Monday, September 29, 2014

ህወሃቶች “አቅም ግንባታ” የሚሉት፤ እኛ ደግሞ “አቅም አድክም” የምንለው ሂደት

ህወሃት የመምህራንን፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችንና የመንግስት ሠራተኞችን ”አቅም እገነባለው” ብሎ ተነስቷል። ለዚህ “አቅም ግንባታ” እያሉ ለሚጠሩት አሰለቺ እና አደንቋሪ አቅም አድክም ፕሮፖጋንዳ እየወጣ ያለው ወጪ ለሌላ ተግባር ውሎ ቢሆን ኑሮ የተሻለ ይሆን ነበር። የተሻለ ነገር በህወሃቶች መንደር ይሠራል ብሎ መጠበቅ ግን ሞኝነት ነው። ህወሃት የተፈጠረው አገርን ለማፍረሰና ህዝብን ለማስጨነቅ እንጂ የተሻለ ሥራ ሠርቶ ህዝብን ለማስደስት አይደለም።

ህወሃቶች በአፍቅሮተ ንዋይ አብደው አቅላቸውን የሳቱ፤ ለእውቀትና ከእነርሱ በተሻለ ደረጃ ለሚያውቅ ቅንጣትም ታክል ክብር የሌላቸው፤ ውሸት የመኖሪያቸው ድንኳን ሁኖ ለብዙ ዘመን ያኖራቸው ቡድኖች ናቸው። በዚህ ሁኔታ ራሳቸውን የገነቡ ቡድኖች የሌሎችን አቅም እንገነባለን ብለው የመነሳታቸው ነገር አገራችን የገባችበትን የውርደት አዘቀት ፍንትው አድርጎ የሚያሳየን ነው።

የንዋይ ፍቅር የክፋቶች ሁሉ መሠረት ነው። ህወሃቶች በዚህ በክፋት ሁሉ መሠረት በሆነው በንዋይ ፍቅር ያበዱ በመሆናቸው ህወሃቶችን ከክፋት፤ ክፋትን ደግሞ ከህወሃት ለይቶ ለማየት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። እነዚህ ቡድኖች በአፍቅሮተ ነዋይ አብደው ለእብደታቸውም መድሃኒት ጠፍቶ እኛ ከሌለን አገሪቷን እንበትናታለን በሚል ቅዥት ውስጥ እንደሚኖሩም የታወቀ ነው። ህወሃቶች ገንዘብ ሊያሰገኝ የሚችለውን ማንኛውንም ዓይነት ወንጀል ለመፈፀም የሚያቅማሙ አይደሉም። ህዝቡን በሙሉ በገንዘብ የሚገዛ ቢያገኙ ህዝቡን በሙሉ ለመሸጥ ወደ ኋላ ይላሉ ብሎ ማሰብም አይቻልም። ይህን በመሰለ የሞራል ውደቀት ውስጥ የሚገኙ ህወሃቶች የህዝቡን አቅም እንገነባለን ሲሉ ትንሽም አለማፈራቸው አገራችን ከደረሰችባቸው የሞራል ውደቀቶች መካከል አንዱ ሁኖ ሊጠቀስ የሚችል ዓቢይ ጉዳይ ነው።

ህወሃቶች ለእውቀትና ከእነርሱ በተሻለ ደረጃ ማሰብ ለሚችል ሰው ያላቸው ጥላቻ ወደር የለውም። ለዚህም ነው ከእነርሱ መካከል ይሄ ነው ተብሎ ሊጠቀስ የሚችል የተመሰገን የተማረ ሰው የማይገኘው። ለህወሃቶች የተማረ ማለት ሲጠሩት አቤት ሲልኩት ወዴት እያለ ለሆዱ ያደረ እንጂ ለአገሬ፤ ለህዝቤ፤ ለወገኔ ምን በጎ ተግባር ልፈፀም የሚል አስተሳሰብ ያለው ሰው አይደለም። የህወሃቶች ዋነኛው ችግር የተማረ ሰው መጥላታቸው ብቻ ሳይሆን ሁሉንም እኛ እናውቃለን ማለታቸውም ጭምር ነው።ሁሉን እኔ አውቃለሁ ማለት ደግሞ የድንቁርና ታላቅ ምልክት ነው። ከዚህ ድንቁርና ራሱን ማላቀቅ ያልቻለ ቡድን የዜጎችን አቅም እገነባለው ብሎ መነሳቱ ከአስገራሚ በላይ ሁኖብናል።

