Wednesday, April 30, 2014

የኢህአዴግ መንግስት በሚቃወሙትና በሚተቹት ላይ እየወሰደ ያለውን አፈና እና እስር የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲታገለው ጥሪ እናቀርባለን!!!

April 29, 2014

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ(አንድነት) የተሰጠ መግለጫ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

ፓርቲያችን አንድነት አበክሮ በተደጋጋሚ እንደገለፀው ኢህአዴግ ያነበረው አምባገን እና ክፉ ስርዓት ዜጎች በተለያየ ጊዜ የሚያነሱትን የሰብዓዊ መብት፣ የዴሞክራሲና የፍትህ ጥያቄ የሚቀለብሰው ወታደራዊ አቅሙን በመጠቀም ነው፡፡ በዚህ ህገ-ወጥ አካሄዱም ስርዓቱን ይቀናቀናሉ የሚላቸውን ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች፣ ታዋቂ ሰዎችና በግለሰብ ደረጃ ተቃውሞ የሚያሰሙ ዜጎችን የተለያየ ስም እየሰጠ ወደ እስር ቤት አውርዷል፡፡ እያወረደም ይገኛል፡፡ በርካታ ዜጎች የአስከፊው ስርዓት ሰለባ ሆነዋል፣ እየሆኑም ነው፡፡ ሀገራችን በመነጋገርና በመደማመጥ ችግራችንን የምንፈታባት እንዳትሆን ሆን ተብሎ ለዘላለም መንገስ በሚፈልጉ ባለጊዜዎች የፊጥኝ ታስራ፤ ዜጎቿ እንደቀደመው ስርኣት ሁሉ በእስር እየተሰቃዩ ይገኛሉ፡፡

እንደዜጋም በታላቋ ሀገራችን በሰቆቃ እንድንኖር ተፈርዶብናል፡፡ ኢህአዴግ ዛሬም ከመንገድ አፍሶ መውሰዱን ቀጥሏል፡፡ ማሰቃየቱንና ማንከራተቱን ገፍቶበታል፡፡ ከጊዜና ሁኔታዎች እንደመማር ዛሬም ለስርዓቱ አደጋ ናቸው የተባሉ ወጣቶች ሰበብ እየተፈጠረ ወደ ማሰቃያ ስፍራ እየተጋዙ ነው፡፡ የገዥው ፓርቲ አፈ-ቀላጤ በሆኑ ሚዲያዎች የታሰሩት ክስና ወደፊት የሚታሰሩት እነማን እንደሆኑ እየተነገረ ይገኛል፡፡ ወጣት አመራሮቻችንና አባላትን የማሸማቀቅ ስራ እየተሰራም ነው-ስራ ከሆነ፡፡

የኢህአዴግ መንግስት ሰሞኑንም በግል ተነሳሽነታቸው ለሀገራቸው አስተዋፅኦ ለማድረግ ወስነው በብዕራቸው የሰብኣዊ መብት እንዲከበርና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲረጋገጥ በሚወተውቱ የነበሩ የዞን ዘጠኝ አባላትና ጋዜጠኞች ላይ የወሰደው የእስር ርምጃ የሚያመለክተው በቀጣዩ አመት የሚካሄደውን ምርጫ አስመልክቶ የተወሰደ የማሸማቀቅና የወጣቶችን ጥያቄ ለመቀልበስ የሚፈልገው የአምባገነኑ ስርዓት ተግባር ነው፡፡

ፓርቲያችን ሚያዝያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም አመሻሽ ላይ ዞን 9 በተሰኘ ድረ ገጽ (ብሎግ) ላይ በሳል ፖለቲካዊና ማህበራዊ ትችቶችን በማቅረብ ከሚታወቁትን ወጣት ጋዜጠኞች ማህሌት ፋንታሁን፣ በፍቃዱ ሀይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ ዘላለም አጥናፍ ብርሀን፣ አቤል ዋበላ እንዲሁም ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ፣ ጋዜጠኛ አስማመው ኃ/ጊዎርጊስ እና ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት የሚሸረሽር እንደሆነ እናምናለን፡፡ አፈናው ግን ሌሎችን በሺዎች የሚቆጠሩ ብሎገሮችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችን እንደሚፈጥር አንጠራጠርም፡፡

የኢህአዴግ መንግስት የከፈተው የእስር ርምጃ በአስቸኳይ እንዲያቆምና የታሰሩትም ታሰሩ ከተባለበት ሰዓትና ደቂቃ ጀምሮ የሚገኙበትን አጠቃላይ ሁኔታ እንዲጣራ፤ መንግስት ያሰረበትን ተጨባጭ ማስረጃ ካለ ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ፤ ያ ካልሆነ ግን እስረኞቹን በአስቸኳይ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቅ እናሳስባለን፡፡ ፓርቲያችን ዘላቂው መፍትሄ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመፍጠር የሚደረገውን ትግል አፋፍሞ መቀጠልና በሰላማዊ ትግል አምባገነኑን ስርኣት ማስወገድ ብቻ እንደሆነ ያምናል፡፡

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ሚያዚያ 21 ቀን 2006 ዓ.ም

አዲስ አበባ

በዞን ዘጠኝ ጦማርያን እና በጋዜጠኞች ላይ የተወሰደው የእስር እርምጃ እንዳሣሰበው ሲ.ፒ.ጄ ገለጸ።

ሚያዚያ ፳፩ (ሃያአንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ዓለማቀፉ የጋሴጠኞች ተንከባካቢ ድርጅት(ሲፒጄ)  ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ መንግስት ሰሞኑን በ9 ጸሀፍያን ላይ የወሰደው የእስር እርምጃ፤ ሀሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ላይ ከተቃጡ የከፉ እርምጃዎች አንዱ ነው ብሏል።
“የኢትዮጵያ ባለስልጣናት በሰላማዊ መንገድ ሀሳብን መግለጽን እንደወንጀል እየቆጠሩት ነው” በማለት ነው -የሲፒጄ የምስራቅ አፍሪቃ ወኪል-ቶም ሩድስ-እርምጃውን የኮነኑት።
እሁድ ዕለት የመንግስት አቃቤ ህግ በ አዲስ ጉዳይ ዋና አዘጋጅ በ አስማማው ሀይለጊዮርጊስ፣ በፍሪላንስ ጋዜጠኞቹ በተስፋለም ወልደየስ እና በ ኤዶም ካሣዬ፣ እንዲሁም በጦማርያኑ በ አቤል ዋቤላ፣በ አጥናፍ ብርሀኔ፣በማህሌት ፋንታሁን፣ በዘላለም ክብረት እና በበፈቃዱ ሀይሉ ላይ  ከውጪ ድርጅቶች ጋር ይሠራሉ፣ ማህበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀምም በሀገሪቱ አለመረጋጋት እንዲፈጠር ይንቀሳቀሳሉ.. የሚል ክስ እንደመሰረተባቸው ሲፒጄ አውስቷል።
ተስፋለም፣አስማማውና ዘላለም ለፊታችን ሚያዚያ 28 ቀሪዎቹ ደግሞ ለሚያዚያ 29 እንደተቀጠሩ ከሀገር ውስጥ ጋዜጠኞች የደረሰውን መረጃ ዋቢ አድርጎ የጠቀሰው ሲፒጄ፤ በታሳሪዎቹ ላይ እስካሁን መደበኛ ክስ እንዳልተመሰረተ ጠቁሟል።
ሲፒጄ በመግለጫው-ፀሀፊዎቹ ዞን ዘጠኝ ተብሎ የሚጠራ የገለልተኛ አክቲቪስቶች ስብስብ አባል ሆነው የተለያዩ ዜናዎችንና ጽሑፎችን ይጽፉ እንደነበር  አመልክቷል።
“ዞን ሰጠኝ የተሰኘው ስያሜ ከቃሊቲ የተገኘ  መሆኑና  የጸሐፊዎቹ  መሪ ቃል፦”ስለሚያገባን እንጦምራለን” የሚል  መሆኑ በሲፒጄ መግለጫ ተመልክቷል።
ጦማርያኑና ጋዜጠኞቹ የታሰሩት ከደህንነቶች በሚደርስባቸው ወከባ ምክንያት ላለፉት ሰባት ወራት ዘግተውት የቆዩትን የፌስቡክ ገፃቸውን ዳግም በከፈቱ ማግስት መሆኑን እንደተረዳም የጋዜጠኞች መብት ተንከባካቢ ተቋሙ ገልጿል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ አማካሪ የሆኑት ጌታቸው ረዳ ለሮይተርስ የዜና ወኪል ፦”የታሰሩት ጋዜጠኞች አይደሉም፤ እስሩ ከጋዜጠኝነት ሥራቸው ጋር የተገናኘ አይደለም። ከከባድ ወንጀል ጋር የተገናኘ ነው” ማለታቸውን ሲ.ፒ.ጄ ጠቁሟል።
“በጋዜጠኝነት ወይም ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብት ላይ የቃጣነው በትር የለም። ሆኖም ማንም ቢሆን ሙያውን ሽፋን በማድረግ ወንጀል ለመፈፀም ሲሞክር በህግ ይጠየቃል” ሲሉም አክለዋል-አቶ ጌታቸው ረዳ።
“የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ወደለየለት ፈላጪ ቆራጭ አገዛዝ  ማዘንበላቸውን እንዲገቱና በሀገሪቱ  ነፃ ሀሳቦች ይንሸራሸሩ ዘንድ እንዲፈቅዱ ጥሪ እናቀርባለን” ብለዋል-ሚስተር ቶም ሩድስ።
የታሰሩት 9ኙም ጸሀፊዎች በአስቸኳይ ሊፈቱ ይገባል ሲሉም ጠይቀዋል። ዓለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተቋም ሂውማን ራይትስ ዎችና ሌሎች ድርጅቶችም የ ኢትዮጵያ ባለስልጣናት በጦማርያኑ እና በጋዜጠኞቹ ላይ የወሰዱትን እርምጃ በማውገዝ ፤ ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ዛሬ አዲስ አበባ የሚገቡት የ አሜሪካ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ  እስረኞቹን እንዲፈታ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ግፊት እንዲያደርጉ ጠይቋል።
የተለያዩ ዓለማቀፍ የሚዲያ ተቋማትም ሰሞኑን የኢትዮጵያ መንግስት በ9ኝ ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ላይ የወሰደውን የማሰር እርምጃ ሽፋን ሰጥተውታል።
ከሚዲያ ተቋማቱ መካከል ኤ.ቢ.ሲ ኒውስ፣ ሲ ኤን.ኤን፣ ዋሽንግተን ፖስት፣ ሬውተርስ፣ እና አልጀዚራ ይገኙበታል።
እንዲሁም የዩናይትድ ስቴትስ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ በጉብኝታቸው ስለታሰሩት ጦማርያን እና ጋዜጠኞች አጠንክረው እንደተናገሩ  የኒውዮርክ ታይምሱ ታዋቂ አምደኛ  ኒኮላስ ክሪስቶች ለሰጣቸው አስተያዬት፤ “ በጣም  ጠቃሚ ጉዳይ ነው። ዩናይትድስቴትስ  በመላው ዓለም ላይ የፕሬስ ነፃነትን በመደገፍና ከጥቃት በመከላከል ባላት ጠንካራ አቋም ትቆያለች” በማለት ምላሽ ሰጥተውታል።

Monday, April 28, 2014

በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋሉት ጋዜጠኞችና ብሎገሮች ፍርድ ቤት ቀረቡ

ዲስ ጉዳይ) ፖሊስ ለምርመራ 10 ቀናት ጠይቋል ባለፈው ሳምንት ሚያዝያ 17 እና 18 ቀን 2006 ዓ.ም በፖሊስ ቁጥጥር ስር
የዋሉት 3 ጋዜጠኞች እና 6 ብሎገሮች ዕሁድ ሚያዝያ 19 ቀን 2006 ዓ.ም አራዳ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡ ሲሆን
ፖሊስ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ ጠይቆባቸዋል። በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ በማዕከላዊ እስር ቤት የቆዩት ተጠርጣሪዎች ሰኞ ለፍርድ
እንደሚቀርቡ የተጠበቀ ቢሆንም ባልተለመደ ሁኔታ ዕሁድ እንዲቀርቡ የተደረገ ሲሆን የክሱም ሃሳብ በአጭሩ “ሀገሪቱን በሶሻል
ሚዲያ ለማተራመስ ራሱን የመብት ተሟጋች ነኝ ብሎ ከሚጠራ የውጭ ኃይል ጋር በሃሳብም በገንዘብም ተረዳድተውና
ተስማምተው የብጥብጥ ቅስቀሳ ለማነሳሳት አቅደው ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል” የሚል ነው፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ተመሳሳይ
ክስ የቀረበባቸው
ቢሆንም በ3 የተለያዩ
መዝገቦች ተከፋፍለው
ነው ፍርድ ቤት
ቀረቡት፡፡ የአዲስጉዳይ
ጋዜጠኛ አስማማው
ኃይለጊዮርጊስ፣ የአምቦ
ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህር
የሆነው ዘላለም ክብረት
እና የቀድሞው አዲስ ነገር
ጋዜጠኛና በአሁኑ ወቅት
በአዲስ ስታንዳርድ
መጽሔት ላይ የሚሰራው
ተስፋለም ወልደየስ
በመዝገብ ቁጥር
118722 የተጠቃለሉ ሲሆን፤ አጥናፉ ብርሃነ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና ኤዶም ካሣ በመዝገብ ቁጥር 118721 እንዲሁም በፍቃዱ
ኃይሉ፣ ማህሌት ፋንታሁን እና አቤል ዋበላ በመዝገብ ቁጥር 118720 የተካተቱ ተጠርጣሪዎች ናቸው።
በመዝገብ ቁጥር 118721 እና መዝገብ ቁጥር 118722 የተካተቱት ተጠርጣሪዎች ለሚያዝያ 29 ቀን 2006 ተቀጥረዋል።
ጉዳያቸው በመዝገብ ቁጥር 118720 የተካተተው ተጠርጣሪዎች ደግሞ ለሚያዚያ 30 ቀን 2006 ዓመተምህረት ተቀጥረዋል።

Sunday, April 27, 2014

የአዲስ አበባ ፖሊሶች የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችንና ደጋፊዎችን ለማስፈራራት ሙከራ እያደረጉ ነው

ሚያዚያ ፲፯ (አስራ ሰባት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በመጪው እሁድ በጃንሜዳ ለሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ የአዲስ አበባ መስተዳድር እውቅና ቢሰጥም ፣ የአዲስ አበባ መስተዳድር ፖሊሶች ህዝቡ በብዛት እንዳይገኝ ለማድረግ የማስፈራሪያ እርምጃ እየወሰዱ መሆኑን የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ወጣት ብርሃኑ ተክለ ያሬድ ገልጿል።
ወጣት ብርሃኑ እንዳለው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር በሰልፉ ላይ አንድም ነገር ቢከሰት እንዲሁም ከተሰጣችሁ ጊዜ አንድ ማይክሮ ሰከንድ ብታልፉ ሰልፉን እንበትናለን በማለት ለማስፈራራት ሞክረዋል።
ማስፈራሪያውን የሰጡት የፖሊስ አዛዡ በስም ይታወቁ እንዲሆን ጥያቄ የቀረበለት ወጣት ብርሃኑ፣ ኮሚሽነሩ ማንነቱን የሚገልጽ መረጃ በጠረጴዛው ላይ ባለማስቀመጡ ስሙን ለማወቅ እንዳልተቻለ፣ ነገር ግን ቢሮው ውስጥ አብረው የነበሩትን ኮሚሽነር እንደሚያውቃቸው ገልጿል
ቅስቀሳው በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ ና የህዝቡም ማበረታቻ ጥሩ መሆኑን  የገለጸው ወጣት ብርሃኑ ፣ ነገር ግን  በቅስቀሳ ላይ የነበሩ 25 አባሎቻቸው ታስረው እስካሁን አለመፈታታቸውን ገልጿል።
ወጣት ብርሃኑ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ግብ ሳይሆን ወደ ቀጣዩ ትግል መሸጋገሪያ መሆኑን ገልጾ ፣ የአዲስ አበባ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ ድምጹን ያሰማል ብሎ እንደሚያምን ተናግሯል።
ስቱዲዮ ከመግባታችን በፊት በደረሰን ዜና ደግሞ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት ሊቀመንበሩ ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፣ ምክትሉ አቶ ስለሺ ፈይሳ እና የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ በፖሊስ ተይዘው ወደ እስር ቤት ተጉዘዋል። ወደ እስር ቤት እየተጓዙ በነበረበት ወቅት ኢንጂነር ይልቃልን አነጋግረነው ነበር።

ከኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ(ኢጋመ) የተሰጠ መግለጫ፣ የጋዜጠኞቹና የአክቲቪስቶቹ እስር አሳሳቢ ነው፡

April 26, 2014

ትላንት ሚያዝያ 17 2006 አመሻሽ ላይ ዞን 9 በተሰኘ ድረ ገጽ (ብሎግ) ላይ በሳል ፖለቲካዊና ማህበራዊ ትችቶችን በማቅረብ ከሚታወቁት ፀኀፍት መሀከል 7 ቱ (ማህሌት ፋንታሁን በፍቃዱ ሀይሉ ናትናኤል ፈለቀ ዘላለም ክብረት አጥናፍ ብርሀነ አቤል ዋበላ ኤዶም ካሳዬ) እና የአዲስ ነገር ባልደረባ የነበረው ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸዉ ይታወቃል፡፡ ግለሰቦቹ በተለያየ ቦታ በየስራ ገበታቸዉ ላይ እያሉ ሁሉም በተመሳሳይ ሰዓት በፀጥታ ሀይሎች ተይዘዉ ማዕከላዊ ምርመራ ማዕከል ታስረዉ የሚገኙ ሲሆን፤ የተለያዩ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት እስሩ በደንብ የታሰበበት ነበር፡፡

የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ ታሳሪዎቹ ታሰሩ ከተባለበት ሰዓትና ደቂቃ ጀምሮ የሚገኙበትን አጠቃላይ ሁኔታ ለማጣራት አየሰራ ሲሆን ፤ እስካሁን በሰበሰበዉ መረጃ መሰረት ልጆቹን ለእስር የሚያበቃ ምን አይነት ማስረጃ እንደተገኘባቸው ለማወቅ አልቻለም፡፡

ሆኖም ግን ለእስር ከመዳረጋቸው በፊት ከመንግስት ሲርስባቸዉ በነበረዉ ህገወጥ ድርጊቶች ምክንያት ለረጅም ጊዜ ስራቸዉን ካቋረጡ በኋላ በቅርቡ ወደ ስራ መመለሳቸዉን ይፋ አድርገው እንደነበር ከድረገጻቸው ላይ ለመረዳት ችለናል፡፡ ይህ ጉዳይ እስሩን ይበልጥ አሳሳቢ አድርጎብናል፡፡ ስለሆነም የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መንግስት ታሳሪዎቹን ለማሰር ያበቃዉ ተጨባጭ ማስረጃ ካለ ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግ፤ ያ ካልሆነ ግን እስረኞቹን በአስቸኳይ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቅ እናሳስባለን፡፡

የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

Thursday, April 24, 2014

ሰበር ዜና፣ ፖሊስ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትን ማሰሩን ቀጥሏል

April 24, 2014

በዳንኤል ሃረጋዊ

ፖሊስ ቀስቃሾቹን እያሰረ ነው ፖሊስ የእውቅናው ደብዳቤ አልደረሰኝም በሚል በተለያዩ የአዲስ አበባ ክፍሎች ቅስቀሳ ላይ የተሰማሩትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች እያሰረ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በየካ፣ ካሳንቺስና አቧሬ ሲቀሰቅሱ የነበሩ ወጣቶች በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል፡፡ ቀስቃሾቹ ሰልፉ እውቅና እንደተሰጠው የሚያመለክተውን ወረቀት ለፖሊስ ቢያሳዩም ፖሊሶች የእውቅናው ደብዳቡ አልደረሰንም በሚል አስረዋቸዋል፡፡ ቀስቃሾቹ የያዙት የእውቅና ደብዳቤ ግልባጭ ለፖሊስ የተጻፈበት በመሆኑ ሰልፉ እውቅና አግኝቶ እያለ ሆን ተብሎ ለማደናቀፍ እንደሆነ ምክትር ሊቀመንበሩ አቶ ስለሽ ፈይሳ ገልፀዋል፡፡

በላም በረት፣ ቦሌ ድልድይ፣ ኮተቤ፣ መገናኛ ቅስቀሳ ሲያደርጉ የነበሩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች ቅስቀሳቸውን በተሳካ መልኩ አጠናቀዋል፡፡ በሌሎች አካባቢዎች የተሰማሩት አባላት ቅስቀሳውን አጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ በሌላ በኩል በየካ፣ ካሳንቺስና አቧሬን ጨምሮ በሌሎች የከተማይቱ ክፍሎች ፖሊስ ከ20 በላይ አባላትን ማሰሩ ታውቋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ ፖሊስ ቅስቀሳው ላይ ያልነበሩ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችንም እያሰረ ነው፡፡ የታሰሩትን አባላትና ደጋፊዎች ሁኔታ ለማጣራት ወደ የካ ፖሊስ ጣቢያ ያቀኑ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን ፖሊስ አስሯቸዋል፡፡

በዛሬው ቀን ካሳንቺስ ስድስተኛ ፖሊስ ጣቢያ የታሰሩት

1. ብሌን መስፍን
2. አስናቀ በቀለ
3. መስፍን
4. ተስፋዬ አሻግሬ
5. እዮብ ማሞ
6. ኩራባቸው
7. ተዋቸው ዳምጤ

የካ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች

1. ፍቅረ ማሪያም አስማማው
2. እያስፔድ ተስፋዬ
3. ጋሻው መርሻ
4. ተስፋዬ መርኔ
5. ሀብታሜ ደመቀ
6. ዘሪሁን ተስፋዬ
7. ጌታነህ ባልቻ
8. ንግስት ወንዲፍራው
9. ሜሪን አለማየሁ ናቸው

የካ አካባቢ ታስረው የሚገኙ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ምግብ እንዳይገባላቸው ተከልክለዋል፡፡ በሌላ በኩል አህመድ መሃመድ፣ሀይለማሪያም፣ ሱራፌልና አምሃ የተባሉ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት መገናኛ አካባቢ ተይዘው ወደ የካ ፖሊስ ጣቢያ ተዘዋውረዋል፡፡ በአጠቃላይ የካ ፖሊስ ጣቢያ የሚገኙት 14 መሆናቸው ታውቋል፡፡ በሁሉም ፖሊስ ጣቢያዎች የሚገኙት አመራሮችና አባላት በአሁኑ ወቅት ቃል እየሰጡ ሲሆን ሊያድሩ እንደሚችሉም ተነግሯቸዋል፡፡

በሌላ በኩል የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ቢሮ ተደውሎ የሰላማዊ ሰልፉን አስተባባሪዎች ጧት ሁለት ሰዓት ላይ ‹‹ኑ እና እንነጋገር!›› የሚል ጥሪ አድርጓል፡፡ ከሰልፉ አስተባባሪዎች መካከል አቶ ጌታነህ ባልቻ ታስሮ ይገኛል፡፡

Tuesday, April 22, 2014

የኢሳትየድጋፍኮሚቴበኖርዌይየባንክሒሳብቁጥርከፈተ

ሚያዚያ ፲፬ (አስራ አራት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢሳትኖርዌይየድጋፍኮሚቴ፤በኦስሎናበተለያዩአካባቢዎችኢሳትን  ለማጠናከርናየአቅማቸውንለማበርከትለሚተጉየኢሳትደጋፊዎችናቤተሰቦች፤በያሉበትቀላልእናአመቺየሆነውንየአከፋፈልመንገድይጠቀሙዘንድበማሰብ፤በኖርዌይኦስሎበኢሳትስም  የባንክሒሳብቁጥርመክፈቱንበደስታገልጿል።
በተለያየምክንያትየባንክሒሳብቁጥራችንለመጠቀምሁኔታዎችየማያመቿችሁየኢሳትደጋፊዎችለዚሁበተዘጋጁየገነዘብመቀበያደረሰኞችበመጠቀምኢሳትንበመደገፍለድምፅአልባወገንዎድምፅ እንዲሆኑ ኮሚቴው አስታውቋል። የሂሳብ ቁጥሩን በድረገጻችን የምታገኙት መሆኑን ለማስታወቅ እንወዳለን።
የባንክ ሒሳብ ቁጥር
DNB 1503 462 8537
Oslo Norway ሲሆን ለተጨማሪ መረጃ ፦ 452 06 390 / 947 11 734  ይደውሉ ።
የኢሳት የድጋፍ ኮሚቴ በኖርዌይ

Monday, April 21, 2014

[የፋሲካ ወግ] ቴሌፎኑ ‘ለግዜው’ ጥሪ አይቀበልም – ክንፉ አሰፋ (ጋዜጠኛ)

“የደወሉላቸው ደምበኛ ለግዜው ጥሪ አይቀበሉም።…” የምትለዋ አሰልቺ የቴሌ መልእክት ያላጋጠመው ቢኖር ወደ ኢትዮጵያ ስልክ ደውሎ የማያውቅ ሰው ብቻ መሆን አለበት። ኮ/ል መንግስቱ ሃይለማርያም ወደ ቀድሞ ወዳጆቻቸው መደዋወል ጀመሩና በመሃል ተስፋ ቆረጡ አሉ። አስር ለሚያህሉ አርሶአደሮች እና የሰራዊቱ አባላት ዘንድ ደውለው አልተሳካለቸውም። ለሁሉም ጥሪ ያገኙት ምላሽ “የደወሉላቸው ደምበኛ ለግዜው ጥሪ አይቀበሉም።” የሚል ሲሆንባቸው ራሳቸውን ነቀነቁ። ሰው ሁሉ የጨከነባቸው መሰላቸው። እንዲህም አሉ። “የሃገሬ ሰው እንኳን የስልክ ጥሪ፤ የእናት ሃገር ጥሪስ መች ተቀበለ።”

ለአመታት በተከታታይ በሁለት ድጅት እያደገች ያለች ሃገር የስልክ መስመር ችግር ይገጥማታል ብሎ ማሰብ ይከብዳል። ችግሩን በደንብ ላልተረዳው፣ ሰው የሞባይል ስልክ የሚገዛው እንዲሁ ይዞ ለመታየት ነው ያስብል ይሆናል። ይህ አባባል በከፊል ትክክል ነው። ዘመናዊ ስልክ በመያዝ ለላንቲካነት ብቻ የሚጠቀሙበት ሰዎች አይጠፉም። የቻይናው ቀፎ ከሞዴል አርሶ አደሮች አልፎ ተራው አርሶ-አደር እጅ ላይም ገብቷል። አብዛኞቹ ግን ተንቀሳቃሽ ስልካቸውን አይጠቀሙበትም። ለዚህም ይመስላል በርካታ ተንቀሳቃሽ ስልክ የሚይዙ ሰዎች እንዲሁ ለእይታ እና ለላንቲካ ብቻ የሚመስላቸው። አገልግሎቱን በተመለከተ ግን 99 በመቶ የሚሆነው ችግር የመዋቅር ችግር ነው።

ለዓውዳመቱ ወደ ኢትዮጵያ ስልክ የደወላችሁ ካላችሁ፤ ይህ ነገር እንደገጠማችሁ እርግጥ ነው። ዘንድሮ ደግሞ ቴሌ ከፍቷል። የሞባይሉ መስመርማ እንደ አይን እልም ብሎ ነው የጠፋው። ከበርካታ ሙከራ በኋላ መስመር ያገኘ ሰው ካለ በደስታ ይዘልላል። የተቀባዩም ስልክ ካቃጨለ ተዓምር ነው የሚባለው። ከርማ ብቅ እንደምትለው የአዲስ አበባ መብራት… ልክ እንደ ቧንቧ ውሃ፤ ስልኳም “መጣች – መጣች!” ብሎ መጨፈሩ አይቀርም።
(በመከራ መስመር ሲገኝ እንዲህ ያስደስታል)

“እንኳን አደረሳችሁ!” ለማለት እኔም ወደ ሃገር ቤት ስልክ መታሁ።
“የደወሉላቸው ደምበኛ ለግዜው ጥሪ አይቀበሉም።” የሚል መልስ ነበር ያገኘሁት። ለሁለተኛ ግዜ ስሞክር ደግሞ “የደወሉት ስልክ ለግዜው ከአገልግሎት መስጫ ክልል ውጪ ነው።” የሚል ምላሽ አገኘሁ። ደቂቃ ባልሞላ ግዜ ውስጥ ጥሪ ያማይቀበለው ስልክ ከአገልግሎት መስጫ ክልል መውጣቱ አስገረመኝ። ተስፋ ሳልቆርጥ ደገግሜ ሞከርኩ። ቢያንስ ከአስር ግዜ ሙከራ በኋላ፤ መስመር አገኘሁና ሎተሪ የወጣልኝ ያህል ተሰማኝ።

ደስታዬ ግን ብዙም አልዘለቀም። በመሃል እንግዳ ነገር ተፈጠረ። ስልኩን የተቀበለኝ የደወልኩለት ሰው አልነበረም። የተፈጠረው ክስተት – ባለንበት የመረጃ ዘመን እንደ 17ኛው ክፍለዘመን “ቴሌ በኦፐሬተር መስራት ጀመረ እንዴ?” ያሰኛል። ነገሩ ግን ሌላ ነው። ስልኩን ያነሳው የተለመደው የስልክ ጠላፊ ስለመሆኑ አንዳች ጥርጥር አልነበረኝም። ሶማሌያውያን መርከብ ሲጠልፉ ጸሃዩ መንግስታችን ደግሞ የስልክ ፓይረት መሆኑን ሂዩማን ራይትስ ዎች በዚያን ሰሞን ነግሮን ነበርና።

ውጭ ሃገር ያለ ኢትዮጵያዊ ዘመድ ለመጠየቅ መደወሉ አይቀርም። ተስፋ የማይቆርጥ፤ ደጋግሞ ይሞክራል። እንደ እድል የስልኩን መስመር ካገኘ ደግሞ ሌላ ችግር ይገጥመዋል። ዘው ብለው የሚገቡ የስልክ ጠላፊዎች መስመሩን ያውኩታል። ሌላው አማራጭ ደግሞ አጭር የጽሁፍ መልእክት ነው። በኢትዮጵያ ቴሌኮም አጭር መልእክት ከመላክ ይልቅ ደብዳቤ ጽፎ በፖስታ መላኩ እየፈጠነ መጥቷል። አጭር መልእክት የሚደርሰው ከቀናት ብኋላ ነው። ከላኪው ዘንድ መልዕክቱ መድረሱ ቢረጋገጥም ተቀባዩ ጋ ጨርሶ ላይደርስም ይችላል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ በቅርቡ በሰጡት ጋዤጣዊ መግለጫ “የኢትዮጵያ ቴሌኮም ቴክኖሎጂ ከዴንማርክ፣ ከኖርዌይ እና በከፊል ከእንግሊዝ ቴክኖሎጂ ጋር አንድ ነው” ብለው ነበር። በዚህ መግለጫቸው አቶ ሃይለማርያም የኢትዮጵያን የኢንተርኔት አገልግሎት፣ እንዲሁም የስልክ መስመሩ ጥራት እና አስተማማኝነት በደንብ አድርገው ነበር “ለጋዜጠኞቹ” የገለጹላቸው። ይህን ተናግረው እንዳበቁ ግን የራሳቸውም ስልክ መጠለፉን ሰማን። ጆሮ ለባለቤቱ ባዳ ነው እንዲሉ አልሰሙት ይሆናል እንጂ፤ “እኛ ሲም ካርድ፤ አንተ ደግሞ ቀፎ ነህ!” ይሏቸዋል – ከላይና ከታች ያሉ አለቆቻቸው።

የኢትዮጵያን ስልክ አገልግሎት ከዴንማርክ፣ ኖርዌይ እና እንግሊዝ ጋር አወዳድረው ማወደሳቸው ግን ራሳቸው ካዴሬዎቹንም ሳይቀር ሳያሰፍራቸው አልቀረም። ሰውየው የኢትዮጵያን ቴሌኮም እያወዳደሩ ያሉት 99.9 በመቶ ሳያቋርጥ አገልግሎት ከሚሰጠው አራተኛው ጀንሬሽን የምእራቡ ቴክኖሎጂ ጋር ነው። መቼም ሁሉም ይዋሻሉ። ነብሳቸውን ይመርና አቶ መለስ ዜናዊም ይዋሹ ነበር። ለዛ ያለው ውሸት አለ። እጅ፣ እግርና አይን የሌለው ውሸትም አለ። እንዲህ አይነት ያፈጠጠ ውሸት ግን እመራዋለሁ የሚሉትንም ሕዝብ እንደመናቅ ይቆጠራል። እኚህ ሰው የሞራል እሴታቸውን ሁሉ አሽቀንጥረው ሊጥሉት ይችሉ ይሆናል። ምሁራዊ ግብአታቸውንም ለተራ ፖለቲካ ጥቅም ሊያስወግዱት ይችላሉ። እምነታቸውስ እንዲህ አይነቱን ቅጥፈት ይፈቅድላቸው ይሆን?
የቴሌ የኢንተርኔት አገልግሎት የመንግስት አልባዋ ሶማልያን አንድ መቶኛም። ኮሜዲያን ክበበው ገዳ እንደቀልድ የነገረኝ ቁም-ነገር የኢትዮጵያን ኢንተርኔት ፍጥነት በደንብ ይገልጸዋል። ክበበው ሰሜን አሜሪካ የስራ ጉብኝቱ ወቅት ፎቶ ተነስቶ ለቤተሰቡ በኢሜይል ይልካል። የላከው ፎቶ መድረሱን ለማረጋገጥ በነጋታው ወደ አዲስ አበባ ደወለ።
“ፎቶ ደረሰ?”
“አልደረሰም!”
ሌላ ቀን እንደገና ደውሎ የላከው ፎቶ እንዳልደረሰ ተነገረው። ለሶስተኛ ግዜ ደውሎ ኢሜይሉ እንደደረሰ ጠየቀ። አሁንም አልደረሰም ተባለ። እንዲህ እያለ ሳምንት ሞላው።
“በሳምንቱ እኔ ቀድሜ ደረስኩ።” ነበር ያለው ክበበው።
የኢሜይል መልእክቱ መድረሱ ከተረጋገጠ በኋላ – ሌላ ችግር ገጠመው። ኢሜይሉ ሲከፈት ግማሽ አካሉን ነበር የሚያሳየው። ፎቶው እስኪያወርድ (ዳውንሎድ እስኪያደርግ) ደግሞ ግማሽ ቀን መፍጀቱ ግድ ነበር።

ይህንን አገልግሎት ነው አቶ ሃይለማርያም ከምእራቡ አለም አገልግሎት ጥራትና ፍጥነት ጋር እያወዳደሩ የሚነገሩን። በአስር ሜትር ርቀት ላይ ሆኖ በስልክ መገኛኘት ህልም በሆነበት ሃገር፤ ስለ ስልክ ጥራት መናገር ቅጥፈት ብቻ ሳይሆን የሰውየውንም የሞራል ውድቀት ያመላክታል።
የኢትዮጵያ ቴሌኮም ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ቀጥሎ ትልቅና ግዙፍ የሃገሪቱ ተቋም ነው። እድገቱ ግን ያሳዝናል። በአስር አመት ግዜ ውስጥ ብቻ እንኳን እድገቱ በ75 በመቶ ቁልቁል ወርዷል። ለዚህ ዋናው ምክንያት ተቋሙ አገልግሎት መስጠቱን አቁሞ ወደ ስለላ ተቋም መቀየሩ ነው። ባለፈው ወር ይፋ የሆነው ባለ 100 ገጹ የሂዩማን ራይትስ ዎች ዘገባ ይህንን መንግስታዊ የስልክ እና የኢንተርኔት ጠለፋ አረጋግጧል።

“የተቃዋሚ ፓርቲ አባል የነበረን አንድ ዜጋ አፍነው ካሰሩት በኋላ ውጭ የተደዋወለበትን የስልክ ቁጥር ዝርዝር አሳዩት።” ይላል ጠቀማጭነቱ ዩናይትድ ስቴትስ የሆነው አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋም። ሰውየው የታሰረው ያልተከፈለ የስልክ ሂሳብ ኖሮበት አልነበረም። ባለስልጣናቱንም አላማም፣ ወይንም መንግስትን በሃይል ለመገልበጥ አላሴረም። ወንጀሉ፤ ከውጭ ሃገር ስልክ ስለተደወለለትና ከወዳጅ ዘመዶቹ ስለተወያየ ብቻ ነበር። ይህ ደግሞ ፍጹም እንግዳ ነገር ነው። ከተለምዶ ልማታዊ መንግስት አስተሳሰብም እጅግ የከፋ!

