Thursday, November 10, 2016

የኢትዮጵያ መንግሥት በውጭ ሀገር ሠላማዊ ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ሠዎችን ቤተሠቦች አስሯል ሲል የመብት ድርጅቱ ሒውማን ራይትስ ወች አስታወቀ።

የኢትዮጵያ መንግስት በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከአገር ውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ተቋውሞ እየደረሰበት ይገኛል። በተለያዩ የውጭ ሃገራት ወያኔን በከፍተኛ ደረጃ በመቃወም ወደ አደባባይ የሚወጡትን ኢትዮጵያውን ማሰርና ማፈን ቢያቅተው በኢትዮጵያ የሚኖሩትን ቤተሰቦቻቸውን ማሰር እንደጀመረ የሰብአዊ መብት ድርጅት (Human Rights Watch)በ 27 ጥቅምት 2009ዓም ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል። በአውስትራሊያ ሜልቦርን በሰኔ 2008ዓም የሶማሊያ ክልል ፕሬዝዳንት የሆኑትን አቶ አብዲ መሃመድ ኡመርና የዚህ ክልል ተወካይ ያካተተ ቡድን ወደ አውስትራሊያ ሊያደርገውን ያቀደውን የስራ ጉብኝት በመቃወም ኢትዮጵያውያን በሜልቦርን አደባባይ ለሰልፍ ወጥተው ነበር። በዚህ ከፍተኛ ተቋውሞ ምክንያት ይህ የስራ ጉብኝት ተስተጋጉላል። በዚህ ሰልፍ ላይ የተገኙ የወያኔ ቅጥረኞች ፎቶ በማንሳት ለወያኔ በማቀበል የእነዚህን ኢትዮጵያውያንን ቤተሰቦች ለእስር እንዲዳረጉ አድርገዋል።

ቪኦኤ በዜናው ሽፋኑ የሰብአዊ የመብት ድርጅቱ  ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው  በቁጥጥር ስር ከዋሉት መካከል በአውስትራሊያ በሰኔ ወር ሠላማዊ ሠልፍ ላይ የተሳተፉ ኢትዮጵያዊ በዕድሜ የገፉ ወላጅ እናት እንደሚገኙበትም ታውቋል።

የዚህ ግለሰብ ሶስት ወንድሞችም የደረሱበት መጥፋቱን የመብት ድርጅቱ ዘግቧል።

የ25 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ ሹክሪ ሻሃፌ ጉሌድ ተወልደው ያደጉት በሶማሊያ ክልል ሲሆን በአውስትራሊያ ለአለፉት ስድሥት ዓመታት ኖረዋል፤ በአለፈው ሰኔ ወር ሜልበርን አውስትራሊያ የሶማሌ ክልል ፕሬዚዳንት አብዲ መሐሙድ ኡማር በቅፅል ስማቸው አብዲ ኢሌ ተብለው የሚታወቁት በጎበኙበት ወቅት ተቃውሞ መግለፃቸውን ይናገራሉ፡፡

የወያኔን አገዛዝና ወያኔን በመቃወም ከአውስትራሊያ በተጨማሪ በአውሮፓ በሰሜን አሜሪካ እንዲሁም በደቡብ አፍሪካ ከፍተኝ ሰልፎች በማድረግ ድምጹን በነጻነት በኢትዮጵያ ውስጥ ማሰማት ላልቻለው ጭቁኑ ኢትዮጵያ ህዝብ አንደበት በመሆን ይገኛሉ።

የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ምልምል አርበኛ ታጋዮች አሰልጥኖ አስመረቀ

የኢትዮጵያን ህዝብ ከጭቆናና የስቃይ ህይወት ለማላቀቅ እና አምባገነኑን የህወሓት አገዛዝ ገርስሶ ለመጣል የትጥቅ ትግል እያደረገ የሚገኘው አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ትምህርትና ስልጠና መምሪያ ለወራት ያክል በወታደራዊ፣ ፖለቲካዊና ሌሎች ተጓዳኝ ትምህርቶች ዙሪያ ሲያሰለጥናቸው የቆዩትን ምልምል አርበኛ ታጋዮች እሁድ ጥቅምት 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በደማቅ ስነ-ስርዓት አስመርቋል ፡፡