ውሸት ጥሩ ነገር እንዳልሆነ ከህወሃቶች በቀር ሌላው ሁሉ የሚስማማበት ነገር ነው። ህወሃቶች ግን ውሸትን እንደ ታላቅ የትግል ስትራቴጂ ይቆጥሩታል።ህወሃቶች በግለሰብ ደረጃ ሳይሆን በአገር ደረጃ ሲዋሹ ቅንጣት ታክል እፍረት አይሰማቸውም። እንዲያውም ውሸታቸውን እውነት እንደሆነ አድርገው ያምናሉ። ለምሳሌ ኢኮኖሚው ከ11% በላይ አድጓል ይላሉ። ይሄ አሃዝ እውነት እንዳልሆነ ይታወቃል። ህወሃቶችና የሰበሰቧቸው ኮተታም ካድሬዎች ይሄን ውሸት እውነት ነው ብለው ያምናሉ። በአጠቃላይ ህወሃቶች ስለራሳቸውም ሆነ ስለሚገዙት ህዝብ እውነቱን መናገር ሞኝነት ነው የሚል ፅኑ ዕምነት አላቸው። ይሄን ከመሰለ ፅኑ ደዌ ራሳቸውን ማላቀቅ ያልቻሉ ደካሞች የሌላውን አቅም እንገነባለን ሲሉ አለማፈራቸው ያሳፍራል።

የሰሞኑ አቅም ግንባታ ብለው የሚጠሩት ግርግር ዓላማው እና ግቡ በተሻለ ደረጃ ማሰብ የሚችሉ ዜጎች ልዩ ልዩ አማራጮችን ማየት አቁመው አካሄዳቸውን በሞራልም ሆነ በእውቀት ውዳቂ ከሆነው ከህወሃት ጋር እንዲያደርጉ ለማድረግ ነው። ብዙ ኮተታም ካድሬዎቻቸው ለራሳቸው እንኳ የማይገባቸውን አብዮታዊ ድሞክራሲ የሚባለውን ፍልስፍና አዘረክርከው ይዘው በተማሪዎችና በመምህራን ፊት ያለምንም ዕፍረት ተጎልተው እየዋሉ ነው። እነዚህ ቡድኖች ከእነርሱ በተሻለ ደረጃ የሚያስብውን ኃይል መፍራት ብቻ ሳይሆን ሥር የሠደደ ጥላቻም አላቸው። በዚህ በሚፈሩትና በሚጠሉት ዜጋ መሃል ተገኝተው ለሚጠየቁት ጥያቄ መልስ መስጠት ሲገባቸው ማስፈራራት ዛቻ እና ስድብን የመልሳቸው ማሳረጊያ አድርገውታል።

በመሠረቱ አቅም ግንባታ ሲባል ዜጎች ራሳቸውንም ሆነ አገራቸውን ወደ ተሻለ ደረጃ ሊያደርሱ የሚችሉበትን ሁኔታ በራሳቸው ማመቻቸት የሚችሉበትን አስተሳሰብ እንዲያሳድጉ የሚያስችል ነው። አቅም የሚገነባው የዜጎችን የመጠየቅ እና የመመራመር ችሎታ አዳብሮ የተሻለ አማራጭ እንዲያፈልቁ እንጂ መንግስት የሚለውን ብቻ አምነው እንዲቀበሉ ለማድረግ አልነበረም። የህወሃቶች አቅም ግንባታ ግን ዜጎች ማሰብ አቁመው መጠየቅንም ፈርተው ምንሊክ ቤተ-መግስት ውስጥ ከተተከሉት ዛፎች እንደ አንዱ ሁነው እንዲኖሩ ለማድረግ ነው። እነዚያ ዛፎች መጥረቢያውን ሥሎ ሊገነድሳቸው ለሚያንዥብበው ዛፍ ቆራጭ ገንድሶ እሰከሚጥላቸው ድረስ ጥላ ይሆኑታል። ያ መጥረቢያውን ስሎ የተከለላቸው ሰው ጠላታቸው መሆኑን የማወቅ አቅም ግን የላቸውም። የህወሃቶች የአቅም ግንባታ ግቡ ዜጎች እንደ ዛፉ እንዳያስቡ እና ጠላትን ከወዳጅ የሚለዩበትን አቅም ማዳከም ነው።

