Saturday, March 7, 2015

ሕወሓትን ለማስወገድ ሁላችንም እንረባረብ!!

በዳዊት ዮሃንስ

የዘመናት ሥልጣኔ ባለቤትና የአፍሪካ የነፃነት ፋና ወጊ የነበረችው አገራችን ኢትዮጵያ ዛሬ በህወሓት መዳፍ ሥር ወድቃ ሕዝቦቿ የመከራና የሰቆቃን እንጀራን በሚጋግሩበት በአሁኑ ወቅት ጥቂት የአገዛዙ ሹማምንት “ጊዜ የሰጠው ቅል …” እንዲሉ በጥጋብና በትዕቢት ተወጥረው አሸሸ ገዳሜ ይላሉ፡፡ ነገን በተስፋ መሰነቅ ያቃታቸው አያሌ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ግን አገር እያላቸው አገር አልባ ሆነው አለምን ባነጋገረ ሁኔታ ራሳቸውን ለብርቱ ስቃይና ለሞት አሳልፈው እየሰጡ በየማዕዘናቱ እየተሰደዱ በከፋ ሰቆቃ ውስጥ እያለፉ እነሆ 24 የመከራ አመታት ነጎዱ። ስደቱ ከዕለት እለት እጅግ አሳሳቢ በሆነ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱ በእርግጥም ይህች አገር የማን ናት? ያሰኛል፡፡ 

የዳቦ ቅርጫት እየተባለች ስትሞካሽ የኖረችው ኢትዮጵያ የሚላስ የሚቀመስ ጠፋቶ ሕዝቦቿ አንጀታቸው እየተጣበቀ አደባባይ ወጥተው ብሶታቸውን እንዳያስተጋቡ አንደበታቸው እየታፈነ፣ የሕወሓት ሹመኞች እንደልባቸው በሚቦርቁበት አሻንጉሊት ፓርላማ ሕዝብን የሚያሸማቅቁና ዜጎችን እግር ተወርች የሚጠፍሩ ሕጎች እየተፈበረኩ ሲተገበሩ፣ ሕዝቡ ከድህነት ጋር ታግሎ ያፈራውን አንጡራ ሃብቱን በጠረራ ፀሐይ ሲቀማና ሲዘረፍ የአገዛዙ ሹማምንትና ሆድ አደር ባለሃብቶች ለቀጣይ ሦስትና አራት ትውልድ የሚተርፍን የአገር ሀብት በየአቅጣጫው እየዘረፉና እየተቀራመቱ አገሪቱን በድቅድቁ አጨልመዋታል። 

ታሪክ እንደሚዘክረው ቀደምት አባቶቻችን ጣሊያን አገራችንን ሊነጥቅና በባርነት ሊገዛን በዘመናዊ ጦር ሲወረን አገር የለንም ብለው አልተሰደዱም፡፡ የሕይወት መስዋዕትነትን ከፍለውና የጠላትን ጦር ድባቅ በመምታት አንበርክከው ኢትዮጵያን የራሳቸው አደርገው ለኛ አስረክበውን አልፈዋል፡፡ ዛሬ ግን በመካከላችን የወጡ ዘረቢስ ፋሽስቶች አገር እንደሌላው ባይተዋር ወይም አንደ ፀጉረ ልውጥ ቆጠረውን ሲሳለቁብንና ሲያጎሳቁሉን ዝም ብለን የመመልከታችን ነገር ሁሌም ለእኔ እንቅልሽ ነው። ወገን ምንድን ነው ዝምታው! ከአባቶቻችን የወረስነው እኮ ባርነትን አይደለም ይልቁኑ ጀግንነትን አልገዛም ባይነትን እንጂ። ስለዚህ ዛሬ ዘረ ቢስ የሕወሓት ፋሽስቶቹን እምቢኝ አሻፈረኝ ብለን በፅናት ልንታገላቸው መነሳት በሁላችንም ጫንቃ ላይ የወደቀ ግዴታ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ 