የዜጎች ሁሉ ስልክ በቴሌ በኩል ይጠለፋል። እንደ ስካይፕ እና ቫይበር ያሉ የቮይስ ኦቨር ስልኮች ደግሞ ፊን ፊሸር በተባለ የኮምፒዩተር ቫይረስ አማካኝነት ይጠለፋሉ። በዚህ አይነት በዜጎች የግል ህይወት ሳይቀር እየገቡ ቴሌን ሙሉ በሙሉ የስለላ ተቋም አደረጉት።

ሞባይል ስልክ እና ኢንተርኔት በአፍሪካ አህጉር በእጅጉ እየተስፋፋ ይገኛል። ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ 30 በመቶ የሚሆነው የአፍሪካ ህዝብ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጠጠቃሚ እየሆነ መጥቷል። በኢትዮጵያ ግን የስልክ እና የኢንተርኔት ተጠቃሚው ከ2.5 በመቶ አልዘለቀም።

ጎረቤት የሆነችው የኬንያ ህዝብ 40 በመቶ የዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ ነው። መንግስት አልባዋ ሶማልያ እንኳን፣ ስድስት የቴሌፎንና ስልክ አቅራቢ ኩባንያዎች አሏት። የሶማልያ ህዝብ ጥራት ያለው የስልክ መስመር እና ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚ ከሆነ ሰንበትበት ብሏል። በኡጋንዳም የዚህ አገልግሎት ሰጪ በመንግስት ሞኖፖሊ ስር አይደለም። ከሰባት በላይ የግል ኩባንያዎች እየተፎካከሩ ፈጣን አገልግሎት እየሰጡ ጠተቃሚውን ህዝብ ወደ 50 በመቶ አድርሰውታል።

ያለነው በመረጃ ዘመን ነውና ያለመረጃ እና ያለ መረጃ ቴክኖሎጂ እድገት አመጣለሁ ማለት ዘበት ነው የሚሆነው። የኢትዮጵያ ሁኔታ ግን ሃገሪቱን ወደ መረጃ ሳይሆን ወደ ጨለማ ዘመን ነው እየመራት ያለው። እንድምናነበው ከሆነ የኢትዮጵያን ቴሌኮም ለማስፋፋት ከሶስት ቢሊየን ዶላር በላይ ወጪ ሆኗል። ይህ ገንዘብ በትክክል ስራ ላይ ቢውል አባይንም ይገድባል። ለዚህ የእድገት ሳይሆን ይልቁንም የጥፋት ጎዳና ተባባሪ የሆነቸው ቻይናም በውጭ ምንዛሪ እየተከፈላት ቴሌን ብቁ የስለላ ተቋም አድርጋዋለች። የኢኮኖሚ ልማትና ትብብር ሚኒስትሩም ከተለያዩ የኢንዱስትሪ ሃሮች ጋር በመተባበር የቴሌ ጥራት ላይ ሳይሆን የሚሰራው የስለላ ሃርድዌር እና ሶፍትዌር ማስገባቱ ላይ ነው።

የሃገሪቱ ግብር ከፋዮች ገንዘብ መልሶ ራሳቸውን እንዲያፍን መደረጉ እጅግ ያሳዝናል።

የቴሌ መልስ መስጫ ላይ ያለው መልዕክት ግን መሻሻል አለበት። “ለግዜው” የሚለው ቢቀየር ድርጅቱን ከሃሜት ያድነዋል። እናም መልእክቱ እንዲህ ነው መሆን ያለበት፣
“የደወሉላቸው ደምበኛ ‘ለሁልግዜ’ ጥሪ አይቀበሉም። ..”
ከዚያ በኋላ ደዋዩም ተስፋ ቆርጦ መደወል ያቆማል።

Friday, April 18, 2014

ይድረስ ለብዙሃኑ የሠራዊቱ አባል ወገናችን!!


የመከላከያ ሚኒስትር በተሰኘው የውሸት ሥልጣን ላይ የተቀመጠው አድርባይ ሲራጅ ፈርጌሳ ለይስሙላው ምክር ቤት ባቀረበው ሪፓርት፣ “የመከላከያ ሚኒስትር የብሔር ተዋጽዖ የተመጣጠነ” እንደሆነ ገለፀ። እንደ ሰውየው ሪፓርት ከሆነ የመከላከያ ሠራዊቱ 29.46 በመቶ አማራ፣ 25.05 በመቶው ከደቡብ ብሔሮች የተውጣጣ፣ 24.45 በመቶ ኦሮሞ፣ 17.47 በመቶው ትግራይ እና የተቀሩት ክልሎች ድርሻ 4.17 በመቶ ነው። መረጃው የተቀናበረው በክልል ቢሆንም የቀረበው ግን በዘር ነው። “ተመጣጠነ” የተባለውም የክልሎች ተዋጽዖ ሳይሆን የዘር ተዋጽዖ ነው። ሠራዊቱን እንዲህ በዘር ሸንሽንኖ የስታትስቲክስ ጨዋታ መጫወት አሳዛኝም አሳሳቢም ነገር ነው። የሆነ ሆኖ ይህ መረጃ፣ መረጃ ነው ተብሎ ለሕዝብ ቀርቧል።

ይህንን መረጃ የሰማ ማሰብ የሚችል አዕምሮ ያለው ሰው የሚጠይቀው የመጀመሪያ ጥያቄ “የሠራዊቱ ስብጥር በተገለፀበት ዓይነት የመኮንኖቹም ስብጥር ለምን አልተገለፀም?” የሚል ነው። ይህ ጥያቄ በአስተዋይ ሰው አዕምሮ ውስጥ በተነሳነበት ፍጥነት ምላሽ ያገኛል፤ ምክንያቱም ምላሹ እዚያው እቁጥሮቹ ውስጥ አለ። የመኮንኖቹ ስብጥር ያልተነገረበት ምክንያት አብዛኞቹ መኮንኖች በ17.47 በመቶው በመሆናቸው ነው። ወደዚህ መምደሚያ የሚደርሰው አሳቢው ስለፈለገው ሳይሆን የመረጃው አቀራረብ አመክኖ (ሎጂክ) ወደዚያ ስለሚገፋ ነው። በዚህም ምክንያት በሲራጅ ፈርጌሳ አንባቢነት የቀረበው የህወሓት ሪፓርት በገዛ ራሱ ላይ ነው የተኮሰውም።

እኛ እንደ ሲራጅ ፈርጌሳ የዘር ስታትስቲክስ ውስጥ አንገባም፤ መልዕክታችን ለተገፋውና እየተበደለ ላለው ለመላው የሠራዊቱ አባል ነው።

ይድረስ ሹመትና ኃላፊነት ተነፈገህ፤ የጥቂቶቹን ሀብትና ዝና ጠባቂ እንድትሆን ለተፈረደብህ ወገናችን!!! እስከመቼ ለህወሓትና ጥቂት አጎብዳጅ መኮንኖች ባርነት ትገዛለህ? ይህ ውርደትህ የሚያበቃው መቼ ነው? የታጠቀው መሣሪያ የአገርህና የራስህ ክብር ማስጠበቂያ፤ ነፃነትህን መጎናፀፊያ የምታደርገው መቼ ነው? ለመሆኑ ለመኮንንነት የሚያበቃ ጭንቅላት፣ ልምድ ወይም እውቀት ከፓርቲ አባልነት ነው የሚገኘው? ህወሓቶችና አጋሮቻቸው በሠራዊቱ ያሉትን ቁልፍ ኃላፊነቶችን ሁሉ ጠቅልለው ይዘው “ጀሌዎቻችን እንዲሆኑ ፈቅደንላቸዋል” የሚል ሪፓርት የሚያቀርቡት ምንኛ ቢንቁን ነው? ይህንን ውርደት ኢትዮጵያዊው ወኔህ እንዴት ይቀበለዋል?

ኢትዮጵያዊው ወታደር ከሌላው ኢትዮጵያዊ በባሰ በአምባገነንና ዘረኛ አለቆቹ እየተዋረደ እንደሆነ በገሃድ የሚታይ ጉዳይ ነው። የህወሓት አባላት ቁልፍ የስልጣን ቦታዎችን ይዘው ጦር ሠራዊቱን እንደ ፓርቲ መዋቅር ሲመሩት ማየት የሠራዊቱን አባላት ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ኢትዮጵያዊ የሚያንገበግብ ጉዳይ ነው። ሠራዊቱ አገርና ሕዝብን ሊጠብቅበት ይገባ የነገረው መሣሪያ በንጹሃን ዜጎች ላይ እንዲያነሳ፤ ሰላማዊ ሰዎችን እንዲደበድብ፣ እንዲረግጥና እንዲገድል የሚያዙት እነዚህ የህወሓትና ጥቂት አጎብዳጅ አለቆቹ እንደሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያውቃል። ሆኖም የኢትዮጵያ ወታደር የታዘዘው ሁሉ የሚፈጽም ባርያ አይደለምና በእነዚህ ጥቂት ዘረኛ አለቆችህ ላይ እንዲነሳ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይጠይቃል።

ውድ የኢትዮጵያ ወታደር ሆይ!!! “ዘረኛነት በቃኝ” በል። ለነፃነት፤ ለእኩልነት፤ ለአገር ክብር በሚታገሉ ወገኖችህ ላይ ክንድህን አታንሳ። የጥቂት ዘረኞችን ሥልጣን በማራዘም ከሚመካብክ የኢትዮጵያ ድሃ ሕዝብ ጋር ዘላቂ ቂም ውስጥ አትግባ። በትእቢት “ሁልሽንም ረግጠን እንገዛለን” ብለው የሚፎክሩት አንተን ከወገንህ ጋር ደም በማቃባት ነውና “እምቢ!” በላቸው። ለዘረኞች ስልጣን ብለህ አትሙት! እንዲያውም ለገዛ ራስህ ክብር፣ ለቤተሰቦችህና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ግንባር ቀደም አርበኛ ሁን።

ከላይ የተባለው ለፓሊስ አባላትም ይሠራል። በህወሓትና ህወሓት በየቦታው በፈጠራቸው ጀሌዎች የሚመራ በመሆኑ ከሕዝብ ፍላጎት በተፃፃሪ የቆመ ይምሰል እንጂ የኢትዮጵያ ፓሊስ የሕዝብ ወገን እንደሆነ በተለያዩ አጋጣሚዎች የታየ ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍትህ እጦት የሚሰቃየውን ያህል ብዙሃኑ ፓሊስ በፍትህ እጦት እየተሰቃየ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ የኑሮ ጫና እንዳዳከመው ሁሉ የኢትዮጵያ ፓሊስም ኑሮ ከብዶታል። እንደሌላው ሰው ሁሉ ፓሊስንም ዘረኝነት አስመርሮታል። ብዙሃኑ ፓሊስ አቅሙን በጥቂት አምባገነን አለቆቹ ላይ የሚፈትሽበት ጊዜ ደርሷል።

የስለላ ተቋማቱ ጉዳይ ለየት ይላል። “ደህንነት” ተብሎ በሚሞካሸው የጆሮጠቢዎች ስብስብ በሆነው መሥሪያቤት እና በኤክትሮኒክስ ብርበራ የተሠማሩ “ባለሙያ ጆሮ ጠቢዎች” ውስጥ ህወሓት በአለቃነትም በምንዝርነትም አብዛኛውን ቦታ ይዟል። ሆኖም እዚህም የሕዝብ ወገኖች እንዳሉ ይታወቃሉ። በእነዚህ ቦታዎች ያላችሁ የሕዝብ ወገኖች ሲቻል በገሃድ ሳይቻል በሚስጥር ተቋማቱን የማዳከም ሥራችዎችን መሥራት የህሊናና የዜግነት ግዴታችሁ ነው። ከእናንተ ብዙ፤ እጅግ ብዙ ይጠበቃል። የምታሾልኳት ትንሿ መረጃ የብዙዎችን ሕይወት ልትታደግ ትችላለች፡

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በህወሓት የጦር፣ የፓሊስና የስለላ መዋቅሮች ውስጥ የሕዝብ ወገኖች እንዳሉ ያውቃል። እነዚህ ወገኖቻችን እንደሌላው ሕዝብ ሁሉ – አንዳንዴም ከሌላው በባሰ ሁኔታ – በፍትህ እጦት፣ በኑሮ መክበድና በዘረኝነት እየተሰቃዩ መሆናቸው ያውቃል። እነዚህ ወገኖቻችን ጥለው እንዲወጡ፤ ይህ ካልተቻለም ከውስጥ ሆነው የወያኔን የጦር፣ የፓሊስና የስለላ መዋቅሮች እንዲያፈራርሱ ጥሪ ያደርጋል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!





Tuesday, April 15, 2014

የሶማሊ ክልል ፕሬዚዳንት ከስልጣን የምነሳ ከሆነ ክልሉ የራሱን እድል በራሱ ይወስናል አሉ

ሚያዚያ ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢህአዴግ ምክር ቤት በሶማሊ ክልል የሚፈጸመው ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት በክልሉ ያሉትን ባለስልጣኖች ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ የኢህአዴግን ባለስልጣኖችን በአለማቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት የሚያስጠይቅ መሆኑን ድምዳሜ ላይ የደረሰው ኢህአዴግ፣  ፕሬዚዳንት አብዲ ሞሃመድ ኡመርን ለማውረድ እንቅስቃሴ መጀመሩ  ፕሬዚዳንቱ ይህንን ንግግር እንዲናገሩ እንዳደረጋቸው ምንጮች ገልጸዋል።
አቶ አብዲ   የእርሳቸው ታማኝ ደጋፊ የሆኑ በውጭ አገራት የሚኖሩ የክልሉን ተወላጆች ጅጅጋ ውስጥ በሰበሰቡበት ወቅት ፣ እርሳቸው ከስልጣን የሚወርዱ ከሆነ፣ ክልሉ የእራስን እድል በራስ የመወሰን መብት እስከመገንጠል የሚለውን የህገመንግስት አንቀጽ ተግባራዊ እንደሚያደርግ ዝተዋል። ኢህአዴግ አንዳንድ እጃቸውን ከሰጡና በሃይል ታፍነው ከተወሰዱ የቀድሞ የኦብነግ አመራሮች ጋር የጀመረው ቅርርብ አቶ አብዲን አላስደሰተም።
አቶ አብዲ በእርሳቸውና በተወሰኑ የህወሃት ጄኔራሎች የሚመራ   ልዩ ሚሊሺያ የሚባል ሰራዊት  መቋቋማቸው ይታወቃል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ታላቁዋን ሶማሊያን ለመመስረት አላማ ይዞ ሲንቀሳቀስ ለነበረው ሙሀመድ አብዱላህ ሃሰን በጅጅጋ ከተማ የተሰራው ሃውልት ተመርቋል። በቅኝ ግዛት ዘመን ለታላቁዋ ሶማሊያ መመስረት ሲታገል የነበረው ሙሀመድ ሃሰን ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ተከታታይ ጦርነት አድርጎ ነበር።
የክልሉ መንግስት የኢትዮጵያን አንድነት የማይፈልገውንና ለታላቁዋ ሶማሊያ መመስረት ሲታገል ለነበረው ሰው ሃውልት ማቆሙ ብዙዎችን ያስገረመ ክስተት ሆኗል። ሙሃመድ ሃሳን በሞቃዲሾ ከተማም  እንዲሁ ታላቅ ሃውልት ተገንብቶለታል።