ህወሃቶች ከ11% በላይ አድገናል ይላሉ። እደገቱ እውነት ከሆነ ለምን እንራባለን? ለምንስ ዜጎች ስደትን ይመርጣሉ? ለምንስ የጨው፤ የሳሙና፤ የስኳር፤ የቲማቲም እና የሽንኩርት ዋጋ የማይቀመስ ሆነ? ብሎ የሚጠይቅ ዜጋ ጠፍቶ፤ የውሸቱን የ11% እድገት ተቀብሎ የሚኖር ዜጋ የመፍጠር ብርቱ ቅዥት አላቸው።በዚህ ቅዥት ውስጥ እንዳይኖሩ የሚያጋድቸው የለም፤ ውሸታቸውንም አምኖ መኖር የእነርሱ ችግር ነው። የእነርሱ ውሸት አምኖ መኖር አገር የሚያፍረሰው እና ዜጎችን የሚያሰጨንቀው የእኛን ውሸት እመኑ ብለው ወደ ማስገደድ ደረጃ ሲደርሱ ነው። አሁንም እያደረጉ ያሉት ይሄንኑ ነው። የመንግስት ሠራተኞች፤ መምህራንና ተማሪዎች ተገደው የህወሃቶችንን ውሸት እየተጋቱት ይገኛሉ። ኢትዮጵያዊያን ህወሃቶችን ማመን ካቆሙ ብዙ ዘመን ተቆጥሯል። ህወሃቶች በእንግሊዘኛው “ፓቶሎጂካል ላየርስ” ተብለው የታወቁ ናቸው። ይሄ ደግሞ በሽታ ነው። የህወሃቶች ውሽት ወደ በሽታ የተሸጋገረ ስለሆነ በማንኛውም መድረክና ሁኔታ የሚናገሩትን ማመን አይቻልም።ለምሳሌ የአዜብን ስታይል እንመልከት በስልክ ከጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና ጋር ስትነጋገር መጀመሪያ “አዎን እኔ አዜብ ነኝ” አለች ከአንድ ደቂቃ በኋላ ተመልሳ ደግሞ “አይ እኔ አዜብ አይደለሁም“ አለች። ይሄ እንግዲህ ውሸት ወደ በሽታ ተሸጋግሮባቸው የመኖሪያቸው ድንኳን መሆኑን ያሰየናል። እንግዲህ ዜጎች የህወሃቶችን ውሸት አንሰማም፤የእናንተንም አቅም ግንባታ አንፈልግም ማለት የሚችሉበት አገር የላቸውም። ዜጎች ይሄን እሰማለሁ፤ ያንን ደግሞ መስማት አልፈልግም የሚባል መብታቸው በህወሃቶች ተገፏል። ይህ የዜጎችን የመምረጥ መብት የገፈፈ ገዥ ቡድን እያደረገ ያለው የዜጎችን አቅም ማዳከም እንጂ የዜጎችን አቅም መገንባት አይደለም።አቅም በግዴታ አይገነባምና።

