሊያሳንሱት አየን።

እ.ኤ.አ. በ1998 ገደማ አቶ ዳዊት ዮሃንስ በሆላንድ ውስጥ ህዝባዊ ስብሰባ ጠርቶ ነበር። ከስብሰባው መሃል አንድ ሰው ከመቅጽበት ተነስቶ ‘ለኦቦ ነጋሶ ጊዳዳ የሚያደርሱልኝ ጥብቅ መልእክት አለኝ’ አለ። ስብሰባውን የሚመራው አቶ ዳዊት ዮሃንስም ሰውዬው ተነስቶ መልእክቱን እንዲናገር ፈቀደለት። ሰውየው ከመቀመጫው ተበሳ።

“ፊንፊኔ መሃል ላይ ያለው የምኒሊክ ሃውልት በአስቸኳይ እንዲነሳ ይንገሩልን!” አለ ፊቱን ቅጭም አድርጎ በኩራት እየተናገረ።  በስብሰባው የነበርን ሰዎች ግን ለተናጋሪው አፈርን። ያሳፈረን ይህንን መልእክት ማስተላለፉ አልነበረም። ሰውየው ሊናገር ከመቀመጫው ሲነሳ ሌላ አንገብጋቢ ጉዳይ ያነሳል ብለን ገምተን ስለነበር እንጂ።  ‘ሰዎች በዘራቸው (በኦሮሞንታቸው) ብቻ የሚታሰሩት፣ የሚሰቃዩትና የሚገደሉት እስከመቼ ነው?’ የሚል መልእክት ነበር የጠበቅነው። ምክንያቱም ወቅቱ በቁጥር 20 ሺህ የሚደርስ የኦሮሞ ተወላጆች የጦር ካምፕ እስረኛ እንዲሆን ካደረጉ በኋላ፤ የኦነግ መሪዎች በባሌ ሳይሆን በቦሌ እየተሸኙ የወጡበት ሰሞን ነበር።  የኦነግ መሪዎች ከህወሃት ጋር በጋራ መስርተውት የነበረውን ቻርተር ረግጠው በመውጣታቸው ምክንያት ኦሮሞው ወገናችን የህይወት መስዋእትነት ጭምር ይከፍል የነበረበት ወቅት።

ዳዊት ዮሃንስም አግባብ ያለው ጥያቄ መሆኑን ከተናገረ በኋላ መልእክቱን ለርእሰ-ብሄሩ እንደሚያደርስ ቃል ገብቶ ሄደ።  መልእክቱን ለዶ/ር ነጋሶ ያድርስ፤ አያድርስ የታወቀ ነገር የለም። ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በዚያን ወቅት የሃገሪቱ ርዕሰ-ብሄር ነበሩ። እንኳንና የተባለውን መልእክት ሊያስፈጽሙ፤  እሳቸውም የዛ ስርዓት ሰለባ ሆነው አየን።

የአጼውን ሃውልት ግን ዛሬ በባቡር ሃዲድ ስራ ምክንያት ከነበረበት ስፍራ እንዲነሳ አድርገውታል።

የተዛባ ታሪክ ይዘን፣  ጥላቻን ብቻ በምናባችን አርግዘን የት እንደምንደርስ አላውቅም። አሁንም በመፍትሄው ላይ ሳይሆን በችግሮቹ ላይ ተወጥረናል።  የምኒሊክ ሃውልት ተነሳም አልተነሳ እንደ እንስሳ ለሚታደነው የኦሮሞ ህዝብ ምን ፋይዳ አለው?  “በእስር ያሉ ወገኖቼ ይፈቱ!” ለማለት እንኳን ሞራል ሳይኖረን አእምሯችንን በአፈ-ታሪክ ብቻ ወጥረን አንዲት ኢንች እንኳን ወደፊት መራመድ እንዳልቻልን ለምን አናስተውልም?

አጼ ምኒሊክ ኢትዮጵያን ግዛት አንድነት ለማስፋፋት ባደረጉት ጦርነት ወንጀል ፈጽመው ከሆነ አጽማቸው ወጥቶ ለፍርድ ይቅረብ ነው የምትሉት?  ወይንስ ይህ ትውልድ የዚያ ወንጀል ውርስ አለበት? ውርስ ካለበትስ ማን ነው ወራሹ? አማራው? ጉራጌው ወይንስ ኦሮሞው?  እንደ ዘረኞች፣ ደም መለካት ካለብን እኚህ መሪ ከአማራም፣ ከኦሮሞም፣ ከጉራጌም ይወለዳሉ። ጠለቅ ብለን ከሄድን ደግሞ ራስ ጎበና ዳጬን በዚያ ስእል ውስጥ እናያለን። ምእራብ እና ደቡብ ኢትዮጵያን በሃይል የያዙና ያስገበሩ የአጼው የጦር መሪ። ራስ ጎበናን ልንጠላቸው እንችል ይሆናል። ኦሮሞነታቸውን ግን ልንክደው አንችልም።   የወንጀል ውርስ በተዋረድ (guilt by association)  ውስጥ ከገባን የኦሮሞን ህዝብም በአእምሯችን ለፈጠርነው ወንጀል ወራሽ ልናደርገው ነው።

