Tuesday, February 17, 2015

ተመስገን ደሳለኝ ምልክታችን ነው! – ከበድሉ ዋቅጅራ

ተመስገን ደሳለኝ ምልክታችን ነው፤ ልንሸፍነው ያልቻልነው ምልክት፡፡ ተመስገን የተከሰሰውና የተፈረደበት ከአሸባሪዎች ጋር ግንኙነት አለው ወይም ደግሞ አሸባሪ ነው ተብሎ አይደለም፤ የተከሰሰውም የሶስት አመት እስር የተፈረደበትም በጻፈው ጽሁፍ ነው፡፡ በመሆኑም ተመስገን ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ ህገመንግስታዊ መብታችን ያለመከበር ምልክት ነው፡፡ ተመስገን ጠንካራ ግለሰባዊ ሰብእናውንና ህገመንግስታዊ መብቱን በመጠቀም፣ ለዚህች ሀገርና ለህዝቦቿ ይበጃል ያለውን ሀሳብ ለመግለገልጽና በሰላማዊ መንገድ ለመሟገት አፍላ የወጣትነት እድሜው ያላጓጓው ዜጋ ነው፡፡ በመሆኑም ተመስገን የ‹መሬት ላራሹንና የብሄረሰቦችን መብት ጥያቄ አንግበው በነሳት ላመኑበት እንደታገሉት አይነት ወጣቶች ዛሬም ለመኖራቸው ምልክት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ተመስገን የዘመን ተሻጋሪው ኢትዮጵዊ አስተሳሰባችንና ስብእናችን አጋላጭ ምልክት ነው፡፡ በዘመነ ፊውዳሊዝም ለተገኘው ለውጥ (ትሩፋቱ በጎም ይሁን ክፉ) መስዋእትነት የከፈሉት ጥቂቶች ናቸው፡፡ በደርግ አብዮታዊ አገዛዝ ዘመንም የታሰሩት፣ ተገድለው የተጣሉት፣ ለትግል የወየኑት፣ የተሰደዱት ጥቂቶች ናቸው፡፡ አሁንም ከዚሁ የተለየ አይደለም፤ ስለህዝባችንና ሀገራችን፣ ስለፖለቲካዊው አስተዳደራችን ያገባናል ብለው በድፍረት መንግስትን የሚሞግቱት ጥቂቶች ናቸው፡፡ በሶስቱም ዘመን በአጋጣሚው ተጠቅመው ሀገራዊና ህዝባዊ ጥቅምን፣ በአንድ እንጀራ አፉን ለሚዘጋ ወስፋታቸው ጩኸትና በቃኝ ለማያውቅ ፍትወተ-ንዋይ ማርኪያ የተጠቀሙበት በርካቶች ናቸው፡፡ አብዛኛው ህዝብ ግን በገዢዎቹ የጭካኔ ድንኳን ውስጥ በፍርሀት ተደቅድቆ ‹‹በአያገባኝም›› እንዳላዘነ አለ፡፡ ይህ ህዝብ ስለልጁ መረሸን አልጠየቀም፤ አላለቀሰም፡፡ በገዢዎቹ የሚጣሉበትን አዋጆች ይቆጥራል እንጂ፣ በአዋጆቹ ስለሚያጣው መብቱ ወይም ስለሚያጎናጽፉት ትሩፋት አይጠይቅም፡፡ ይህ ህዝብ እያጨበጨበ የሚፈጥራቸውን ተሟጋቾቹን (ጀግኖቹን) እራሱን እየነቀነቀ ወደ እስር ቤት፣እያለቀሰ ወደ ቀብር ከመሸኘት በቀር ‹‹ለምን?›› ብሎ አይጠይቅም፡፡ በመሆኑም ተመስገንና ሌሎች ሀሳባቸውን በሰላማዊ መንገድ ሲገልጹ፣ ለእስርና ለስደት የተዳረጉ ዜጎች፣ የዚህ ከዘመን ጋር እየሰለጠነና እየዳበረ የመጣ ጸያፍ ኢትዮጵያዊ ስብእና አሉታዊ ምልክቶች ናቸው፡፡

No comments:

Post a Comment