ህወሃቶች የሙስና ምንጮች መሆናቸው የታወቀ ነው።ከህወሃት መንደር ከሌብነት የፀዳ ባለስልጣን አይገኝም።ሁሉም ሌቦች፤ ሁሉም ሥነ-ምግባር የጎደላቸው ሰው ምን ይለኛልን የማያውቁ ናቸው። እነዚህ ቡድኖች የሚፈፅሙትን ሙስና ማስቆም አገሪቷ ከገጠሟት ፈተናዎች መካከል አንዱ ቢሆንም መቆም ይኖርበታል። ይሄን ሙስና የማስቆም ኃላፊነት ከህወሃቶች እና ከኮተታም ካደሬዎቻቸው ውጪ ያሉ ዜጎችን ሁሉ ትብብር የሚጠይቅ ነው። በዚህ ረገድ መምህራኑና ተማሪዎች ለህወሃቶች ያነሷቸው ጥያቄዎች ተጠናክረው መቀጠል ይኖርባቸዋል። ህወሃቶች በሙስና መጨማለቃቸውን ከሌቦቹ ህወሃቶች በቀር ሁሉም ያውቃል። ህወሃቶች ከእንቅልፋቸው ሲነቁ በሚሊዮን የሚቆጠር ሃብት በእጃቸው ሲገባ የትግሌ ውጤት ይላሉ እንጂ ሰርቄ ነው የሚል አስተሳሰብ በአእምሯቸው ዝር አይልም። የህወሃቶች ትልቁ ችግር የሚፈፅሙትን ዝሪፊያ ሁሉ የትግላችን ውጤት ነው ይገባናል ብለው ከልባቸው ማመናቸው ነው። በዚህ ዓይነት አስተሳሰብ የተቃኘ ቡድን የዜጎችን አቅም ለመገንባት በሚል እያካሄደ ያለው አደንቋሪ ስልጠና ተብየው የዜጎችን አቅም ያዳክም እንደሆነ እንጂ በምንም መሠፍረት የማንንም አቅም አይገነባም።

እነዚህ ቡድኖች ያለ ምንም ዕፍረት ሙስናን እንታገላለን ይላሉ። በሙስና የተጨማለቁ ባላስልጣናት ሙስናን እንዋጋለን ብለው በድፍረት ሲናገሩም ይደመጣል።በሙስና የተዘፈቁ ባላስልጣናት መኖራቸው እየታወቀ ለምን ህግ ፊት አይቀርቡም ተብለው ሲጠየቁ መልስ የላቸውም። ኢታማዦር ሹሙ ሳሞራ የኑስ ዋና ሌባ መሆኑ ይታወቃል፤ በዘረፈው የህዝብ ሃብት የባንክ ቤት ባለድርሻ እሰከመሆን ደርሷል። መላኩ ፈንቴን እንዲታሠር የበየነው ህግ ሳሞራ የኑስን አይነካም። ሁሉም ኢትዮጵያዊ በህግ ፊት እኩል ነው ቢባልም ሳሞራ የኑስና መላኩ ፈንቴን እኩል የሚያይ ህግ በኢትዮጵያ የለም። በዚህ ዓይነት የሞራል ዝቅጠት ውስጥ የሚገኝ ቡድን የሚገነባው አቅም ምንድ ነው? ዜጎችን በምን አቅጣጫ ወደየት ለመውሰድ ያለመ ስልጠና ነው እየተሰጠ ያለው ተብሎ ቢጠየቅም የሚገኘው መልስ ዜጎች ሁሉ እንደ ህወሃት በጎጥ አስተሳሰብ ተተብትበው፤ ሰው ምን ይለኛል ማለትን ረስተው፤ እግዚአብሄርን መፍራት ትተው፤ ግራና ቀኝ ማየትን አቁመው ከአንድ ማሰብ ከማይችል እንስሳ ሳይለዩ እንዲኖሩ ማድረግ ነው።

የግንቦት ሰባት የፍትህ፤ የነፃነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ ህወሃት የተባለውን ዘረኛና ዘራፊ ቡድን ከተቆናጠጠበት የሥልጣን ኮርቻ ላይ አውርዶ አገሪቷን የሁሉም ለማድረግ የሚችለውን እያደረገ ነው። ለኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከህወሃት የበለጠ ጠላት የለም። ህወሃት ዋነኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት መሆኑ ሊሠመርበት የሚገባ ነጥብ ነው። ይሄን ጠላት ሳያቅማሙ በሁሉም መስክ መታገል ግዜው የሚጠይቀው ከዜጎች የሚጠበቅ ተግባር ነው።