ኢህአዴግ የ2007 ምርጫ ማሸነፊያ ስትራቴጂዎችን አወጣ

ሚያዚያ ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከኢህአዴግ የውስጥ ምንጮች ለኢሳት የተላከው የ2007 ዓም ምርጫ ማስፈጸሚያ እቅድ እንደሚያሳየው ለአርሶ አደሩ የማዳበሪያ እዳ እፎይታ በ2006/2007 የመኸር ምርት ዘመን የሚሰጥ ሲሆን፣ ለከተማ ነዋሪዎች ደግሞ  በ20 ሺ ብር ቅድመ ክፍያ ለመኖሪያ ቤት ግንባታ የሚውሉ ቦታዎችን ይሰጣል።
20 ሺ ብር የቅድመ ክፍያ ገንዘብ ለማቅረብ ለማይችሉት የከተማ ነዋሪዎች  የምርጫ ቅስቀሳ በሚካሄድባቸው ወራት ከባንክ በብድር ገንዘቡን ለመልቀቅ  እቅድ አውጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጿል፡፡ የቦታ መስጠት ሂደቱን በመላ ሃገሪቱ ተግባራዊ ለማድረግ የቦታ መረጣ አዘጋጅቶ መጨረሱንም ገልጿል፡፡
ኢህአዴግ የማሸነፊያ ስትራቴጂዎች በሚል ርእስ ከዘረዘራቸው ተግባራት መካከል “  አርሶ አደሩንና አመራሩን የመዳበሪያ እዳ እፎይታ በ2006/2007 የመኽር ምርት ዘመን እንዳለ መንገር፤ ተቃዋሚችን ማንኳሰስ፣ በኢህአዴግ ላይ ሊነሱ የሚያስቡትን እስከ ማግለል እንዲደርስ ማሰረዳት፣ ምርጫውን በ1 ለ 5 እንዴት ድምፅ እንደሚሰጡ ማስረዳት /በሙከራ ማሳየት፣ ያለውን የፍትህ እና የልማት ችግር ወደ ፊት እንደሚፈታ በተስፋ መሙላት” የሚሉት ተጠቅሰዋል።
ኢህአዴግ ባዘጋጀው የስትራቴጂ ወረቀት ላይ ” የኢህአዴግ ትምህርት እና ስልጠና ከአመቱ መጀመሪያ ጀምሮ ህዝቡን ለመቀየር ቅርብ ናቸው  ለተባሉ አርሶ አደሮች እና የቀበሌ አመራሮችን ‹‹ የኢህአዴግ ታሪክ››፤ የኢህአዴግ የልማት ስልቶች ፤ የብሄርተኝነት ግንባታ፤ የሃገራችን የምርጫ ተሞክሮ፤” በሚሉት ርእሰ ጉዳዮች ላይ የሰጠው ስልጠና መሳካቱን ይዳስሳል።
የአማራ እና የኦሮምያ ክልሎችን ማመን እንደማይቻል የሚገልጸው ሰነዱ፣  ”አመራሩ  ኢህአዴግ ከወደቀ እስር ቤት እንደሚገባ ፤ የሚመጣው መንግስት አሁን በስልጣን ላይ ያሉትን የአመራር አካላት ቤተሰብም ጭምር ህይወት የሚያመሳቅል መሆኑን በማስረዳት፣’ ኢህአዴግ ወይም ሞት’ ብሎ በመነሳት ሊያሰፈፅም እንደሚገባው ያትታል።
የስራ መመሪያው ለከፍተኛ ጀማሪ አመራሮች በአስኳይ መውረዱን ለማወቅ ተችሎአል። የምርጫ ማስፈጸሚያ እቅድ ስልጠና የወረዳ እቅድ ከቀረበ በኋላ ተገምግሞ ሲያልቅ በዚህ መሰረት ቀበሌዎች ምርጫዎችን እንዴት ማሸነፍ እንደሚችሉ የቀበሌ እቅድ እንደሚያዘጋጁም ተገልጿል።
ለታችኛው አመራር ስልጠና የሚያገለግሉ መልእክቶች ተብለው ከተዘረዘሩት መካከል ” ምርጫ 2007 የኢህአዴግ አሸናፊነት ይረጋገጣል ፣“ታላቁ መሪያችን ያስቀመጠልንን አደራ እናስቀጥላለን “፣ “በገጠር ቀበሌዎች የልማት ፣ የዴሞክሲና የመልካም  አስተዳደር ግቦቻችን  በዘላቂነት ለማሳካት እንረባረባለን ፣ ፈጣን  ልማት መልካም  አስተዳደርና  የህዝብ ተጠቃሚነት ተልእኮን  የተገነዘበ ንቁ  የቀበሌ አመራር  የመፍጠር ተልእኳችን ይሳካል ፣  ለአብዮታዊ  ዴሞክራሲ መስመራችን  አስተማማኝ  ደረጃ  መድረስ ብቁ የቀበሌ አመራር የመፍጠር ትግላችን ተጠናክሮ ይቀጥላል  ፣  መጭው ጊዜ ከኢህአዴግ ጋር ብሩህ ነው“ የሚሉት ይገኙበታል።
ከኢህአዴግ የውስጥ ምንጮች ለመረዳት እንደተቻለው ደግሞ ኢህአዴግ የራሱን አባሎች በተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ አስርጎ በማስገባት  በተቃዋሚ ስም አሸንፈው እንዲወጡ ለማድረግ እየሰራ ነው።

Monday, April 14, 2014

አንድ ባርያ ነጻ የሚወጣው መቼ ነው? ሲፈቅድ ነው? ወይስ ሲፈቀድለት? (ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም)

April 14, 2014

በአለፈው ሳምንት (ፋክት ቁጥር 36) ወይዘሮ መስከረም የተለያዩ መጻሕፍትን በመጥቀስ በሴቶች ላይ ያለውን መጥፎ ጫና በደንብ ያስመሰከረች ይመስለኛል፤ ግን እኮ በሴቶች ላይ ያለው ጫና የቆየ፣ ክፉና ጎጂ መሆኑን ማንም ያውቀዋል፤ ቁም-ነገሩ ያለው ከዚያ የባህል ጭነት በራስ ጥረት ወጥቶ፣ ነቀፌታንም ሆነ እርማትን ለመቀበል ሳይፈሩና ሳያፍሩ እንደመስከረም በአደባባይ ሀሳብን በመግለጽ በአገርና በወገን ጉዳይ መሳተፍና ሌሎችም እንዲሳተፉ የተቻለን ሁሉ ማድረጉ ላይ ነው፤ ለዚህ ነው ይህንን መልስ የምጽፈው፤ ወይዘሮ መስከረም በአጋጠሟትና በምታያቸው እንቅፋቶች ላይ ማተኮርዋ እንደርስዋ መንፈሳዊ ወኔው የሌላቸውን ያስፈራራቸዋል እንጂ አያበረታታቸውም፤ የማንንም አፍአዊ ጫና ተቋቁመው በራሳቸው የውስጥ ኃይል እንዲመሩ እናድርግ።

አንድ መጽሐፍን በመጥቀስ ወይዘሮ መስከረም የሚከተለውን ጽፋለች፡–

ፈጣሪ የሠራውን ውጫዊ ገጽታን ማሽሞንሞን በቂ እንደሆነ ሲነገራት የኖረች ሴት፣ በምን ተነሳሺነት አእምሮዋን የሚመግብ እውቀት ልትሻ ትችላለች? … በልጅነት እውቀትን ወደመሻት ያልተገፋ ማንነት በጉብዝና ወራት አላዋቂ በመሆን ቢወቀስ ትርጉም አይኖረውም፤ …››

ወይዘሮ መስከረም ሔዋን ሲነገራት የማትሰማ የመጀመሪያዋ ሰው (ልብ በሉ ሴት አላልሁም፤) መሆንዋን እንዴት እስከዛሬ ሳታውቅ ቀረች? ባለመጽሐፉም ይሁን መስከረም የሔዋንን ታሪክ ሳያነሡ መቅረታቸው መሠረታዊ ስሕተት ነው፤ በተጠቀሱት ሁለት ዓረፍተ ነገሮች ውስጥ አንድም እውነትን የሚመስል ነገር የለም፤ መስከረም ‹‹የሔዋን ዘር›› ከማለት በፊት የሔዋንን ሥራ ቆም ብላ ብታስታውስ የጠቀሰችውን መጽሐፍ እኔ እንደምነቅፈው ትነቅፈው ነበር፤ የሔዋን ታሪክ የሚነግረን የሚከተለውን ነው፡ ‹‹ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደሆነ ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ፣ ለጥበብም መልካም እንደሆነ አየች፤ ከፍሬውም ወሰደችና በላች፤ ለባልዋም ደግሞ ሰጠችው፤ እርሱም ከእርስዋ ጋር በላ፤ የሁለቱም ዓይኖች ተከፈቱ፤›› ዘፍ. 3

የሁለቱም ዓይኖች ተከፈቱ ማለት ‹‹እንደእግዚአብሔር መልካምንና ክፉን የሚያውቁ›› ሆኑ ማለት ነው፤ አሁንም ሔዋን መስከረምና ባለመጽሐፉ እንዳቀለሏት አለመሆንዋን መረዳት ይቻል ነበር፤ እንዲያውም ከዚህ በፊት እንደጻፍሁት ሔዋን የመጀመሪያዋ አብዮተኛና የነጻነት እናት ነች ለማለት ይቻላል! በአንጻሩ አዳም የፍርሃት አባት ነው፤ ‹‹ራቁቴን ስለሆንሁ ፈራሁ፤›› ያለው እሱ ነው! ስለዚህ ወይዘሮ መስከረም ‹‹የሔዋን ዘር›› የምትለውን በድላለችና ይቅርታ መጠየቅ ሳያስፈልጋት አይቀርም!

ሔዋን የተጠቀመችው ውጫዊ ገጽታን የሚያሽሞነሙን ሳይሆን የውስጥን የመንፈስ ኃይል ቆፍሮ በማውጣት ነበር፤ በዚህ የውስጥ ኃይል ለሚጠቀም ከውጭ ግፊት አይጠብቅም።

‹‹እውቀትን ወደመሻት ያልተገፋ ማንነት›› አይወቀስም፤ ትላለች ወይዘሮ መስከረም፤ እየተገፉ የሚገኘው ባርነት ነው፤ እውቀት የሚገኘው በነጻነት ነው፤ መገፋት ከእውቀት ያርቃል እንጂ ወደእውቀት አያስቀርብም፤ የመስከረም ዋናው መልእክት ሰላቢውን እንጂ ሰለባውን አትውቀስ የሚል ነው፣ ወይም የኔ ሀሳብ አህያውን ፈርቶ ዳውላውን ዓይነት ሆኖባታል፤ ለመሆኑ ሰለባ የሚሆን ከሌለ ሰላቢ ይኖራል ወይ? ሰለባ ከመሆን በፊት ሰለባ ላለመሆን መጣር አንዱ የኑሮ ዓላማ አይሆንም ወይ? ከዚህ በፊት ስለጨቋኝና ተጨቋኝ ደጋግሜ ጽፌ ነበር፤ ጭቆና የጨቋኙ ባሕርይ የሚሆነውን ያህል የተጨቋኙም ባሕርይ ይሆናል፤ ለጨቋኙ ጭቆና የሚጠቅመውን ያህል ለተጨቋኙም ጭቆና ይጠቅመዋል፤ ለጨቋኙ ጭቆና የኑሮው መሠረት የሆነውን ያህል ለሚርመሰመሱት የጨቋኝ ሎሌዎች ጭቆና የኑሮ መሠረታቸው ነው፤ እንዲህ እያለ ወርዶ ወርዶ የጭቆና ጠቃሚነት ለሎሌው ሎሌ፣ ለሎሌው ሎሌ ሎሌ … በኢትዮጵያ ምናልባትም የመጨረሻዋ የጭቆና ሰለባ ሚስት ትሆናለች፤ ወይም ልጆች ይሆናሉ! ጨቋኝና ተጨቋኝ የባሕርይ ቁርኝት አላቸው፤ አንዱ ያላንዱ አይኖርም፤ ወይዘሮ መስከረም ይህ እውነት ያልሆነበት ሁኔታ ወይም አጋጣሚ የምታውቀው ካለ ብታጋራን ደስ ይለኛል፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሙታናቸውንም እንዲቀብሩ ሙታንን ተዋቸው፤›› የሚለው ኢየሱስ ክርስቶስ የሞቱትንና በቁማቸው የሞቱትን ሲያመሳስላቸው ነው! ለእኔ የሚታየኝ እንዲህ ነው።

መስከረም ብዙ ታላላቅ ሴቶችን ጠቅሳለች፤ በእስዋ ግምት ሁሉም በአባታቸው ወይም በባላቸው እየተገፉ ወደትልቅነት መድረኩ የወጡ ናቸው፤ አዙራ ብታየው የጠቀሰቻቸውን ሴቶች ገፉ የምትላቸው ወንዶች መጀመሪያውኑ በሴቶቹ ተገፍተው እንደነበረስ ሊታሰብ አይገባም? ምናልባት ከጠቀሰቻቸው ሴቶች ይልቅ መስከረም የሄለን ኬለርን ታሪክ ብታስታውስ ኖሮ መገፋትን አታነሣም ነበር፤ ሄለን ኬለር በሕጻንነትዋ ዓይኖችዋም ጆሮዎችዋም ሥራቸውን አቆሙ፤ የሄለን ኬለር የመንፈስ ጥንካሬ ከውስጥዋ አዲስና የተሻሉ ዓይኖችንና ጆሮዎችን እንድታበቅልና እንድትማር፣ ከታወቀ ዩኒቨርሲቲም የመጀመሪያዋ ሴት ምሩቅ ለመሆን እንድትበቃ አድርጓታል፤ ይህች አስደናቂ ሴት ከመቶ ሠላሳ ዓመታት ግድም በፊት ማኅበረሰቡ በሴቶች ላይ የነበረውን አጥር ሰብራ፣ ዓይኖችዋ ባለማየታቸውና ጆሮዎችዋ ባለመስማታቸው የገጠማትን እክል አሸንፋ ራስዋን ከወንዶች በላይ ለማድረግ በቅታለች።

መገፋትን የሚፈልግ ሁሉ፣ ካልገፉት የማይነቃነቅ ሁሉ፣ ሬትን ሲግቱት ይጣፍጣል እያለ የተቀበለ ሁሉ፣ ዶሮ ማታ፣ ዶሮ ማታ፣ እያሉ አታልለው እንኳን ዶሮ የለም ሹሮ ሲሉት የማይናደድ ሁሉ፣ ምኞቱ ልደግ ልመንደግ እያለ ሲነዘንዘው በአፈና ጭጭ የሚል ሁሉ ለወቀሳ ብቻ አይደለም ለውርደትም ክፍት ነው፤ ስለዚህም ተወቅሶ ከውርደት ከዳነ ወቀሳው ትልቅ አስተዋጽኦ ያደርጋል ማለት ነው፤ ዞሮ ዞሮ የሰው ልጆች ሁሉ — ሴት፣ ወንድ፣ ወጣት ሽማግሌ-አሮጊት፣ ባለሥልጣን ተራ፣ ገበሬ ነጋዴ፣ ወታደር ፖሊስ፣ አስተማሪ አስተዳዳሪ፣ ዳኛ ጠበቃ፣ ሀኪም መሀንዲስ፣ … — የፈለገውን ቢሆን ላለበት ሁኔታ ኃላፊነቱ የራሱና የግሉ ነው፤ ራሱን የሚገነባው ወይም ራሱን የሚንደው ራሱ ነው፤ ሰበብ እየፈለጉ ከዚህ ኃላፊነት መውጣት ቀላል ቢመስልም ተመልሶ እምቦጭ ነው፤ ዳገቱን ለመውጣት የሚመረውን እውነት መቀበል ያሻል።

በመጨረሻም በማናቸውም መንገድ፣ በማናቸውም ጊዜ፣ በየትኛውም ቦታ ወደቁልቁለት የሚገፉትን ወይም የሚነዱትን ‹‹እምቢ!›› ብሎ ድምጹን ያላሰማ ገደል ገብቶ ሲንፈራፈር ከራሱ በቀር የሚወቅሰው የለም፤ አቅመ-ቢስነት ከውጭ አይመጣም።

የኢትዮጵያን ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ እና የዲያስፖራውን ሚና በተመለከተ በኖርዌይ ኦስሎ ሕዝባዊ ውይይት ተካሄደ

Ginbot7 meeting in Norway
በዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ  የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ አዘጋጅነት አፕሪል ቅዳሜ 12/2014  በኖርዌይ ኦስሎ ከተማ  የኢትዮጵያን ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ እና የዲያስፖራውን ተሳትፎ በተመለከተ ታላቅ ሕዝባዊ ስብሰባ ተካሄደ:: በሕዝባዊ ስብሰባው ላይ ቁጥራቸው ወደ ሁለት መቶ የሚጠጉ በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች ከኦስሎ እና ከተለያየ ከተማ በመምጣት በስብሰባው ላይ የተገኙ ሲሆን  የግንቦት 7 የፍትህ የነፃነት እና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር አባል አቶ ቡዙነህ ፅጌ የስብሰባው ተጋባዥ እንግዳ በመሆን ሰፋ ያለ ንግግር አድርገዋል::

ሕዝባዊ ስብሠባው በኖሬጅያውያን የሰአተ አቆጣጠር ከቀኑ 15:00 እስከ ምሽቱ 21:00 ሰዓት የተካሄደ ሲሆን የዲሞክራሲያዊ ለለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ሕዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ አቢ አማረ በኢትዮጵያ ውስጥ በወያኔ አረመናዊ ስርአት በጭካኔ በግፍ ለተገደሉ እና በተለያዩ አስር ቤቶች በፖለቲካ ኣስተሳስባችው ምክንያት ያለወንጀላች የሚስቃዩ ውድ ኢትዮጵያዊን ወገኖቻችን በማስብ  በዚሁ ዘረኛ ቡድን አስቃቂ የኣካል ጉዳት ለተፈጸባቸው ኢትዮጵያዊን  የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት በማስደረግ ስብሰባውን አስጀምረውታል::