የቴዲ አፍሮ “ጥቁር ሰው” አልበም  የሚያሞግሰው ኢትዮጵያን ከወራሪ ጠላት የታደጉትን ጀግኖች ነው። እነ ፊታውራሪ ሃብተጎርጊስ ዲነግዴን እና እነ ባልቻ አባ ነፍሶ። ቴዲ አፍሮ ለነዚህ ጀግኖች ባያቀነቅንላቸውም ከታሪክ መዝገብ ላይ ልንፍቃቸው አንችልም። የታሪክ ተመራማሪዎች ስለነዚህ ጀግኖች የጻፉት አፈ-ታሪክ ወይንም ድርሰት አይደለም። በጀግኖቹ የምንኮራው በዘራቸው ሳይሆን የሰሩት ገድል ነው። በ’ጥቁሩ ሰው’ የተመራው ይህ የጸረ-ቅኝ ግዛት ገድል ከኢትዮጵያ አልፎ ለመላው አፍሪካና ለጥቁር ህዝቦች ነጻነት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። ይህ ሊዋጥላችሁ የሚገባ እውነታ ነው። በዚያ ገድል የሚያፍሩ ካሉ የራሳቸው ጉዳይ። መላው የአፍሪካ ህዝብ ግን ይኮራበታል። የአለም ጥቁር ህዝብም ሲያስታውሳቸው ይኖራል።

ዘር እየቆጠርን ከሄድን ብዙ የሚጎረብጡ ነገሮችን ልናነሳ ነው። በግዛት ማስፋፋቱ ሂደት ግን አንድ ሃቅ አለ።  ኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ህልቀ መሳፍርት ኢትዮጵያዊ አልቋል። ይህ ደግሞ የድንበር መስፋፋት፤ እድገት እና ስልጣኔ ይዞት የሚመጣው ችግር እንጂ አንድን ህዝብ ለመጨረስ ጥናት ተደርጎ የተሰራ እንዳልሆነ ታሪኩን ከስር መሰረቱ ማየቱ ይበጃል። ችግሩ በእኛ ላይ ብቻ ሳይሆን በአያሌ ሃገሮች እንደተከሰተ የታሪክ መዛግብት ይነግሩናል። በ17ኛው ክፍለዘመን የተከሰተው የኢንዱስትሪ አብዮት ሳብያ እንኳን ከሁለተኛው የአለም ጦርነት የማይተናነስ እልቂት ነበር።

አጼ ምኒሊክን ከጀርመኑ ኦቶ ቮን ቢስማርክ ጋር የሚያመሳስሉ ምሁራንም አሉ። እርግጥ ነው ጀርመን  አሁን የያዘችውን ግዛት ቅርጽ እንድትይዝ ያደረገው ፕሩሲያዊው ቢስማርክ ነው። ቢስማርክ የጀርመንን አንድ ታላቅ ኤምፓየር ለመፍጠር አንባገነን፣ ሃይለኛና ጦረኛ መሆን ነበረበት። ታዲያ ይህችን ሃያል ሃገር በመመስረቱ ጀርመኖች አልጠሉትም። ይልቁንም የጀግንነት ስያሜ ለግሰውታል። አያሌ የመታሰቢያ ሃውልቶችንም አቁመውለታል።

ቢስማርክ የህግ ምሁር ነበር። አጼ ምኒሊክ ግን መደበኛም ሆነ ዘመናዊ ትምህርት የተማሩ ሰው አልነበሩም። ከታሪክ እንደምንረዳው በአጼ ልብነድንግል ዘመነ መንግስት፤ የግራኝ አህመድ ወረራን ተከትሎ የነበረውን መከፋፈልና መተላለቅ ለማስቆም መሪዎች ተነሱ።  ሃገርን አንድ የማድረጉን ትግል አጼ ዮሃንስ ጀመሩት፣ አጼ ቴዎድሮስ ቀጠሉበት ከዚያም እምዬ ምኒሊክ ተረከቡት።

አጼ ምኒሊክ ለአመታት በኦነግ ሰዎች ተወግዘዋል። ውግዘቱ አሁንም እታገልለታለው የሚሉትን ህዝብ ችግር ሲፈታው አለየንም። በ1991 ከህወሃት ጋር ጋብቻ ፈጽመው የምኒሊክ ቤተ-መንግስት ሲገቡ ይናገሩት የነበረውን ሁሉ ረሱት። ከቶውንም ያነሱት የነበረው የኦሮሞ ህዝብ የመብት ጉዳይ ሳይሆን የስልጣን ጥያቄ ለመሆኑን አረጋገጡልን።  የሽግግር መንግስቱን ቻርተር ሲያጸድቁ “ኢትዮጵያዊ አይደለንም” የሚለውንም ሳያውቁ ዘንግተውት ነበር። ከገዢው ፓርቲ ጋር የጀመሩት ግዚያዊ ጋብቻ በፍቺ ሲጠናቅቅ የምኒሊክ ጠላትነት መፈክራቸውን እንደገና አነሱት።