ተከብሬ የምኖርበት አገር ያስፈልገኛል የሚል ሁሉ ንቅናቄያችንን እንዲቀላቀል ዛሬም ደግመን የትግል ጥሪያችንን እናቀርባለን። እኛ አገር ያሳጡንን ቡድኖች በሚገባቸው ቋንቋን ለማነጋገር ሳንቅማማ የትግሉን ባቡር ተሳፍረናል። የትግሉን ባቡር አሁኑኑ ተሳፈሩና ለሁላችንም የትሆን አገር እንፍጠር።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

Tuesday, September 9, 2014

ወጣቱን ለማደንቆር ያለመው ስልጠና ህወሓትን ለመቅበሪያነት ይዋል

ህወሓት፣ ከሶስት መቶ ሺህ በላይ የመንግሥት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን በየቦታው ሰብስቦ እያሰለጠነ ነው። ይህ ሲያልቅ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ስልጠና ይቀጥላል ተብሏል። በድምሩ ወደ ግማሽ ሚሊዮን የሚጠጋ ወጣት አንድ አይነት ሰነድ አንብቦ ለ2007 ትምህርት ይዘጋጃል ማለት ነው። ስልጠናው ወደ መንግሥት ሠራተኞችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎችም ይስፋፋል ተብሎ ይገመታል።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በዚህ ሥልጠና ላይ ያለውን እይታ በነሐሴ 16 ቀን 2006 ዓም ቁጥር 328 ርዕሰ አንቀጹ መግለጹ ይታወሳል። ግንቦት 7 የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በወያኔ ስልጠናዎች ላይ ተቃውሞ ለማሰማት መድፈራቸው ወጣቱ ለለውጥ የተዘጋጀ እንደሆነ አመላካች መሆኑን ተገንዝቦ ይህ የለውጥ ፍላጎት በድርጅት እንዲታገዝ ወጣቱ በትናንሽ ሕዋሶች ራሱን እንዲያደራጅ መክሯል። ሆኖም ግን ህወሓት ለስልጠናው የሰጠው ትኩረት ቀድሞ ከታሰበው በላይ በመሆኑ ንቅናቄዓችን በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ እንደገና ሊመለስበት ወስኗል።

ህወሓት፣ ይህንን ያህል መጠነ ሰፊ ስልጠና ማድረግ ለምን አስፈለገው? የዲሞክራሲ ኃይሎችስ ይህንን ስልጠና እንዴት ለራሳቸው ጥቅም ሊያውሉት ይችላሉ?

ህወሓት ይህንን ትርጉም የለሽ ስልጠና በአሁኑ ሰዓት ለመስጠት የፈለገበትን በርካታ ምክንያቶች ማቅረብ ቢቻልም የሚከተሉት ሁለቱ ግን ዋነኛዎቹ ናቸው ብለን እናምናለን።

አንደኛውና ዋነኛው ምክንያት ህወሓት የተከታዮች ድርቅ የደረሰበት መሆኑ አድርባይ መሪዎቹን ማሳሰቡ ነው። በሚሊዮን ይቆጠራሉ የሚባሉት የኢህአዴግ አባላት ልባቸው ከህወሓት ጋር አለመሆኑ ግልጽ እየሆነ መጥቷል። በተለይ ደግሞ በተላላኪዎቹ ብአዴን፣ ኦህዴድ እና ደህዴግ የተሰባሰቡ አባላት በግልጽ ህወሓትን መቃወም እየጀመሩ ነው። ህወሓት የራሱን መጥፊያ እያደራጀ መሆኑ የተሰማው በመሆኑ አዳዲስ “ምዕመናንን” ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አካባቢ መመልመል ይፈልጋል። የመንግሥት ንብረትና መዋቅር ለፓርቲ ስልጠና የሚጠቀም በመሆኑ ከብዛት የሚገኝ ትንሽም ቢሆን ጥቅም የሚያገኝ ከሆነ የወጭው ጉዳይ ህወሓትን አያሳስበውም። ስለሆነም ይህ ስልጠና በተቻለ መጠን ብዛት ያላቸዉን የተማተሩ ወጣቶች በአድርባይነት ለህወሓት ማሰለፍን አላማዉ አድርጎ የተነሳ ስልጠና ነዉ።