በመቀጠለም አቶ ዮሀንስ አለሙ የዴምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ሊቀመንበር የመግቢያ ንግግር ያደረጉ ሲሆን በንግግራቸው ስለ ዲምክራሲያዌ ለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ አመሰራረት እና ስለ ድጋፍ ድርጅቱ አላማ በማብራራት የድጋፍ ድርጅቱ በአሁኑ ሰአት በሀገር ቤት በሰላማዊ ትግል የወያኔን መንግስት ለመጣል እየታገሉ ያሉትን የፖለቲካ ድርጅቶችን እየረዳ እንደሚገኝ እና ከሀገር ውጭ ደግሞ የወያኔን መንግስት  በሁለገብ ትግል  ለማስወገድ እየሰራ ያለውን የግንቦት 7 የፍትህ የነፃነት እና የዲሞክራሴ ንቅናቄ የፖለቲካ ድርጅትን በግንባር ቀደምነት እየረዳ እንዳለ በመግለጽ  የወያኔን ዘረኛ ስርአት ለመጣል ሁሉም ሰው አስተዋጿ ማድረግ እንደሚጠበቅበት እና ማንኛውም  ኢትዮጵያዌ ዜጋ በሀገራችን የጋራ ጉዳይ ስለሆነው  የኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ ሀሳብ በመለዋወጥ ፣በመካከላችን ያሉትን ማንኛውንም የሃሳብ ልዩነቶች ወደ ኋላ በመጣል ፣ በመቻቻል፣ ሀገር እያፈረሰ እና ሕዝብ እያዋረደ ያለውን የዘረኛውን የወያኔን መንግስት ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሁለገብ ትግል ለማስወገድ መረባረብ እንዳለበት አጽኖት ሰጥተው ንግግር አድርገዋል::



በመቀጠለም ዲምክራሲያዊ ለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ድጋፍ ከሚሰጣቸው ድርጅቶች መካከል አንዱ የግንቦት 7 የፍትህ የነፃነት እና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር አባል የሆኑት አቶ ቡዙነህ ፅጌ የስብሰባው ተጋባዥ እንግዳ ሰፊውን ጊዜ በመውሰድ ከንጉሱ ስርአት ጀምሮ በደርግ መንግስት ዘመንም በሀገራችን የተደረጉ የፖለቲካ ንቅናቄዎችንና ለውጦችን አንድ በአንድ በመዘርዘር አሁን ካለው የወያኔ ኢህአዲግ መንግስት ጋር በማነጻጸር ሰፋ ያለ ትንታኔ ያቀረቡ ሲሆን አሁን ላይ ሀገሪቱን እየመራው ነው የሚለው የወያኔ መንግስት ከዚህ ቀድሞ ኢትዮጵያን ከመሩት ከሁለቱ መንግስታቶች ማለትም ከንጉሱም ከደርግም መንግስት ጋር ሲነጻጸር ፈጽሞ እንደማይገናኝ የወያኔ መንግስት ዘረኛና የዘረኝነት ፖለቲካ እያራመደ ያለ አረመናዊ መንግስት እንደሆነ አብራርተዋል::

የግንቦት 7  የፍትህ የነፃነት እና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር አባል አቶ ቡዙነህ ፅጌ አክለውም ከወያኔ በፊት የነበሩ ሁለቱ መንግስታቶች ለውድቀት የዳረጓቸውን ምክንያቶች በመጥቀስ የወያኔን አንባ ገነናዊ መንግስት ለአፋጣኝ ውድቀት ሊዳርጉት ይችላሉ የሚሉትን ግልጽ ምክንያቶች በመዘርዘር አስቀምጠዋል:: አቶ ቡዙነህ በሁለት የኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በማንሳት እና በማብራራ ከሕዝብ ውይይት እንዲያደርጉበት ለመወያያ ያቀረቡ ሲሆን እነዚህም:

1, በሙስሊሙ ማህበረሰብ እና በወያኔ መካከል ያለው ግጭት

2, የህዳሴ ግድብን  በማስመልከት ያለው ተቃውሞ

ስለሙስሊሙ ማህበረሰብ ተቃውሞ ሲናገሩ የሙስሊሙ ትግል በሁለት አመታት ውስጥ የተደረገው ሰላማዊ ትግል በጣም የተሳካና ወያኔ በቀላሉ ሊያዳፍነው ያልቻለው ሰላማዊ መብትን የመጠየቅ ትግል እንደሚያደንቁ በመናገር ነገር ይህ በሙስሊም ማህበረሰብ በኩል እየተደረገ ያለው ትግል እስከ አሁን ድረስ ከመንግስት በኩል ምንም አይነት መልስ ሊያገኝ እንዳልቻለ እና ወደፊትም ከወያኔ መንግስት በኩል ምንም አይነት መልስ ያገኛል የሚል እምነት እንደሌላቸው ተናግረዋል:: ለዚህም ማስረጃው የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ከጠየቋቸው አራት የመብት ጥያቄዎች አንዱም ካለመመለሱ በተጨማሪ እስካሁን መሪዎቻቸውም በሃሰት ውንጀላ በእስር እየማቀቁ ያለፍርድ እየተንገላቱ መሆናቸው ነው::

ነገር ገን አሁን እየሆነው ባለው ሁኔታ በእንደዚህ አይነት መንገድ እስከመቼ ድረስ የሙስሌሙ ትግል ይቀጥላል በማለት የተናገሩ ሲሆን አሁን እየሄደ ባለው አካሄድ የሙስሊሙ ተቃውሞ የትግል አቅጣጫውን እስካልቀየረ ድረስ ረጅም ርቀትን ትግሉ ሊቀጥል ይችላል የሚል እምነት እንደሌላቸው እና ነግር ግን የሙስሊሙ ጥያቄ ከእምነት መብት ጥያቄ ባሻገር ወደ የዜግነትን መብት ወደ ማስከበር መለወጥና መሸጋገር  እናደለበት በመናገር የሙስሊሙ ማእበረሰብ ጥያቄ ፍሬ ሊያፈራ የሚችለው  ትግሉ በዚህ መልኩ ሲቀጥል እንደሆነ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ሰተዋል::

በሁለተኛም የህዳሴ ግድብ በሚመለከት  ያቀረቡት ሀሳብ ወያኔ የራሱን የፖለቲካ ኪሳራና በህዝቡ ላይ እያደረሰ ያለዉን ግፍ በዕድገት ስም ለመሸፈን ያመጣዉ እንጂ ታቅዶበትና ለህዝቡ በማሰብ እንዳልሆነ በኢትዮጵያና በህዝቡ ላይ እያደረሰ ያለዉ ግፍ እንደ ማስረጃነት በማቅረብ ያብራሩ ሲሆን እንደ ምሳሌም ወያኔ ሃገራዊ የሆነ አላማ ይዞ ካለመነሳቱ አንፃር የሃገርን ድንበር አሳልፎ እስከመስጠት እየሄደ ያለበትን ሁኔታ ጠቅሰው ይህ አሰራር ደግሞ የዲክታተሮች ባህሪ እንደሆነ አብራርተዋል::

የወያኔ መንግስት በህዳሴ ግድብ ሰበብ ምክንያት በማድረግ በመላው አለም ኢትዮጵያኖች በሚኖሩበት ሀገሮች በመዞር የዲያስፖራውን ቀልብ ለመውሰድ የሚያደርገው የአባይ ቦንድ ሽያጭ ሩጫ በዲያስፖራ ተቃዋሚዎች አማካኝነት በፍጹም እንዳልተሳካለት ይህንንም የወያኔ በአባይ ቦንድ ሽያጭ ስም ገንዘብ ዘረፋ በመቃወም ወያኔን አሳፍረው ከመለሱት መካከል በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያኖች እንደሆኑ በማስታወስ  የዚህ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ሰበብ የወያኔን መንግስት ወደ መጥፎ ውድቀት ላይ ሊጥለው እንደሚችል በማመን የወያኔ መንግስት በአሁን ሰአት ከግብጽ መንግስት ጋር እየገባ ያለው ሰጣ ገባ ለኢትዮጵያ መጥፎ ሊሆን እንደሚችል በመግለጽ ንግግራቸውን አጠቃለዋል::

በመቀጠልም አቶ ብዙነህ ባነሷቸው ነጥቦችና እና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ ከስብሰባው ተሳታፊዎች ለቀረበላቸው በርካታ ጥያቄዎች ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን ሰፋ ያለ ውይይትም ተደርጓል፥፥ ከውይይቱም በማስቀጠል የዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ዳንሄል አበበ የዲምክራሲያዌ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ የአቋም መግለጫ ንግግር ያደረጉ ሲሆን ድርጅታቸው ወያኔ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍና በደል ፈጽመው እንደሚያወግዙ እና ዴምክራሲያዌ ለለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ሁል ጊዜ ከግንቦት 7 የፍትህ የነፃነት እና የዲሞክራሴ ንቅናቄ ጎን እንደሚቆም ቃል በመግባት የአቶ ቡዙነህ ፅጌን በኖርዌይ በመገኛት ለህዝቡ ለሰጡት ገለጻ አመስግነዋል::

በዝግጅቱ መጀመሪያና ማጠቃለያ ላይ የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል መዝሙር በመዘምራን የተዘመረ ሲሆን በየጣልቃው የተለያዩ የባህል ዘፈኖች በተወዛዋዦች ታጅቦ የቀረበ ሲሆን ጣእም ያለው ባህላዊ ምግብም በዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ የሴቶች ክፍል ተስተናግዷል፥፥ ስብሰባውን ተጀምሮ እስኪያልቅ አቶ ፍቅሬ አሰፋ መርተውታል::

በመጨረሻም የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ለዝግጅቱ መሳካት የበኩላችሁን ላበረከታችሁና ከተለያዩ የኖርዌይ ከተሞች ረዥም ርቀት በመጓዝ የዝግጅቱ ታዳሚ ለነበራችሁ ውድ ኢትዮጵያውያን እና እንዲሁም የድርጅቱ አባላቶች ታላቅ ምስጋና እናቀርባለን::

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !

የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ

Thursday, April 10, 2014

በኢትዮጵያ የመብቶች ትግሎች ሁሉ ህወሓትን ከሥልጣን ወደ ማስወገድ አቅጣጫ ያመራሉ!!!

የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ መሪዎች የክስ ሂደት በበርካታ አሳዛኝ ጉዳዮች የታጀቡ ቢሆኑም የሚሰጡት ትምህርት ግን ከፍተኛ ነው። እነዚህ ወገኖቻችን “ችሎት” በተሰኘው የአገዛዙ የድራማ መድረግ በመገኘት ፍትህን ለመግደል ካባ ለብሰው “ዳኞች” ተብለው ለተኮፈሱ የአገዛዙ ተላላኪ ካድሬዎች እና ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ያደረጓቸው ጠንከር ያሉ ንግግሮች ካድሬ “ዳኞችን” አሳፍረዋል፤ ኢትዮጵያዊያንን ግን አኩርተዋል። እኚህ ወገኖቻችን ከወያኔ ችሎት ፍትህ ይገኛል የሚል ብዥታ ባይኖራቸውም መድረኩን መልዕክት ለማስተላለፊያነት ተጠቅመውበታል። በዚሁ መድረክ በአገዛዙ እጅ ከወደቁበት ጊዜ ጀምሮ እየደረባቸው ስላለው ሰቆቃ ሲናገሩ አድማጮች ሊቆጣጥሩት የማይችሉት ሐዘንና እልህ ውስጥ እንዲገቡ አድርጓቸዋል።

ወያኔ እንዲህ ዓይነቱ ጭካኔ የሚፈጽመው በሙስሊም መሪዎች ላይ ብቻ አይደለም። የህግ እውቅና የተሰጣቸው መብቶቻቸው እንዲከበርላቸው በጠየቁ ወገኖቻችን ሁሉ ተመሳሳይ ሰቆቃ ሲፈጸም ኖሯል፤ አሁን እየተፈጸመ ነው። “ኑሮ ከበደን” ያሉ ወጣቶች ተደብድበዋል። “የእርሻ መሬት አጣን” ያሉ ገበሬዎች ከያዙት ቁራሽ መሬት ተፈናቅለዋል፣ ተግዘዋል፣ ከነልጆቻቸው ለጎዳና ኑሮ ተዳርገዋል። በሀረር እና በአዲስ አበባ ከተሞች እንደታየው “ነግደን እንኑር” ባሉ ነጋዴዎች ላይ ከአቅም በላይ ከሆነ ግብር ጀምሮ በንብረታቸው ላይ እሳት እስከመልቀቅ የደረሰ አረመኔዓዊ ድርጊት ተፈጽሟል።

በዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌ አንቀጽ 18 መሠረት እያንዳንዱ ሰው በግሉም ሆነ በጋራ የፈለገውን ሃይማኖት የመከተልና የማስተማር፤ ያልፈለገውን ደግሞ የመተው መብት አለው። ስለሆነም የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ተግባራት በዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌ እውቅና ለተሰጣቸው መብቶቻቸው መከበር ያደረጉት ትግል ነው። ለወጉ ያህል “ሕገ መንግሥት” ተብሎ በሚጠራው ኢትዮጵያዊያንን ለመክሰሻነት ብቻ በሥራ ላይ በሚወለው ሰነድ ውስጥ የተካተቱ ቢሆንም ዓለምዓቀፍ እውቅና ያገኙ መብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ተረግጠዋል። ለእነዚህ መብቶች መከበር በጽናት የቆሙ የኢትዮጵያ ውድ ልጆች ከተራ የመንደር ካድሬና ጆሮ ጠቢ እስከ እስከ ከፍተኛው እርከን ባለ ባለሥልጣኖች ተዋክበዋል፤ ሰቆቃ ተፈጽሞባቸዋል።

ሙስሊሙ ማኅበረሰብ ለእምነት መብቶቹ መከበር እስካሁን ያደረገው ተጋድሎ የሚደነቅ ነው። የተቀናጁ እንቅስቃሴዎቹ፣ ተምሳሌታዊ የተቃውሞ ምልክቶች አጠቃቀሙ የሚያበረታታ ነው። ክርስቲያኑ ከዚህ የሚማራቸው በርካታ ቁም ነገሮች አሉ።

ከሙስሊም እንቅስቃሴና ወያኔ ይህንን እንቅስቃሴ ለማፈን እየሰዳቸው ካሉ እርምጃዎች የምንረዳው አንድ ትልቅ ሐቅ የቱን ያህል ጨዋና የሰለጠነ ቢሆን ወያኔ የሕዝብ ድምጽ ለማዳመጥ ፍላጎት የሌለው መሆኑን ነው። ሙስሊም ወገኖቻችን ጥያቄዎቻቸውን በሚያስገርም ቁጥብ ሥነሥርዓት (ዲሲፕሊን) ቢያቀርቡም ከወያኔ የተሰጠው ምላሽ ግን አፈና፣ ረገጣ፣ ቶርቸር እና ከእስከዛሬዎቹ ይበልጥ አፋኝ የሆኑ ደንቦችና ድንጋጌዎችን ነው። ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ያደረጓቸው ትግሎችም እንደዚሁ ወደ ባሱ የመብት ጥሰቶች እያመሩ ነው። ከዚህ የምንማረው ነገር ትግሉ ውጤታማ እንዲሆን ስትራቴጂዎችን መፈተሽ እንደሚያስፈልግ ነው።

እንደሚታወቀው፤ ሰብዓዊ መብቶች እርስ በርሳቸው የተቆራኙ፤ እርስ በርሳቸውም የሚደጋገፉ ናቸው። አንዱ የመብት ዓይነት ሲጓደል፤ ሌላውም አብሮ ይጓደላል። ለምላሴ የመናገር መብት ተገፎ እያለ የማምለክ መብት ሊፋፋ አይችልም፤ ወይም ደግሞ ፍትሃዊ ዳኝነት የማግኘት መብት ተጥሶ እያለ የማምለክ መብትን የሚያስከብር ተቋም ሊኖር አይችልም።

ለመብቶች መከበር የሚደረጉ ትግሎች፤ በተለይም ደግሞ የሙስሊም ወገኖቻችን ትግል የደረሰበት ደረጃ በአንክሮ ሲጤን ስትራቴጂን በተመለከተ በጥልቀት ልናስብባቸው የሚገቡ በርካታ ጉዳዮች መኖራቸውን እንገነዘባለን። ለጊዜው ሁለት ነገሮች ላይ አጽንዖት ሰጥተን እናልፋለን።

ከላይ እንደተገለፀው የመብት ትግሎች ሁሉ መደጋገፍ ይኖርባቸዋል። ቀደም ሲል በባህርዳር፣ በኋላም በአዲስ አበባ በሴቶች ዓለም ዓቀፍ ቀን አሁን ደግሞ በደሴ ውስጥ እንደታየው የመብት ጥያቄዎች ሁሉ ተደጋግፈው መነሳት ይኖርባቸዋል። ይህ የመደጋገፍ ልምድ የሁለቱ ትላልቅ ሃይማኖቶች ተከታዮች ለየእምነቶቻቸው ነፃነት በሚያደርጉት ትግል ውስጥ መኖር ይኖርበታል። የሙስሊሞች የመብት ጥያቄዎች የክርስቲያኖችም፤ የክርስቲያኖች ደግሞ የሙስሊሞችም መሆን ይኖርበታል።
በሥልጣን ላይ ያለው የህወሓት አገዛዝ አንዱንም የመብት ጥያቄ መመለስ የማይችል መሆኑ ግልጽ መሆን ይኖርበታል። በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ የመብት ጥያቄዎች ግብ ወያኔን ከሥልጣን ከማባረር ያነሰ መሆን አይችሉም። ስለሆነም የመብት ማስከበር ትግል ስናካሂድ ይህን አልመን እና ለዚህም ተዘጋጅተን መሆን ይኖርበታል። ይህ ደግሞ ከፍተኛ የስነልቦና፣ የድርጅትና የስልት ዝግጅት ይጠይቃል።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ሰብዓዊ መብቶችን ለማስከበር ህወሓት ከሥልጣን መወገድ ይኖርበታል ብሎ ያምናል። ወያኔ በሥልጣን ላይ እስካለ ድረስ መገለል፣ መረገጥ፣ መጋዝ፣ መሰደድ፣ መደብደብ፣ የማይቀርልን በመሆኑ ሥቃያችንን ለመቀነስ ወያኔን ማስወገድ ይኖርብናል ብሎ ግንቦት 7 በጽኑ ያምናል። ከዚህ በተጨማሪ በተለያዩ መንገዶችና ምክንያቶች የምናደርጋቸው ትግሎች ወደ አንድ አቅጣጫ ያመራሉ ብሎ ያምናል። ትግሎቻችን ዞሮ ዞሮ ህወሓትን ከሥልጣን ወደ ማስወገድ ማምራታቸው ግልጽ ስለሆነ ለዚህ የሚያስፈልገውን ስነልቦናዊና ቁሳዊ ዝግጅቾችን እናድርግ ይላል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!