የዘር ፖለቲካው ስካር ሞቅ ብሎ በነበረበት በዚያን ወቅት እንደቀልድ ይነገር የነበረ አንድ ቁም ነገር አለ። አንድ የምግብ ቤት በር ላይ በላቲን ፊደል “አማራ መግባት ክልክል ነው!” የሚል ጽሁፍ ሰፍሯል። የጽሁፉ ትርጉም ያልገባው አንድ የአማራ ተወላጅ ጎራ ብሎ ምግብ አዘዘ። አስተናጋጆቹ የሰውየው ድፍረት አስደነገጣቸው። ባለስልጣን ስለመሰላቸው አስተናገደዱት። ዳግም እንዳይመለስም እጥፍ ዋጋ አስከፈሉት። ሰውየው በድጋሚ ሲመጣ ሶስት እጥፍ አስከፈሉት። በሌላ ግዜ ከአምስት ጓደኞቹ ጋር መጥቶ ምግብ አዘዘ። ከተስተናገደ በኋላም አራት እጥፍ ቢል አቀረቡለት።  በዚህ ግዜ ቲፕም ጨምሮ ሰጣቸው።  የሆቴሉ ባለቤት በነጋታው “አማራ መግባት ክልክል ነው!” የሚለውን ጽሁፍ አንስቶ “ኦሮሞ መግባት ክልክል ነው!” በሚል ቀየረው።

በአሁኑ ዘመን ከበድ አለ እንጂ፣ ሰዎችን በጎሳ አደራጅቶ ከማሳደም የቀለለ ትግል የለም። ደም ከውሃ ይወፍራል እንዲሉ፤ ሰዎች በጋራ የሚጋሩትን ነገር እያነሱ ስነልቦናዊ ዘመቻ ማድረግ ስኬት ሊኖረው ይችላል። ዘለቄታ ግን አይኖረውም። የዘር ፖለቲካ ልክ እንደ ስካር ነው። ይሞቃል ከዚያም ይበርዳል። በርግጥ በሞቅታ ግዜ የሚፈጠረው አደጋ ቀላል ላይሆን ይችላል። እ.ኤ.አ. በ1993 በምስራቅና በምእራብ ኢትዮጵያ የተፈጸመው አሰቃቂ ወንጀል ለዚህ ዋቢ ነው። የኦነግ ልሂቃን የ19ኛውን ክፍለ ዘመን ጉዳይ እየደጋገሙ ያነሱልናል።  በ21ኛው ክፍለ ዘመን በራሳቸው እጅ የተፈጸመው ግድያ ግን በብሄራዊ ቴሌቭዥን ጭምር እንድናየው ተደርጓል።  ነብሰ-ጡር ሴቶች በጩቤ ሆዳቸውን እየተሰነጠቁ ሲገደሉ አየን። ነብስ ያላወቁ ሕጻናትና የ90 አመት አዛውንት ጭምር ከተራራ ላይ እየተወረወሩ ሲጣሉም የአይን ምስክሮች ነን። እነዚህ ሰዎች የምናስታውሰው ይህን በመሰለ ወንጀል ብቻ አይደለም። ድርጊቱ የቂምና የቁርሾ አሻራ ጥሎ አልፏል።

ይህ ሁሉ በደል በዘመናችን ተፈጸመ። በዳዮቹ ግን አሁንም በቀልን አርግዘው ይጓዛሉ።

የበደሌ ቢራን አለመጠጣት የኦሮሞን ችግር የሚፈታ ከሆነ፤ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ቢራውን መጠጣት ያቁም። የአኖሌን ሃውልት መሰራት ለኦሮሞ ህዝብ ፍትህ የሚያመጣ ከሆነ ደግሞ፤ ሃውልቱ በየከተማው ይገንባ። ግና ይህ ሃውልት ለመጭው ትውልድ ጥሎት የሚያልፈው ቂምና በቀልን እንጂ፤  ለሚታገሉለት ህዝብ የፍትህ ጥያቄ ዋስትናው ምን እንደሆነ ልንረዳው አልቻልንም።  አሁን ያለው ትውልድ ያልፋል። ከዚህ ትውልድ በኋላ ለሚወለዱት ልጆች ጥለንላቸው የምናልፈው ቅርስ ጥላቻ፣ ቂም እና በቀል ብቻ ይሆናል።

ከዘመናችን ታላቅ ሰው ከኔልሰን ማንዴላ አንድ ነገር እንማር። ማንዴላ የደቡብ አፍሪካን ብቻ ሳይሆን የአለምን ፖለቲካ የለወጠ የፖለቲካ ነብይ ነው። ይህንን ሲያደርግ የፖለቲካ ፎርሙላ አልነበረውም። ክፉን ነገር በበጎ ለማሸነፍ ወሰነ። ጥላቻን በፍቅር ለወጠ። ልክ እንደ ክርስቶስ፣ የበደሉትን ሁሉ ይቅር ብሎ በፍቅር አሸነፋቸው። ታሪክ ሰርቶ አለፈ። ስሙም ከመቃብር በላይ ለዘልአለሙ ይኖራል።