በዚህም የምረቃ ስነ-ስርዓት በዓል ላይ የድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮችና ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች የተገኙ ሲሆን የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ትምህርትና ስልጠና መምሪያ ሃላፊ አርበኛ ታጋይ ተስፋሁን ተገኝ ለተመራቂ አርበኛ ታጋዮች የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክታቸውን ካስተላለፉ በኋላ ከፊት ለፊታችን ትልቅ ግዳጅና ሃላፊነት ስለሚጠብቀን በምትመደቡበት ቦታ ሁሉ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳትሉ ሃገራዊና ድርጅታዊ ግዴታችሁን ለመወጣት በወታደራዊ ስነ-ምግባር የታነፀ ሰራዊት አስፈላጊ በመሆኑ ለዚህ ለተቀደሰ አላማ መከፈል ያለበትን የህይወት መሰዋዕትነት ለመክፈልና የኢትዮጵያን ህዝብ ከባርነት ህይወትና ከጭቆና ለማላቀቅ በሚደረገው የትጥቅ ትግል የበኩላችሁን ድርሻ መወጣት ይጠበቅባችኋል በማለትና አጠቃላይ የስልጠናውን ሂደት የሚመለከት ሪፖርታቸውን አሰምተዋል፡፡

በዚህ የምረቃ በዓል ላይ ተመራቂ አርበኛ ታጋዮች የእጅ በእጅ ውጊያን ጨምሮ የተለያዩ ትርኢቶችን በማሳየት ለበዓሉ ድምቀት ሰተውት የነበረ ሲሆን በተመራቂ አርበኛ ታጋዮች የቀረቡ ስነ-ፅሁፎችና መነባንቦች እንዲሁም አዝናኝና ትምህርት ሰጪ ድራማዎችም ልዩ ትኩረት የሳቡ እንደነበርና በቦታው የተገኙትንም ተጋባዥ እንግዶች አስደምመውት ውለዋል፡፡

Friday, November 4, 2016

በህዝባችን የነጻነት ተጋድሎ እየኮራን ለመጨረሻው ድል ታጥቀን እንነሳ!