የፌደራል ፖሊስ በቦዴዎች ላይ በሰነዘረው ጥቃት ከ20 በላይ ሰዎች ሳይገደሉ እንዳልቀረ አንድ የፖለቲካ ድርጅት አስታወቀ

ሚያዚያ ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት ምክትል ሊቀመንበርና የዞኑ ሰብሳቢ አቶ አለማየሁ መኮንን ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ባለፈው አንድ ወር ውስጥ በቦዴዎችና በኮንሶች መካከል የተነሳውን ግጭት ተከትሎ የፌደራል ልዩ ሃይል በወሰደው እርምጃ ወደ 29 የሚጠጉ ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ለድርጅታቸው ሪፖርት ማድረጋቸውን ገልጸዋል።
የሟቾችን ስም ዝርዝር በማጠናቀር ላይ ሲሆኑ  ሰሞኑን ይፋ እንደሚያደርጉም ምክትል ሊቀመንበሩ ተናግረዋል ሆስፒታል ሄደው የቆሰሉትን ሰዎች መጎብኘታቸውና ማነጋገራቸውን የሚናገሩት አቶ አለማየሁ ፣ ከሁለቱ በስተቀር ሌሎች ወደ 6 የሚጠጉ ሰዎች በፌደራል ፖሊስ ጥይት መቁሰላቸውን እንደገለጹላቸው ተናግረዋል።
ምንም እንኳ የግጭቱ መነሻ መንግስት ካሰፈራቸው የኮንሶ ተወላጆች ጋር የተያያዘ ቢመስልም፣ ቦዴዎች ለሸንኮራ ገዳ ተክል በሚል ከአካባቢያቸውን እንዲነሱ መደረጉ የፈጠረባቸው ስሜት የችግሩ ዋነኛ መነሻ መሆኑን ገልጸዋል። ቦዴዎች ዘላኖች በመሆናቸው ለዛፎች ልዩ እንክብካቤ እንደሚያደርጉ የገለጹት ባለስልጣኑ፣ በእርሻ ስራ የሚተዳደሩት ሰፋሪ ኮንሶዎች ወደ አካባቢያቸው በመግባት ዛፎችን እየቆረጡ የእርሻ ማሳ ሲያስፋፉ ሲመለከቱና ለሸንኮራ ልማት በሚል ቀያቸውን እንዲለቁ ሲገደዱ የፈጠረባቸው ቁጭት ደም አፋሳሽ ወደ ሆነ ግችት ተቀይሯል።
ምንም እንኳ በሁለቱ ጎሳዎች መካከል የተነሳው ግጭት በፌደራል ፖሊስ የሃይል እርምጃ ቢቆምም፣ ውጥረቱ እንዳለ መሆኑን አቶ አለማየሁ ገልጸዋል። እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የፌደራል ፖሊስ አሁንም ድረስ በአካባቢው ይገኛል።
በጉዳዩ ዙሪያ የአካባቢውን ባለስልጣናት ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ በኔትወርክ ችግር ምክንያት ሊሳካልን አልቻለም።

Tuesday, April 8, 2014

የመረጃና ደህንነት አገልግሎት አወዛጋቢ አዋጅ ሥራ ላይ ዋለ

መጋቢት ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ባለፈው ዓመት መጨረሻ በአዲስ መልክ በአዋጅ የተቋቋመውና ዜጎች መረጃ እንዲሰጡ የሚያስገደድደው ብሔራዊ የመረጃ ደህንነት አገልግሎት አዲሱን አዋጅ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
በ1987 ዓ.ም የደህንነት የኢሚግሬሽንና ስደተኞች ጉዳይ ባለስልጣን በሚል ስያሜ ተቋቁሞ በስራ ላይ የነበረው ይህው ተቋም የተሰጠውን ተልዕኮ በአግባቡ ለመወጣት እንዲችል በሚል ባለፈው ዓመት አዲስ የማሻሻያ ረቂቅ ለፓርላማው ቀርቦ መጽደቁ ይታወሳል፡፡
አዲሱ አዋጅ ካስፈለገባቸው ምክንያቶች መካከል በዓለም አቀፍ ደረጃ በመረጃና ደህንነት ዙሪያ የስጋቶች ምንጭ እና የመከላከያ ስርዓትና አሰራር እየተለዋወጠ በመምጣቱ፣በአገር ውስጥ የጸረ ሽብርተኝነት እና የበረራ ደህንነት የማስጠበቅ የመረጃና ደህንነት ተጨማሪ ሃላፊነቶች በአገልግሎቱ ስልጣንና ሃላፊነት ውስጥ እንዲካተቱ እንደተደረገ ያገኘነው መረጃ ይጠቅሳል፡፡
በዚህ አዋጅ መሠረት በፌዴራልም ሆነ በክልሎች ደረጃ ሌላ የመረጃና ደህንነነት መ/ቤት ማቋቋም የተከለከለ ሲሆን የመ/ቤቱ ገቢና ወጪ ሂሳብ ይፋዊ በሆነ መንገድ በኦዲተር እንዳይመረመርና ሂሳብ ነክ ጉዳዮች ለጠ/ሚኒስትሩ ብቻ ሪፖርት እንደሚያደርግ ደንግጓል፡፡
ለመ/ቤቱ ከውጪ ተገዝተው የሚገቡና በተለያየ ምክንያት ለስራ ተብለው የሚወጡ ዕቃዎች ጉምሩክ ሳያያቸው እንዲወጡና እንዲገቡ የተደነገገ ሲሆን የደህንነት ሠራተኞች ሃብት ምዝገባ በጸረ ሙስና ኮምሽን ሳይሆን በተቋሙ እንደሚከናወን ይገልጻል፡፡
የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት በተጨማሪም ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት መረጃ በሚጠየቁበት ጊዜ ትብብር ያለማድረግ ሁኔታ ለሥራው እንቅፋት መሆኑን በመጥቀስ መረጃ መስጠት ግዴታ እንዲሆን በአዋጁ ደንግጓል፡፡ ይህን አዋጅ በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ ሥራ ላይ ለማዋል ተቋሙ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንና በተለይ ከመጪው ዓመት አገር አቀፍ ምርጫ ጋር ተያይዞ ሕግና ስርዓትን ለማስከበር በሚል ዜጎች መረጃ ስጡ እየተባሉ ለእንግልትና ለእስር እንዳይዳረጉ ከወዲሁ ስጋት ፈጥሮአል፡፡

Monday, April 7, 2014

በሀረር በቅርቡ ከታሰሩት መካከል አንዱ ወጣት ተገደለ

መጋቢት ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቀበሌ 10 ነዋሪ የሆነው ዳንኤል ጎሳ የተበላው ወጣት ሀኪም ወረዳ ፖሊስ ጣቢያ ከታሰረ በሁዋላ በእስር ቤት ውስጥ ከፍተኛ ድብደባ ደርሶበት መሞቱን የፖሊስ ምንጮች ገልጸዋል።
ፖሊስ በበኩሉ ወጣቱ በራሱ ቲሸርት ታንቆ መሞቱን የገለጸ ሲሆን፣ የእስር ቤት ምንጮች እንዳሉት ግን ወጣቱ ከፍተኛ ደብደባ ደርሶበት ሊሞት ተቃርቦ እንደነበር፣ ፖሊስ እጁ እንደሌለበት ለማስመሰል ቲሸርቱን አውልቆ በወጣቱ አንገት ላይ በማሰር እራሱን እንደሰቀለ አድርጎ ለቤተሰቡ ሪፖርት አድርጓል።
ወጣቱ መጋቢት 25 ቀን 2006 ዓም መቀበሩን ለማወቅ ተችሎአል። ኢሳት በእስር ቤት ውስጥ የሚፈጸሙ አሰቃቂ ድብደባዎችን በተመለከተ መዘገቡ ይታወሳል። ሶስት ነጋዴዎችም እንዲሁ ፖሊስ ጋራጅ በተባለው እስር ቤት ውስጥ ከፍተኛ ደብደባ ደርሶባቸው ራሳቸውን ስተው ነበር።
በሌላ በኩል ደግሞ ጋዜጠኛ ጀማል ዳውድ ከቀናት እስር በሁዋላ ተፈቷል። የሰብአዊ መብት ድርጅቶች እስካሁን ድረስ ወደ ስፍራው በመሄድ እስር ቤቶችን አለመጎብኘታቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

ያልዘሩትን ማጨድ ከቶ አይቻልም!!

የወያኔ መንግስት የኢትዮጵያን ብሄር ብሄረሰቦች አጋጭቶ በመካከላቸው ጥርጣሬና መፈራራት አንግሶና የታሪክ ጠባሳዎችን እንደ አዲስ በመጓጐጥ እያደማ ከፋፍሎ ለመግዛት ካለመታከት ያደረጋቸው ሙከራዎች ገና ፍሬ ባያፈሩም ቁጥቋጦዎቹ መብቀል ጀምረዋል። እዚህም እዚያም በካድሬዎች የውስጥ ለውስጥ ተልእኮ የሚለኮሱ እሳቶች መብለጭለጭ ጀምረዋል። ሌላው ቀርቶ በአንድ ብሄረሰብ መሃል ሳይቀር በከባቢ ልዩነቶች ብቻ መናቆሮችና መጋደሎች እያስተዋልን ነው። ሰሞኑን በጉጂና በቦረና ኦሮሞዎች መካከል የወያኔ ሎሌዎች በሚያበረታቱት አተካሮ የብዙ ወገኖቻችን ህይወት ጠፍቷል። ሰዎች ከኑሮአቸው ተፈናቅለዋል። ወያኔ እንደኳስ ጨዋታ ተመልካች ዳር ሆኖ ይመለከታል፣ ያጨብጭባል።

ሰሞኑን ባህርዳር ከተማ ውስጥ በተካሄደ የስፖርት ውድድር ላይ አሳፋሪ ክስተት ነበር። ለሰሚው የሚቀፍ ብልግና የተቀላቀለበት ስድብና ቁርቋሶ አይተናል። ከበስተጀርባ ሆነው ይህንን ለፍቅር ብቻ ሊውል የሚገባ የስፖርት ዝግጅት መርዝ ረጭተውበታል። ከዚህ ላቅ ያሉ የተንኮል ድግሶችም ተደግሰው ህዝብ ውስጥ በወያኔ ከተነዙ የመርዝ ቢልቃቶች ውስጥ ስራ ላይ ሳይውሉ ቀርተዋል።

Thursday, April 3, 2014

የአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ጥሰት ዙሪያ ውይይት አደረገ

መጋቢት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-” ኢትዮጵያ መረጃ የሚያወጡትና ጋዜጠኞችን ስሚ” በሚል ርእስ የአውሮፓ ህብረት ሶሻሊስቶችና ዲሞክራቶች ከአለም የጋዜጠኞች መብት ተቆርቋሪ ከሆነው ሲፒጄ ጋር በጋራ ባዘጋጁት የውይይት መድረክ ላይ በቃሊቲ እስር ቤት ከአንድ አመት በላይ ታስሮ የተለቀቀው ስዊድናዊው ጋዜጠኛ ማርቲን ሽብየና በኦጋዴን የተካሄደውን ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት የሚያጋልጥ መረጃ ይዞ የወጣው ወጣት አብዱላሂ ሁሴን፣ የአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባልና የ1997 የኢትዮጵያ ምርጫ የአውሮፓ ህበረት ታዛቢ ሃላፊ፣ የሲፒጄ ጂን ፓወል ማርቶዝ እና የሂውማን ራይትስ ወች ተወካይ የሆኑት ሌስሌ ሌፍኮው ተገኝተው በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች ዙሪያ ንግግር አድረገዋል።
ወ/ሮ አና ጎሜዝ የአውሮፓ ህብረት በኢህአዴግ መንግስት ላይ ስለሚከተለው ፖሊስ ከፍተኛ ትችት አቅርበዋል። የአውሮፓ ህብረት የአውሮፓ ተወላጆች የሆኑትን ማርቲን ሽቢየንና ዮሃን ፔርሹንን ጫና አድርገው ከቃሊቲ እንዲወጡ ሲያደርጉ፣ እስክንድር ነጋ፣ ርእዮት አለሙና ሌሎች በርካታ ዜጎች በእስር ሲማቀቁ ህብረቱ ለማስፈታት ሙከራ አለማድረጉን ተችተዋል።
ወጣት አብዱላሂ ሁሴን በድብጽ ያወጣውን ቪዲዮ ለተሳታፊዎች ያቀረበ ሲሆን፣ ሌስሊ ሌፍኮው ደግሞ ሂማን ራይትስ ወች በቅርቡ ያወጣው የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቹን ለመሰለል ስለሚጠቀምበት ዘዴ ገለጻ አድርገዋል።
በውይይቱ ላይ ኢትዮጵያውያንና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል። ወጣት አብዱላሂ ውይይቱ በወያኔ አፈና ላለው ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ የምስራች ነው ብሎአል።

በመጪው እሁድ በሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የቅስቀሳ ወረቀቶችን በመበተን ላይ የነበሩ የአንድነት ፓርቲ አባላት ታሰሩ

መጋቢት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአዲስ አበባ መስተዳደር የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃለፊ ሆኑት አቶ ያሬድ አማረ ለኢሳት እንደገለጹት ምንም እንኳ የተወሰኑ ሰዎች የታሰሩ ቢሆንም፣ ቅስቀሳው በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ሀብታሙ ታምሩ፣ አሸናፊ ጨመረዳ እና ደራሲ መቶ አለቃ አንዳርጌ መስፍን የቅስቀሳ ወረቀቶችን ሲበትኑ ተይዘው የካ ፖሊስ ጣቢያ ታስረዋል።
ለገሃር ፖሊስ ጣቢያ አካባቢ ደግሞ አክሊሉ ሰይፉና ሰለሞን ጸሃየ መጠነኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸውም አቶ ያሬድ አማረ ገልጸዋል ። ታሪኬ ኬባና ኤፍሬም ሰለሞን በተባሉትም ላይ ሲቪል ለባሽ የደህንነት ሰራተኞች ሊመቱዋቸው ሲሞክሩ ህዝቡ መብታቸው ነው በሚል ተከላክሎላቸዋል።
የአዲስ አበባ መስተዳደር የሰላማዊ ሰልፍ ክፍል አንድነት ፓርቲ ላቀረባቸው የተለያዩ አማራጭ የመሰለፊያ ቦታዎች ፈቃድ የከልከለ መሆኑን ቢገልጽም አቶ ያሬድ ግን ሰላማዊ ሰልፉ መጀመሪያ በተያያዘለት ቦታ ላይ ይካሄዳል ብለዋል
አንድነት ፓርቲ መጋቢት 28 ፣ 2006 ዓም ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ጽህፈት ቤት ተነስቶ መጨረሻውን ጠ/ሚንስትሩ ጽህፈት ቤት የሚያደርግ ሰላማዊ ሰልፍ መጥራቱ ይታወቃል።
የከተማው ህዝብ በነቂስ ወደ አደባባይ ወጥቶ ውሃ፣ መብራትና ትራንስፖርት ችግሮች እንዲቀረፉለት እንዲጠይቅ አንድነት ጥሪ ማቅረቡ ይታወቃል።
አንድነት ፓርቲ ከወር በፊት በባህርዳር ከተማ እጅግ በርካታ ህዝብ በተገኘበት የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጉ ይታወቃል። በእሁዱም ሰልፍ እንዲሁ ህዝቡ በብዛት ተገኝቶ ድምጹን እንደሚያሰማ የፓርቲው አመራሮች ተስፋቸውን እየገለጹ ነው።