በርግጥ አሁን ላይ የሕወሓትን የግፍ አገዛዝ ለማስወገድ ዜጋው ሁሉ እምቢኝ አልገዛም እያለ በሁሉም አቅጣጫ ሁሉንም የትግል አይነት ያልጀመረው ለመጀመር የጀመረው ለመቀጠል እየተሟሟቀ የሚገኝበት ወቅት ላይ እንገኛለን። ይህ ደግሞ መልካም አጋጣሚ ነው። ስለዚህ ሁላችንም በተረባረበ ክንድ በአንድነት ሁሉንም ጸረ ሕወሓት ሃይላት የማበረታቻ ቃል ብቻ ከመስጠት በዘለለ አቅማችን የፈቀደውን ሁሉ ለመለገስ በያለንበት ዝግጁ መሆን ይገባናል። ዛሬ በሃገር ቤት ያሉ ተቃዋሚዎች፣ የመብት ጠያቂዎች፣ የድምጻችን ይሰማ ሚሊዮን ሙስሊሞች ሌሎችም የበደሉ ግፍ ያረፋባቸው አያሌ ዜጎች በሙሉ እያስገመገሙት ያለው ህዝባዊ እምቢተኝነት፤ በሌላው ፈርጅ ደግሞ ነፍሰ በላውን የሕወሓት አገዛዝ በብረት ለመፋለም ቆርጠው ቤታቸውን በዱር በገደል ያደረጉ የነጻነት ታጋዮች በሙሉ በየፈርጃቸው በማበረታታትና በመደገፍ ለአገር አድኑ ህዝባዊ ትግል ጋሻ ሆነን መቀጠል ይኖርብናል።

በነገራችን ላይ የሕወሓት ነፍሰ ገዳይ ሹማምንት ፈጣሪን እየተገዳደሩ ኢትዮጵያን በእጃቸው በመጠፍጠፍ ሰርተው በገፀ በረከትነት የሰጡን ይመስል ነጋ ጠባ ለጆሮ የሚገለማ ዲስኩራቸውንና ውሸታቸውን እያንቧረቁ አደንቁረው ለመግዛት ሌት ተቀን የሚዶሉቱትን ሴራ በቃ በማለት ነቅተን ማክሸፍም የሁላችንም ግዴት መሆን ይገባዋል እላለሁ። ጆሮ ሰጥተን ልንሰማቸው ፈጽሞ አይገባም። ሕወሓቶች የሥልጣን ኮርቻው ላይ ጉብ ባሉ ማግስት በዘር በመገነጣጠል የከፋፈሉን፤ ከጐንደርና ከጋምቤላ ለም መሬቶችን ቆርሰው ለሱዳን በገፀ በረከትነት የሰጡ፤ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ድሃ ገበሬዎችን እያፈናቀሉ መሬቶቻቸውን በመንጠቅ ለውጭ አገር ቱጃሮች በማይረባ ገንዘብ የሸጡ፤ የአገር ሃብትን ጨምሮ በእርዳታና በብድር የተገኘ ገንዘብ ዘርፈውና አዘርፈው ከአገር ያስወጡ የጥፋት መልእክተኞች ናቸው።

ስለዚህ በመጨረሻ በድጋሚ አትኩሮት ሰጥቸ ማስተላልፈው የምፈልገው መልዕክት ቢኖር ሕወሓት ያፈረሳትን አገር፤ ሕወሓት የዘረፈውን የአገርና የሕዝብ ሐብት፤ ሕወሓት የበተነውን ሕዘብ ፤ ሕወሓት ያረከሳቸውን ቤተ እምነቶች፤ ሕወሓት ያነገሰውን ሕግ አልባነት ግድያ አፈና ሺብር ስደትና የግዞት ስርዓት ለማስወገድ መተኪያ የሌላትን ውድ ሕይወታቸውን በመገበር በዚህ ወቅት በየትኛውም የፍልሚያ ጎራ ተሰልፈው የሕወሓትን እብሪት ለማስተንፈስና ለኢትዮጵያዊያን ነፃነት፤ አንድነት፤ ለጋራ እድገት፤ ፍቅርና ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ነፃነት ያለመስዋእትነት አይገኝምና የታሪክና የትውልድ አደራቸውን አንግበው ከሕዝባቸው ጎን ሆነው ግዳጃቸውን በመወጣት ላይ ከሚገኙት ከአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ እንዲሁም ከሌሎች የአንድነት ሃይሎች ጎን በመሰለፍ የተጀመረውን እልህ አስጨራሽ የአገር አድን ትግል ከዳር ለማድረስ መረባረብ ያለብን ሰአት አሁን ስል አጥብቂየ ወገናዊ ጥሪየን አቀርባለሁ። ይንን የተቀደሰ አገርና ሕዝብን የማዳን ተግባር ለዲሰፖራው ወገን እግዚአብሔር ቅን ልቦና ስጥቶት በአንድነት የነፃነት ሃይሎችን እንዲቀላቀል ጥሪየን እያቀረብኩ ፈፃሚው እሱ ነውና ለሐያሉ ጌታም የነፃነታችንንና የትንሳኤያችንን ቀን እንዲያቀርብልን ልመናየን በማቅረብ ፅሁፌን እቋጫለሁ።

ድል ለጭቁኑ የኢትዮጵያ ህዝብ!



No comments:

Post a Comment