በኦሮምያ እና በአማራ የተለያዩ ከተሞች የሚካሄደው የነጻነት ትግል በእጅጉ አስደማሚ ነው። ባለፉት ሳምንታት በጎንደርና በባህርዳር ለስድስት ቀናት እንዲሁም በተለያዩ የሰሜን ጎንደርና የምዕራብ ጎጃም ከተሞች የተደረገው የስራ ማቆም አድማ በአገራችን የቅርብ ጊዜ ታሪክ ያልታየ ወደር የለሽ ተግባር ነው። ህዝቡ የስራ ማቆም አድማ ያደረገው የሚበላውና የሚጠጣው ተርፎት እንዳልሆነ ይታወቃል። እንዲያውም በአገሪቱ የሰፈነው አስከፊ ድህነትና የኑሮ ውድነት እንኳንስ ስራ ተፈትቶ፣ 24 ሰአታት ቢሰራም የሚቋቋሙት እንዳልሆነ እናውቃለን። ነገር ግን ህዝቡ፣ ረሃቡንና ጥማቱን ለሳምንታት ችሎ የአድማውን ጥሪ ተግባራዊ አድርጓል። ይህ ምን ይነግረናል?  በቅድሚያ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ እንዳልነው ህዝቡ በዚህ ዘረኛና አፋኝ አገዛዝ መንገሽገሹን ያሳየበት ነው፤ “ልማቱ ተስፋፍቷል፣ ህዝቡም የደስታና የምቾች ኑሮ መኖር ጀምሯል” እያሉ በድህነቱና በብሶቱ ሲሳለቁበት ለቆዩት እውነተኛ ኑሮውን አሳይቷቸዋል። ይህንኑ ፕሮፓጋንዳ አምነው በመቀበል ወሬውን ሲያራግቡ ለነበሩ የአገር ውስጥና የውጭ የአገዛዙ ጠበቃዎች ግልጽ መልዕክት አስተላልፏል ።
እንዲሁም አገዛዙን ለማስወገድ ህዝቡ ማንኛውንም አይነት መስዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን ያሳየበት ነው። ረሃብና ጥማቱን ችሎ ከውስጡ የተጣበቀውን አለቅት ለማስወገድ መወሰኑን አሳይቷል። “ሩጥ ስንለው የሚሮጥ፣ ተቀመጥ ስንለው የሚቀመጥ ህዝብ ፈጥረናል” በማለት ሲሳለቁበት በነበረቡት ገዢዎች ላይ እየጠራ ተሳልቆባቸዋል። ከእንግዲህም እሱ በፈለገው እንጅ እነሱ በፈለጉት መንገድ እንደማይገዛላቸው ነግሯቸዋል። ከዚህ በተጨማሪ አድማው ከፍተኛ የህይወት መስዋትነት ሳያስከፍል በሌሎችም አካባቢዎች ሊተገበር የሚችል መሆኑን አሳይቷል። ህዝብ ቆርጦ ከወሰነ ምንም ነገር ለማድረግ የማይሳነው መሆኑንም እንዲሁ መስክረናል። ድርጅታችን አርበኞች ግንቦት 7 ህዝቡ ባደረገው ጠንካራ የስራ ማቆም አድማ የተሰማውን ኩራት ለመግለጽ ቃላት ያጥረዋል።
የህዝባቸውን ብሶት ብሶታቸው አድርገው፣ ህዝባቸውን በተሻለ ጎዳና ለመምራት የሚያስችል እውቀትና ክህሎት ያላቸው መምህራንም የትግሉ መሪ መሆን በመጀመራቸው በእጅጉ ኮርተናል። የዩኒቨርስቲ እና የሁለተኛ ደረጃ መምህራን ካድሬዎችን እያሳፈሩ የሸኙበት መንገድ አኩሪና በሁሉም ቦታ ሊተገበር የሚገባው ምርጥ የትግል ስልት ነው።  ምሁራን ለዲሞክራሲ፣ ፍትሃና ነጻነት የሚደረገውን ትግል በመምራት በኩል ከፍተኛ አስተዋጽዎ እንዳላቸው ድርጅታችን በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል። ምሁራን ትግሉ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ  እንዲመራ እንደሚራ ብቻ ሳይሆን ከነጻነት በሁዋላ ለሚመሰረተው ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ስርዓት ዋስትና በመሆናቸው የጀመሩትን ትግል እስከመጨረሻው መርተው ዳር ያደርሱታል ብለን እናምናለን። በተለያዩ ምክንያቶች ትግሉን ያልተቀላቀላችሁ ምሁራን በፍጥነት ትግሉን ተቀላቅላችሁ ህዝባችሁን በመምራት አካባቢያችሁን ነጻ እንድታወጡ በድጋሜ ጥሪ እናቀርባለን።
ለህዝባዊ ጥሪው ፈጣን ምላሽ የሰጣችሁ ነጋዴዎች፣ የባጃጅና ታክሲ አሽከርካሪዎች እንዲሁም የመንግስት ሰራተኞች፣ ድርጅታችን እየከፈላችሁ ላለው ወደር የለሽ መስዋትነት ከፍተኛ አክብሮት አለው።  ግብር ባለመክፈል እንዲሁም የተለያዩ የትግል ስልቶችን እንደያካባቢያችሁ ሁኔታ በመጠቀም ትግላችሁን ከቀጠላችሁ፣ አገዛዙ እናንተን ለመግደል ለተሰለፉት ጥቂት የአገዛዙ ወታደሮች፣ የደህንነት እና የፖሊስ ተቋማት የሚከፍለው ገንዘብ ስለማያገኝ  በመጨረሻ እጁን እንዲሰጥ ማድረግ ይቻላል። አሁንም ትግሉን ዳር የማድረስ ታሪካዊ አደራ ተጥሎባችሁዋል እና ትግላችሁን ቀጥሎ እንላለን።
ከንቱ ለሆነ አላማ የህዝባችሁ መጨፍጨፍ እረፍት ነስቷችሁ የጠመንጃችሁን አፈሙዝ በአፋኙ አገዛዝ ላይ ያዞራችሁ ፣  መሳሪያችሁን አስረክባችሁ ከህዝባችሁ ጋር የተቀላቀላችሁ ወይም በውስጥ ሆናችሁ በተለያዩ መንገዶች ለምትታገሉ የስራዊቱ አባላትም እንዲሁ ከፍ ያለ አክብሮታችን ይድረሳችሁ።  ከህዝቡ ጎን ለመቆም ያልወሰናችሁ ዛሬውኑ ወስናችሁ ከነጻነት ትግሉ ጎን ተሰለፉ። ለህዝብ ያልሆነ አገዛዝ ለእናንተ ሊሆን አይችልም። እናንተ ምን አይነት ህይወት እንደምትገፉ እናውቃለንና ከዚህ የስቃይ ህይወት ለመውጣት ብቸኛው መንገድ የስቃዮች ሁሉ ምንጭ የሆነውን የወያኔን አገዛዝ ማስወገድ በመሆኑ ጥሪያችንን እንደሰማችሁ የነጻነት ሃይሎችን ለመቀላቀል ወስኑ።
አርበኞች ግንቦት 7 እንደትናንቱ ሁሉ ዛሬም ባለው አቅም ሁሉ ህዝባዊ ትግሉን እየደገፈ ይገኛል። የመጨረሻው የነጻነት ደወል እሰከሚደወል ድረስም ትግሉን ከህዝቡ ጋር ሆኖ ይቀጥላል።