የመከላከያ ሰራዊት በቦዲዮች ላይ ተኩስ ከፍቶ በርካታ ሰዎችን ማቁሰሉን ከአካባቢው የደረሰን መረጃ አመለከተ

መጋቢት ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መጋቢት 24 ቀን በቦዲዎችና በኮንሶዎች መካከል ለአንድ ወር ያክል የቆየውን ግጭት ለማብረድ በሚል ወደ አካባቢው የተጓዘው የመከላከያ ሰራዊት በቦዲዎች ላይ በመትረጊስ የታገዘ ተኩስ በመክፈቱ በርካታ ነዋሪዎች መቁሰላቸውን ከእነዚህም ውስጥ 17 አሮጊቶች፣ ህጻናትና ወጣቶች በሃና ጤና ጣቢያ በህክምና ላይ እንደሚገኙ ጂንካ የሚገኘው የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ኅብረት ጽ/ቤት ለኢሳት ገልጿል።
የመከላከያ ሰራዊቱ የወሰደውን እርምጃ ተከትሎ በሰላማጎ ወረዳ አስተዳዳሪና ምክትል አስተዳዳሪ በአንድ ወገን የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊው አቶ ስጦታው በሌላ ወገን ሆነው እየተወዛገቡ መሆኑ ታውቋል።
የኮንሶ የአገር ሽማግሌዎች በበኩላቸው ” ወደዚህ አካባቢ አምጥታችሁት ስታሰፍሩን ከህዝብ ጋር ተመካክረናል፣ ሰላም ነው ብላችሁ ቢሆንም፣ ከመጣን በሁዋላ ግን ለተደጋጋሚ ግጭት ተዳርገናል። ይህም ሆኖ ግችቶችን በጋራ በአገር ባህል መሰረት እየፈታንና እያስተናገድን ባለንበት ጊዜ ይህን አይነት አሰቃቂ እርምጃ መውሰድ ከእንግዲህ ወዲያ አብሮ ለመኖር ያለንን ተስፋ የሚያጨልመው” ነው በማለት መናገራቸውን ድርጅቱ ገልጿል።
የጽ/ቤቱ ሰራተኞች ሆስፒታል ድረስ ሄደው የቆሰሉ ኮንሶዎችና ቦዲዎችን ጎብኝተዋል።
በቦዲና ወደ አካባቢው ሄደው እንዲሰፍሩ በተደረጉት ኮንሶች መካከል በሚደርሰው ተደጋጋሚ ግጭት እስካሁን 4 ኮንሶዎችና 2 ቦዲዎች እንዲሁም አንድ ሾፌር  ተገድለዋል። 3 ኮንሶችና 1 ፖሊስ ሲቆስሉ 72 ቤቶች መቃጠላቸውን፣ ሰውናርድበጊዮ መንደር ደግሞ 1 የማዳበሪያ መጋዘን ከነማዳበሪያዎቹ መቃጠሉን ድርጅቱ በላከው መረጃ አመልክቷል።
በግጭቱ ሳቢያ ለተፈናቀሉ ኮንሶዎች እርዳታ ለማድረስና ለማከፋፈል ወደ ስፍራው ያቀናው ሾፌር ብርሃኑ ማሞ ከምሽቱ 1 ሰአት ላይ ሰውነቱን ወንዝ ዳር ቆሞ እየታጠበ ባለበት ጊዜ ማንነቱ ባልታወቀ ሰው በተተኮሰ ጥይት ተግደሎ አስከሬኑ አዋሳ ውስጥ ተልኮ ተቀብሯል።
አካባቢው አሁንም በከፍተኛ ውጥረት ውስጥ መሆኑን ድርጅቱ አክሎ ገልጿል። በጉዳዩ ዙሪያ የአካባቢውን ባለስልጣናት ለማነጋገር ያደርግነው ሙከራ አልተሳካም።

Wednesday, April 2, 2014

[በአባይ ግድብ ዙሪያ የተጻፈ አጭር ሀተታ] ትንሹዋ ወያኔና ትልቁ ወያኔ አላኖሩኝም

ለለውጥ ያህል ከራሴ ችግር ብጀምር ምን አለበት? ግለሰብ ካልኖረ ማኅበረስብ አይኖርም፡፡ ደሞም የኔ ችግር የሁሉም ፣ የሁሉም ችግር የኔ መሆኑን የማያምን አንባቢ ቢኖር ችግር አለበት ማለት ነውና በጊዜ ራሱን ፈትሾ መድሓኒት ቢጤ ቢያፈላልግ ሳይሻለው አይቀርም፡፡

ትንሹዋ ወያኔ ጠምሳኛለች፡፡ እኔን ብቻም አይደለም የጠመሰችው፡፡ ብዙዎች ኢትዮጵያውያንንም እንጂ ነው፡፡ ከወያኔ ባልተናነሰ ሁኔታ ኑሯችንን እያቃወሰችው ትገኛለች – ትልቁ ወያኔ በደጅና በቤት ውስጥ እርሷ ደግሞ በቤት ውስጥ ብቻ በተናጠልና በቡድን እየተጋገዙ ወዲያ ወዲህ ውልፊት ልንል በማይቻለን ሁኔታ ወጥረውናል፡፡ ምን እንደምናደርግም ጨንቆናአለ፡፡ ይቺ የቤት ውስጥ ወያኔ ዐይጥ ናት፡፡

ዘመኑ ለይቶለት የዐይጦችና  የወያኔዎች ሆኗል ወንድሞቼና እህቶቼ ማለትም ኢትዮጵያውያን፡፡ በኔ ቤት የተረፋት ነገር የለም፤ ለወትሮው ካልሲና ጨርቃ ጨርቅ እየለቃቀመች ነበር ወደጎሬዋ እምትወስድ፡፡ ዛሬ ግን ዘመን ተቀይሮ ባዶ ሞሰብ ሣይቀር መቆርጠም፣ አልሙኒየም የምጣድ አከንባሎ መጎርደም፣ ቁም ሣጥን መቀርጠፍ ይዛለች፤ ወያኔነት ከዚህ በላይ አለ? መጽሐፎችን አንብባ ላታነብ ነገር በጥርሶቿ መከታተፍ፣ ምግቦችን ከጉሮሮዋችን እየነጠቀች ማንከት፣ በሌሊትና አንዳንዴ ደግሞ በማንአለብኝነትና ወደር በሌለው ዕብሪት በቀንም ቤትን ተቆጣጥራ ሰላምን ማወክ የዘመናችን ትንሹዋ ወያኔ ገደቡን ያለፈ የድፍረት ተግባር ሊሆን በቅቷል – ወያኔን ተማምና መሆን አለበት መቼም፡፡ ድፍረቷ እኮ ድፍረት እንዳይመስላችሁ፡፡ ኧረረረረረ…. እንዳቃጠልሽኝ የሚያቃጥል ይዘዝብሽ፡፡ ብዙ ሰዎች በርሷ እንደተቸገሩና ዘመኑ ለርሷና ለወያኔ ዓይነቶቹ ምሥጥ መሠሪዎች የሰጠ መሆኑን ይህን ችግር የማወያያቸው ሰዎች ሁሉ ይነግሩኛል፡፡

ዛሬና አሁን በኢትዮጵያ የሰዓት አቆጣጠር ከሌሊቱ 6፡30 ገደማ ሲሆን ቀን የገዛሁትን እንትን በስምንት የጦር ግምባር አጥምጄ ወደብሶት አደባባይ መውጣቴ ነው – እንዳትሰማኝና እንዳታውቅብኝ ነው የገዛሁትን ነገር በእንትን የገለጸኩላችሁ ታዲያን – እንጂ “እዚያው በላች እዚያው ቀረች” የሚል አደገኛ መርዝ መግዛቴን ለመናገር አፍሬ እንዳይመስላችሁ፡፡ ለነገሩ ወያኔና ዐይጥ ከጠላታቸው የሚከላከሉበት ብዙ ተለዋዋጭ ዘዴ ስላላቸው በበሶ ዱዔት ያዘጋጀሁትን ግብዣ እንደሚቀበሉትና እንደማይቀበሉት አላውቅም – ውጤቱን ነገ አያለሁ፤ ዲዲቲና ወባ እንኳን ተለማምደው ጓደኛሞች መሆናቸውን ቀደም ሲል ሰምተን የለም? የሆነው ሆኖ ችግሩ ቀላል እንዳይመስላችሁ፤ ከአራት ኪሎ ቤተ መንግሥት የተለቀቁ ነው የሚመስሉት – እንደደፋርነታቸውና እንደሆዳምነታቸው፡፡ የሚምሩት ነገር እኮ የላቸውም፡፡ የሚሆንልኝ መስሎኝ “ዕቃ አትንኩብኝ፤ ቤቱ እንደሆነ ይበቃናል፡፡ ካለኝ አልፎ አልፎ ቀለብ እቆርጥላችኋለሁ – ከሌለኝ ግን ምን አደርጋለሁ? ብቻ አትተናኮሉኝ እንጂ እኔ መርዝ አላጠምድባችሁም፤ የዛሬን ኑሮ መቼም እናንተም ታውቁታላችሁ፡፡ ከመጠለቁ እግርን የሚፋጀው እሳተ መለኮቱ የቻይና ካልሲ እንኳን ባቅሙ ሠላሣና ዐርባ ብር በገባበት ወቅት እባካችሁን ተከባብረን እንኑር፡፡…” ብዬ ቃል ገብቼ በቤቴ ውስጥ የሚያደርሱትን ጉዳት ሰምቼ እንዳልሰማሁና ዐይቼም እንዳላየሁ ለብዙ ጊዜ ትቻቸው ነበር፡፡ እነሱ ግን የእንጀራ ሞሰብ አልጋችን ላይ አስቀምጠን ከባለቤቴ ጋር በየተራ እየጠበቅን እስክናድር ድረስ አሰቃዩን – የቤት ውስጥ ወያኔዎች! አሁን ባሰብኝና ቃሌን አፈረስኩ፡፡ እናም … የነሱስ አብነቱ ቀላል ነው፡፡ አለ እንጂ ወያኔ ለያዥ ለገራዥ ያስቸገረ! የወያኔስ ሰማያዊ መርዝ ካልተጨመረበት በምድራዊ መርዝ ብቻ አይጠራም፡፡ እናም ጎበዝ ግዴላችሁም ለላይኛውም በርትተን እንጩህ፡፡ የቃመ ብቻ ሣይሆን የጮኸም ተጠቀመ ሲባል ሰምቻለሁ፡፡

ወያኔና ዐይጥ አንድ ናቸው፡፡ ይሉኝታ አያውቁ፤ ፍቅር አያውቁ፤ ሀፍረትና ኅሊና እሚባል የላቸው፤ የተረገሙ ፀረ-ሕዝቦች፡፡

የሰሞኑ የወያኔ ኢቲቪ ወሬ የአባይ የህዳሴ ግድብ ብቻ ሆኗል፡፡ ነገሩ “አንድ ያላት እንቅልፍ የላት” ዓይነት ነው፡፡ በሌሎች ሀገራት በየአሥር ኪሎ ሜትሩ የሚገኝ ግድብ ኢትዮጵያ ውስጥ ብርቅ ሆኖ ጆሯችን እስኪደነቁርና እጅ እጅ እስኪለን ድረስ አባይን እየተጋትን ነው፡፡ ይህ ግድብ ከኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው ይልቅ ፖለቲካዊ ፋይዳው እንደሚያመዝን ቀድሞውንም የታወቀ ነው፡፡ ፈረንጆቹ አንድን ነገር “politicized” ሆኗል ሲሉ ያ እንዲያ ሆነ የሚሉት ነገር በፊት ለፊት ከቆመለትና ከሚወራለት ዓላማ ውጪ ለሌላ ጉዳይ ውሏል ማለታቸው ነው፡፡ የወያኔ የህዳሴ ግድብም ወያኔ እንደሚለው ለሀገሪቱ የሚሰጠው የተለዬ ጥቅም ኖሮ ሣይሆን ሕዝብን ለማዘናጊያነትና ሊጠቀስም ሣይጠቀስ ሊዘለልም ለሚችል የተለዬ ፖለቲካዊ ፍጆታ መሆኑን እናውቃለን፡፡ አለበለዚያ የስድስት ሺህ ሜጋ ዋት ኮረንቲ ከቁም ነገር ተጥፎ እስከዚህን ድረስ 24 ሰዓት ከበሮ የሚያስደልቅና ይቀምሰውና ይልሰው ያጣን ድሃ ሕዝብ ያለ ርህራሄ የሚያዘርፍ ሆኖ አይደለም፡፡ “አንቺ ቁም ነገርሽ የጎመን ወጥሽ” እንደምንል ወያኔም በዚህች ድልድይ ማነው ግድብ ዕንቅልፍ አጥቶ እኛንም እንደሱ አትተኙብኝ እያለን ነው፡፡

በማለፊያ ክርስቶሳዊ አባባል አንድ የአደባባይ ምሥጢር እንድናገር መልካም ፈቃዳችሁ ይሁንልኝ፤ “እውነት እውነት እላችኋለሁ” አባይ ተገድቦ ቢያልቅ በኔም ሆነ በሌሎች ወገኖቼ ሕይወት ላይ አንዳችም ቁሣዊም ሆነ መንፈሣዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ በምንም ዓይነት መንገድ፡፡ እርግጥ ነው – የተሟላ የቴክኒክ ዕውቀት ያለው የሰው ኃይል ካለና እንዳሁኑ በተጭበረበረ የግዢ ሂደት አማካይነት ፎርጅድና የአገልግሎት ዘመኑን ጨርሶ የተጣለ የማቴሪያል አቅርቦት ከተወገደ እንዲሁም የሕዝብ ብዛት በቁጥጥር ሥር ከዋለ ምናልባት ልክ እንዳሁኑ በመብራት ዕጦት ዳፍንት ውስጥ ላንገባ እንችል ይሆናል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን አሁንም ልክ እንዳሁኑ ሁሉ ለማይጠረቃው የመንግሥት ባለሥልጣናት ኪስ ማደለቢያና ለአነስተኛ የሀገር ገቢ ሲባል ቤት ያለው ሰው ሳይጠግብ ለዬጎረቤት ሀገር ኮረንቲ መቸብቸቡ ከቀጠለ የዚያኔም ቢሆን – አባይም ተገድቦ ማለት ነው – የመብራት ፈረቃው ላይቀርልን ይችላል፡፡ እናም በአባይ ግድብ ሳቢያ ከወያኔ ጋ ድብን ያለ ፍቅር የገባችሁ ወገኖች እውነቱን ከወዲሁ እንድትረዱት ላሳስብ እወዳለሁ፡፡ ወጥመድ ውስጥ ዘው ብላችሁ አትግቡ፡፡ ሀገር ካላችሁ ሁሉም አለና፡፡

ኢትዮጵያዊ መንግሥት ቢኖረን አንድ አይደለም አሥርና ከዚያም በላይ ትላልቅ ግድቦች ሊኖሩን የመቻላቸው ዕድል ሰፊ ነው፡፡ “ልማታዊ መንግሥታችን፤ ባለራዕዩና አባይን የደፈረ ጠቅላይ ሰይጣናችን ማነው ሚኒስትራችን” እያላችሁ ሟቹን ወያኔ የምታንቆለጳጵሱ ጥቅመኞች ሁሉ ዐይናችሁን ወደጭቁኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ አዙሩና እውነቱን ለመረዳት ሞክሩ፡፡ ወያኔ ከኢትዮጵያ ታሪክ አንጻር ዕድሜው የጤዛ ያህል ነው፡፡ በማታለልና በማጭበርበር 23 ዓመታትን መኖሩም የሚገርም ነው፡፡ ለዚህ ቆይታው ግን ተጠያቂው ወያኔ ብቻ ሣይሆን በተንሸዋረረ ልማት ስም አንጀታቸው ለወያኔ የሚንቦጫቦጭ አድር ባዮችና እበላ ባይ ሆዳሞች የሚያደርጉለት ሁለገብ እገዛም ጭምር ነው፡፡ የኛም አንድ አለመሆንና በሃሳብ መለያየት ለወያኔ ዕድሜ መርዘም የድርሻውን አበርክቷል፡፡ ሌላ ሌላውን ምክንያት እናንተም ታውቃላችሁ፡፡

ወያኔ የአባይን ግድብ ብቻ ሣይሆን ሌሎች በሃያና ሠላሣ የሚቆጠሩ ታላላቅ ግድቦችን መሥራት ይችላል፡፡ እንዴት? በየተራ እንይ፡፡

ለአንድ ጡረተኛ ፕሬዚደንት መኖሪያ ቤት የተከራዩት በወር ስንት ብር ነው? (ልብ አድርግ – ከ400 ሺ ብር በላይ ነው!) በየወሩ የተመደበው ሌላ ሌላ ጥቅማ ጥቅምስ ስንት ነው ? ይህ በራሱ ቢደማመር በዓመትና በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ – የሙስና መርዝ ካልተጠናወተው በቀር- አንድ መለስተኛ ግድብ ይሠራል፡፡ ለአንዲት ድሃ ሀገር ተጧሪ “ፕሬዚደንት” – ለዚያውም ፈርም የሚባልን ወያኔያዊ ደብዳቤ ለሚፈርም ከዘበኛ ያነሰ ሥልጣን ለነበረው ሰው – ይህን ሁሉ ወጪ መመደብ በስተጀርባው ሌላ ቤተኛን በእግረ መንገድ ለመጥቀም የተሸረበ ሤራ አለ ማለት ነው እንጂ አሳማኝነቱና ምክንያታዊነቱ በፍጹም አይተየኝም – “ራቁቱን ለተወለደ … “ ምን አነሰው ነበር እንዴ የሚባል? ይህ ነገር ራስን ያለማወቅ ችግር ወይም ስለሀገር ያለማሰብና በእልህ የሀገርን ሀብት የማባከን አዝማሚያ ይመስለኛል፡፡ እንደኢቲቪ የቁጭ በሉ አገላለጽ ሣይሆን እንደተጨባጩ እውነታ ከአጠቃላዩ ሕዝብ ከ85 በመቶ በላይ በባዶ እግሩ በሚሄድባት የድሃ ገበሬዎች ሀገር ውስጥ አንድን ተጧሪ ባለሥልጣን እንዲህ አንቀባርሮ የሚይዝ መንግሥት ደግሞ አንድ ግድብ ለመገንባት በሚል ሰበብ ከኔ ቢጤው ተራ ዜጋ – የወር ደመወዙ ከልመና ካላወጣው፣ እየሠራ ከሚደኸይና የኗሪ አኗኗሪ ከሆነ ምንዱብ ሠራተኛ መዋጮ መጠየቅ አልነበረበትም – አሣፋሪ ነው፡፡ እኔ እንዴት እንደምኖር አውቃለሁ፡፡ እንኳንስ ከደመወዜ ተቆርጦ ይቅርና አሁን የሚከፈለኝ ደመወዝ ተብዬ ዕጥፍ ድርብ ቢከፈለኝ እንኳን የኑሮውን ክብደት ሊያቃልልኝ አይችልም፤ የኔ ቢጤዎች የምንኖረው አንዷን ኪሎ ቅቤ በ“አጠቃቀስኩሽ” ሥልት ለዓመት እንደተጠቀመችባት ብልህ ሴት ዓይነት የኑሮን ጨውና ቅመም በብልሃት ‹አጠቃቀስኩሽ› እያልን ነው፡፡ ይህን የአባይ መዋጮ በተመለከተ የወያኔ መንግሥት ደደብነትና አስተዋይነትን ማጣት በእጅጉ ይገርመኛል – ለነገሩ ደደብነትና ወያኔ ለካንስ ሞክሼዎች ናቸውና፡፡ ስንቶችን እያዘባነነ የሚያኖር መንግሥት ጦሙን ከሚያድር ዜጋ በግድ የወር ደመወዙን ሲቆርጥ በዚህ መንግሥት ባለሥልጣናት ጭንቅላት ውስጥ የሚገኘው ነጭ ጭቃ ምን እንደሆነ ወይም የምን እንደሆነ ለማወቅ በከንቱ የምንዳክር አንጠፋም – በበኩሌ በራስ ቅላቸው ውስጥ ምን ተሸክመው እንደሚዞሩ ለመረዳት ሞክሬ ሲሰለቸኝ ደክሞኝ ትቸዋለሁ – እንዲያው ግን አምባርጭቃ ይሆን እንዴ? ሲገርሙ!