ሁለተኛው አቢይ ምክንያት ደግሞ ህወሓት ለኢትዮጵያ ወጣት ለማስተላለፍ የፈለገው መልዕክት ወደ እያንዳንዱ የዩኒቨርስቲ ተማሪ ጆሮ መድረሱን ማረጋገጥ መፈለጉ ነው። መልዕክቱም “ሜዳ ውስጥ ያለሁት ተጫዋች እኔ ብቻ ነኝ። ለሚቀጥሉት አርባና አምሳ ዓመታትም እኔን የሚገዳደረኝ አይኖርም፤ ስለሆነም የኢትዮጵያ ወጣት ሆይ ለለውጥ ያለህ ተስፋ ከንቱ ነው። አርፈህ ቁጭ ብለህ ተገዛ” የሚል መልክት ነው።

ስልጠናዎቹ ከላይ የተጠቀሱትን ሁለት ዓላማዎችን በሚገባ ማስፈፀም ይችላሉ ብሎ መገመት ከባድ ነው። የስልጠናው ይዘት እጅግ የወረደ እና የሰልጣኞቹን ብስለት ግንዛቤ ውስጥ ያላስገባ መሆኑ ስልጠናውን ምፀት የበዛበት አድርጎታል፤ አሰልጣኞቹንም ትዝብት ውስጥ ጥሏቸዋል። የስልጠናዎቹ ጽሁፎች (ማንዋሎች) ይዘት ደግሞ የአዘጋጆቹ የእውቀት ማነስ ምን ያህል አሳሳቢ ደረጃ ላይ ያለ መሆኑ ለተማሪዎቹ ተጨባጭ ማስረጃዎች ሆነውላቸዋል። በአጠቃላይ ስልጠናው ለአሰልጣኝ ካድሬዎች ያልተዘጋጁበት ፈተና ደቅኖባቸዋል። የኢትዮጵያ ወጣት ሲሞሉት የሚሞላ ባዶ ጋን አለመሆኑን እያዩት ነው። ወጣቶች ጠጣር ጥያቄዎችን ያነሱባቸዋል፤ አሰልጣኖች እነዚህ ጥያቄዎች እንዴት መመለስ እንዳለባቸው ስለማያውቁ ይደናበራሉ። መልስ ሲጠፋ ቁጣ፣ ዛቻና ማስፈራሪያ ይከተላል።

ይህም ሆኖ እነዚህ ስልጠናዎች ለህወሓት ምንም ውጤት አያስገኙም ብሎ ማለፍ አይቻልም። የስልጠናዎቹ ውጤት የሚወሰነው ግን የኢትዮጵያ ወጣት ከህወሓት ውጭ ለሚመጣ መረጃ ባለው ቅርበት መጠን ነው። ሁሉም የመረጃ ምንጮች ተዘግተውበት የህወሓትን የእድገትና የሰላም መዝሙር ሲሰማ ለኖረ ሰው በስልጠናው የሚሰጡ ባዶ ፕሮፖጋንዳዎችን የመቃወሚያ ምክንያት አይኖረውም። ለተለያዩ የመረጃ ምንጮች ቅርበት ያለው ወጣት ግን የህወሓት መዝሙር ከግራዚያኒ የእድገትና የሰላም መዝሙር የተለየ አለመሆኑን ይረዳል። በፋሺስት ወረራ ወቅት ግራዚያኒም ኢትዮጵያን በመንገድና በህንፃ እየገነባሁ ነው፤ በጥቂት ዓመታት ውስጥ አውሮፓ የደረሰችበት ደረጃ ላይ አደርሳታለሁ ይል እንደነበር ይታወሳል።