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ መሪዎች በመጪው አርብ ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጣሉ!!

አባይ ሚዲያ ዜና
አክሊሉ ታደሰ
ባሳለፍነው እሁድ ኦክቶበር 30 2016 ምስረታውን በመሪዎቹ የፊርማ ስነ-ስርአት ይፋ ያደረገውና በአራት ድርጅቶች የተመሰረተው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ መሪዎች በመጪው አርብ ኖቨንበር 4 2016 በዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው ናሽናል ፕሬስ ክለብ በንቅናቄው አላማና ራእይ ዙርያ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ንቅናቄው ባዘጋጀው በዚህ ጋዜጣዊ ጉባኤ ላይ አቶ ሌንጮ ለታ፡ዶ/ር ዲማ ነገዎ፡ ዶ/ር ኮንቴ ሙሳ፡ አቶ ሙሉነህ እዩዔልና አቶ በቀለ ወያ እንደሚገኙና ማብራርያ እንደሚሰጡ ሲታወቅ በታዛቢነትም አቶ ሀ/ገብርኤል አያሌው እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ በተጨማሪ በሚደረገው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የተለያዩ አለም አቀፍ ሽልማት ተሸላሚ የሆነችው ጋዜጠኛና አክትቪስት እሪዮት አለሙ እንደምትገኝ ሲታወቅ ይህ በናሽናል ፕሬስ ክለብ የሚደረገው ጋዜጣዊ መግለጫ አርብ ኖቨንበር 4 ከቀኑ 12፡15pm እስከ 2፡30pm ድረስ የሚቆይ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የሀገር ሉአላዊነት ማስከበር፡ የብሄር ብሄረሰቦችን መብት ማረጋገጥና እድገትና ብልፅግናን በማምጣት የፌደራል ስርአት መገንባት በሚሉ ሶስት ዋና ዋና አላማዎች የያዘውና በአራት ድርጅቶች የተመሰረተው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ በወያኔ እየተፈፀመ ያለውን የጅምላ ግድያ፤ እሰርና ወከባ አጥብቆ ያወገዘ ሲሆን የታወጀውም ህገ-ወጥ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለወራት ሀገሪቱን ሲንጥ የቆየውን ህዝባዊ እንቢተኝነት በሀይል ለመጨፍለቅ ታስቦ የታወጀ መሆኑንና ይህ አዋጅ በሀገሪቱ ላይ ዘላቂ መረጋጋትን ሊያመጣ እንደማይችል አስታውቆ  ለአሜሪካና የአውሮፓ መንግስታት በሀገራችን ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር እንዲኖር ለዚህ የወያኔ የሽብር አገዛዝ  ድጋፍ ከማድረግ ይልቅ  ከንቅናቄው ጋር በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ ማድረጉም ለማወቅ ተችሏል፡፡