የህወሓትን ኢትዮጵያን ለአርባና አምሳ ዓመታት የመግዛት እቅድን ወጣቱ ምክንያታዊ ነው ብሎ ይቀበላል? የራሱን አፋኝ ህጎች አክብረው እየተፍጨረጨሩ ያሉ ተቀናቃኖቹን እንኳን በእንጭጩ እየደፈጠጠ ያለ ሥርዓት “ኃላፊነት የሚሸከም አጣሁ” የሚለው ሰበቡ በወጣቱ ዘንድ ምን ያህል ተቀባይነት ይኖረዋል? በግንቦት 7 እምነት ይኸኛው የስልጠና ዓላማ ሊሳካ የሚችለው በዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ድክመት ብቻ ነው። ዘረኛውንና ዘራፊውን ወያኔ መጣል ብቻ ሳይሆን ከወያኔ በኋላ ፍትህ፣ እኩልነትና ብልጽግና የሚሰፍኑበትን ስትራቴጄ ያዘጋጀና ለስትራቴጂዉ ክንዉንራሱን ያዘጋጀ ድርጅት መኖሩን የኢትዮጵያ ወጣት ማወቅ ይኖርበታል። ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ከሌሎች ዲሞክራሲያዊ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ኢትዮጵያን ወደ ነፃነት፣ እኩልነትና ብልጽግና ጎዳና ለማስገባት እየታገለ መሆኑን ሁሉም ወጣት ሊገነዘብ ይገባል። ይህ ግንዛቤ ካለ የኢትዮጵያ ወጣት ለእብርተኛው፣ ዘረኛው፣ ሙሰኛውና ከፋፋዩ ህወሓት ተገዢ አይሆንም።

በስልት ከተጠቀምንበት ህወሓት ብዙ ሚሊዮኖች የሕዝብ ገንዘብ አውጥቶበት ያዘጋጀው ስልጠና ለራሱ ከሚሰጠው ጥቅም በላይ ለዲሞክራሲያዊ ኃይሎች የሚሰጠው ጠቀሜታ ይበልጣል። ለምሳሌ፣ ግንቦት 7 እነዚህን ስልጠናዎች የኢትዮጵያን ወጣት ለትግል ያላቸውን ዝግጁነት ለመገምገም ተጠቅሞበታል። “የኢትዮጵያ ወጣት ለትግል ዝግጁ ነው – የቀረው ድርጅት ነው” ሲል የግምገማውን ውጤት አሳውቋል። በዚህም ርዕሰ አንቀጽ ይህንኑ መልዕክት ማስረጽ ይፈልጋል።

በአምባገነን ሥርዓቶች ውስጥ የሚኖሩ ዲሞክራሲያዊ ድርጅቶች ከተለመዱ አደረጃጀቾች መለየት አለባቸው። መደበኛ (Formal) አደረጃጀቶች አባላትን ለአደጋ ያጋልጣሉ። በዚህም ምክንያት ነው ግንቦት 7፣ ኢ-መደበኛ (Non Formal) አደረጃጀቶች የሚመርጠው። በእኛ ሁኔታ “ኢ-መደበኛ አደረጃጀት” ስንል አራት ይሁን አምስት የሚተማመኑ ወጣቶች የሚፈጥሩት የግንቦት 7 ሴል ነው። ይህንን ሴል የፈለጉትን ስም ሊሰጡት ይችላሉ – እድር፣ ክበብ፣ የሆነ ስፓርት ቡድን ደጋፊ የተመቻቸውን ስያሜ ይስጡት። የተቋቋመበት ዓላማ ግን ግልጽ ነው – ለፍትህና ለነፃነት የሚደረገውን ትግል ማገዝ ነው። ይህ ኢ-መደበኛ ስብስብ ራሱን የግንቦት 7 አካል አድርጎ ይቁጠር። የግንቦት 7 ፕሮግራሞችንና ጽሁፎችን ያንብብ። ስብስቡ ለመረጃዎች ራሱን ቅርብ ያድርግ። መረጃዎችን ይለዋወጥ። በሂደት ቀጣዩ መንገድ ግልጽ እየሆነለት ይመጣል።

እየተካሄደ ያለው የህወሓት የጅምላ ስልጠና ለኢ-መደበኛ ድርጅቶች መስፋፋት ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል። የግንቦት 7 አባላትና ደጋፊዎች እነዚህን ስልጠናዎች የግንቦት 7 ሴሎችን ለማደራጀት እንዲጠቀሙበት እንመክራለን። ግንቦት 7 በኢትዮጵያ ወጣት የፈጠራ ችሎታ ላይ እምነት አለው። የኢትዮጵያ ወጣት አደንቁሮ ሊቀብረው የመጣውን ስልጠና ህወሓትን ለመቅበሪያነት እንደሚጠቀምበት የግንቦት 7 እምነት ነው።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!