ወያኔዎች ኢንሳ በሚሉት የስለላ ድርጅታቸው ኢሳትን በዋናነት ጨምሮ የተቃዋሚ ሚዲያዎችን ሲቻላቸው ከዓለም ለማጥፋት ያ ባይቻል ደግሞ ወደ ሀገር ገብተው ሕዝብን በማንቃት የወያኔ ቅሌትና ውርደት እንዲሁም ከብረት የጠነከረ ፈርዖናዊና ናቡከደነፆራዊ የግፍ አገዛዛቸው ሕዝብ ላይ በዬጊዜው የሚፈጥረው ጭቆናና ግፍና በደል እንዳይገለጥባቸው በማሰብ በየወሩ የሚከሰክሱት የሀገር ሀብት አንድ አባይን ብቻ ሳይሆን አሥር ባሮና አሥር አዋሽን ያስገድባል፡፡ በዚያ ረገድ እኛን ብቻ ሣይሆን ሌላውን ዓለምም በሚያስደምም ሁኔታ እንደጉድ ነው ገንዘባችንን ለኛው መጨቆኛ የሚመዠርጡት፡፡ ይህን የማናውቅ እየመሰላቸው ከሆነ ተሞኝተዋል፡፡ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ለትርኪ ምርኪ የሚዲያ ማፈኛ ቁሣቁስና የውጪ ኤክስፐርቶች እንዲሁም የስለላ ቫይረስ ለመግዛት ሜዳ ላይ ከሚበትኑት ለሀገር ዕድገት ቢያውሉት ከጉራማይሌያዊ የልመና ባህላቸው በወጡ ነበር፡፡ እንደነሱ የገንዘብ አወጣጥ እኮ ኢትዮጵያ እጅግ ሀብታም ናት፡፡ እነሱ ገንዘብን በሚሊዮንና በቢሊዮን መዝረጥ የሚያደርጉት የነሱን ሥልጣን ለማስጠበቅ መሆኑ ከፋ እንጂ እንዳመነዛዘራቸው ለጭቁኑ ሕዝብ ቢሆን ኖሮ ረሀብና እርዛት ከሀገራችን ጠቅልለው ከወጡ በትንሹ 23 ዓመታትን ባስቆጠሩ ነበር፡፡ ለደኅንነት የተቃዋሚ ክትትልና የፀረ-ስለላ ስለላ አባላት በገፍ የሚወጣው መዝገብ የማያውቀው ወጪ፣ በወያኔ አገዛዝ የፊጥኝ ከታሰረው ምሥኪን ሕዝብ ተቀምቶ የወያኔን ወንበር ለመጠበቅ ለተሠማራው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ተብዬ የሚገፈገፈው ገንዘብ፤ ለመሣሪያ ግዢና በግዢው ሰበብ በሙስና ወደግል ካዝና የሚዶለው ቁጥር የማይገልጸው እጅግ ብዙ ገንዘብ፣ በመከላከያና በደኅንነት እንዲሁም በመሰል የፀጥታ ተቋማት ለሚርመሰመሰው ጆሮ ጠቢና አፋዳሽ ሁላ ካለበቂ ሥራ እንደ ቅጠል የሚረግፈው የሀገር ገንዘብ፣ ካበቂ ጥናትና ካለተጨባጭ ሀገራዊ ፋይዳ በዬጊዜው ለሚቋቋሙ አዳዲስ መሥሪያ ቤቶችና አደረጃጀቶች የሚወጣው ገንዘብ፣ ውጤቱ አስቀድሞ ለሚታወቅ የማይረባ ምርጫ የሚከሰከሰው ብዙ ሚሊዮን ገንዘብ፣ ለአብዮታቸው ጥበቃ ሲባል ለዬግልገል ካድሬው የሚዘራው ብር፣ሕወሓትን በዋናነት ይዞ ለዬአጋር ድርጅት ተብዎች ዓመታዊ የምሥረታ በዓላት ለፈንጠዝያና ለቸበርቻቻ የሚወጣው ገንዘብ፣ በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጪም በባለሥልጣናት የሚመዘበረው የሀገር ሀብትና ንብረት … ሁሉ ቢደማመር ሀገራዊ ልመና ሱስ ላልሆነበት የመንግሥት መዋቅር ያለ አንዳች ምፅዋትና ቡገታ  አንድ አይደለም ከመቶ በላይ ግድብና ሌላም የልማት ዕቅድ ያሠራል፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አንድ ብሔራዊ እስቴዲየም ለማሠራት ወገቤን የሚል መንግሥት ያላት ኢትዮጵያ 200 ታንኮችንና በአሥራዎች የሚቆጠሩ የጦር አውሮፕላኖችን በአንዴ ሲገዛ በሰበቡም ከፍ ሲል ለመግለጽ እንደተሞከረው በመቶ ሚሊዮን የሚገመት ገንዘብ በየማይማን የጦር “ጄኔራሎች” የግል ካዝና ሲገባ ስናይ “የነዚህ ሰዎች ዜግነት ምን ይሆን? በውነቱ ኢትዮጵያዊነቱ ይቅርና ጤናማነታቸው የማያጠራጥር ሰዎችስ ናቸው ወይ?” ብለን መጨነቃችን አይቀርም፡፡ ሰው እኮ አንድ ዓመት ይዘርፋል፤ አንድ ዓመት ይዋሻል፤ አንድ ዓመት ይሰርቃል፤ አንድ ዓመት ይሞስናል፤ አንድ ዓመት ይዘሙታል፣ አንድ ዓመት ያጭበረብራል፣ አንድ ዓመት … አዎ፣ በወረት ለተወሰነ ጊዜ ከመስመር መሠወር/መጥፋት ያለ ነው፡ አንድ ሰው የሀብት ፍቅር ካራዠው  መቼስ ምን ይደረጋል በሚፈልገው ነገር እስኪጠረቃ ድረስ ወይም በቃኝን እስያውቅ ድረስ ለተወሰነ ጊዜ መጥፎ ነገርን እያደረገ ይቆያል፤ ሰው ከሆነ ግና በሕይወት ውጣ ውረድ መማር አለበት፡፡ የተሸከመው አንጎል ጭቃ ሣይሆን ዛሬን ከነገና ትናንትን ከትናንት በስቲያ እያመዛዘነ ገምቢ ግንዛቤን ሊያስጨብጠው የሚችል ትልቅ መለኮታዊ ስጦታ ስለሆነ በሕይወት ፈተና ተሸንፎ ከተዘፈቀበት ሰውነትን ከሚያሳንስና ኅሊናን ከሚያጎድፍ ወደእንስሳነት ደረጃም ከሚያወርድ አዘቅት ለመውጣት መሞከር አለበት – ከወያኔ እንዲያውም ብዙ እንስሳት የተሻሉ “ሞራላዊ” ፍጡራን ናቸው፡፡ ዕድሜ ልኩን በክፋትና በመጥፎ ድርጊቶች ተበክሎና በዚያው ቆርቦ መኖር ለታዛቢም ይሰቀጥጣል፡፡ ወያኔዎች ከጧት እስከማታ ቢያጋፍሩ በቃኝን የማያውቁና በቂምና በበቀል የታጀሉ ትንግርተኛ ፍጡራን ናቸው – “የሞኝ ዘፈን ሁልጊዜ አበባዬ” እንዳትሉኝ እንጂ ለምሳሌ በዐሥራዎቹ ዕድሜ ሳሉ የጀመራቸው ፀረ-ኢትዮጵያና ፀረ-አማራ ጥላቻ አሁን ድረስ በስተርጅናም አብሮ ዘልቆ እነስብሃትንና ሣሞራን ምን ያህል እያሰቃያቸው እንደሆነ የምናውቀው ነው፡፡ ይሄ ታዲያ መረገም አይደለም ትላላችሁ? ብቻ ይህንን የምለውን ሁሉ የማናውቅና ሁኔታዎች ሲያመቹና ጊዜው ሲደርስ የማንጠይቅ ከመሰላቸው አሁንም ተሞኝተዋል፡፡

ካሉት ጥቂት መጻሕፍት ውጪ ምንም ምድራዊ ሀብትና ንብረት እንዳልነበረው ካላንዳች ሀፍረት በራሱ አንደበት ሲናገር የነበረውና የባሕርይ አምሳያው ወላጅ አባቱም “ [በድህነቱ ምክንያት] የአምስት ብርና የአሥር ብር ኖቶችን እንኳን መለየት አይችልም” በማለት የወፍ ምሥክሯ ድምቢጥ ዓይነት የዋቢነት ቃሉን የሰጠለት መለስ ዜናዊ 3.7 ቢሊዮን ዶላር በስሙ ተመዝግቦ መገኘቱን አንድ ዓለም አቀፍ ተቋም በቅርቡ አጋልጧል፡፡ ከዚያም ቀደም ብሎ በዚሁ ብዔል ዘቡል የበኩር ልጅ በሰምሃል መለስ ስም ከአምስት ቢሊዮን ዶላር (ሚሊዮን አይደለም!) – ልድገመው ከአምስት ቢሊዮን ዶላር በላይ ተቀማጭ ገንዘብ እንደተገኘ ተዘግቧል፡፡ በአባትና ልጅ ስም የተገኘው ገንዘብ ብቻውን ከሁለት በላይ የአባይን መሰል ግድቦችን ያስገነባል፡፡ ታዲያ የምን ቧጋችነትና ማራሪነት ነው? የምንስ ማስመሰል ነው? የቆሎ ተማሪ የሀብታምም ልጅ ቢሆን ቧግቶ መብላቱ፣ ለምኖ ካልበላ ትምህርቱ ስለማይገባው ነው የሚል አፈ ታሪክ ስላለ ነው፡፡ ኢትዮጵያስ ካልቧገተችና ድሃ ልጆቿን ራቁታቸውን ካላስቀረች ልትለማ አትችልም ማለት ነው? ምን ዓይነት ዕንቆቅልሽ ነው? ኢትዮጵያየን ከ30 ዓመታት በላይ በሙያዬ ያገለገልኳት ሰውዬ የእኔ ልጅ በወያኔ ወለድ የኑሮ ውድነት ሳቢያ በቀን አንዴም መመገብ እያቃተው ከኔ ከአባቱ መናኛ የወር ደሞዝ ለአባይ አዋጣ ስባል ሰምሃል መለስ ደግሞ የኢትዮጵያን አንጡራ ሀብት በሎንዶን ታላላቅ ሆቴሎች እየተዘዋወረች ከሎንዶናውያንና ወያኔያውያን ወሮበሎች ጋር በዬምሽት ክበባቱ ጢምቢራዋ እስኪዞር እየጠጣች ስታስታውክበትና አለመላው ስትዘባነንበት ሲታይ ምን ዓይነት ሀገራዊ ስዕል ነው የምናስተውለው? የዚህን አስገራሚ እውነት ተፈጥሯዊ ፍትህስ መቼ ነው የምናየው? የሆነ የሚያበሳጭ ሀገራዊ ምስል በአእምሯችሁ ብልጭ አላለባችሁም? ስንቱ ባለሥልጣንና የጦር አበጋዝ ነው ከነየልጁ በዚህ መልክ በሀገር ሀብት እየተጫወተ የሚገኘው? ታዲያ ይሄ ሁሉ አላግባብ በሙስናና በዝርፊያ የሚባክን ሀብት ስንት ግድብ፣ ስንት የባቡር መንገድ፣ ስንት አውራ ጎዳና፣ ስንት ሆስፒታል፣ ስንት ትምህርት ቤት፣ ስንት ኮሌጅና ዩኒቨርስቲ (ያልተማሩ መምህራን የታጨቁበት ባዶና ከርክክብ ሥነ ሥርዓቱ ቀድሞ የሚሰነጣጠቅ – ጥቂት ቆይቶም የሚፈራርስ ሕንፃ ሣይሆን በሁሉም ረገድ ደረጃውን የጠበቀ ማለቴ እንደሆነ ተረዱልኝ)፣ ስንት የበጎ አድራት ተቋም፣ ስንት ክሊኒክና የጤና ኬላ፣ ስንትና ስንት የመኖሪያ ቤቶችና ሕንፃዎች አይሠራም ነበርን? ይህ ሁሉ ገንዘብ ቅን ተገዢ ያደረገንን ማይምነት ከኢትዮጵያ ምድር ጠራርጎ አያወጣውም ነበርን? ይህንንም ሕዝቡ አያውቅብንም ዘመኑ ሲደርስም አይጠይቀንም ብለው ከሆነ በርግጥም ተጃጅለዋል፡፡ ለነገሩ ሆድ አለልክ ሲጠግብ እኮ ጭንቅላት ፉዞ ይሆናል አሉ፡፡

በቀዳማዊ ኃ/ሥ ጊዜ ስንት ብድርና ዕርዳታ ወደ ሀገር ገባ? በደርጉስ? በአሁኑ የወያኔ ጉጅሌስ? በዕርዳታና በብድር መልክ ከሚገባው ገንዘብ ምን ያህሉ ነው በትክክል በታለመበት ሥራ ላይ የሚውለው? አሁን የሚባለውን እንስማ ካልን ወደ ሀገር ከሚገባው የብድርም ሆነ የዕርዳታ ገንዘብ ውስጥ ሩብ ያህሉ እንኳን የሀገር ጥቅም ላይ አይውልም፡፡ ይመዘበራል፤ የግለሰቦችን ኪስ ያሞቃል፡፡ ለሀገር የሚቆረቆር ባለሥልጣንም ሆነ ተቆጣጣሪ ለጋሽና አበዳሪ ሀገር ባለመኖሩ በኢትዮጵያ ስም የተቃፈፈው የዕርዳታም ይሁን የብድር ገንዘብ እሳት ውስጥ የገባ ቅቤ ሆኖ ይቀራል፡፡ በመሠረቱ ሙሰኝነት ዱሮም ነበር – ግን እንደዛሬው ዐይኑን ያፈጠጠና ግዘፍ ነስቶ በአደባባይ ሲራመድ የሚታይ አልነበረም፤ ይሉኝታ የሚባል የኅሊና ዳኛ በመጠኑም ቢሆን  ነበር፡፡ ዛሬ ግን ደመወዙን የምናውቀው አነስተኛ ባለሥልጣንና የሥራ ኃላፊ ሁሉ የወር ገቢው ለሦስት ቀንም እንደማይበቃው እየተረዳን ወር ከወር ጮማ ሲቆርጥና ዊስኪ ሲጨልጥ ነው የሚገኘው – የሚመነዝረው ረብጣ ብርማ አይነሣ፡፡ ከየት አመጣው? ባለፈው ከአንድ መጽሔት እንዳነበብኩት እርሱና ሚስቱ ተኝተው ባደረጉት ነገር ምክንያት ፈጣሪ የሰጣቸውን ሦስተኛ ልጅ ሚስቱ ብቻ እንደሰጠችው በመቁጠር ትልቅ የፌሽታ ድግስ በቤቱ ውስጥ አድርጎ የ2.5 ሚሊዮን ብር መኪና ቁልፍ ለምሽቱ የሸለመው ወያኔ ሀብታም ያን የሚጫወትበትን ገንዘብ ከየት አባቱ እንዳመጣው ብንጠይቅ መልስ የሚሰጠን የለም፡፡ እነዚህን መሰል የወያኔ ንፋስ ወለድ ሀብታሞች በከንቱ የሚቀዳድዱትን ብር ለቁም ነገር ቢያውሉት አንድ ቀርቶ አምስት ስድስት ግድብ አይሠሩም ነበር ወይ? የኔ ቢጤን የሥጋን ምግብ ተውትና በቅጡ የተሠራች ኩርጥ ያለች የአተር ወጥ እንኳን ካዬ ወራት ያስቆጠረ መንዳካ ድሃ ያለችውን መናኛ ሣንቲም በግድ ከሚቀሙ እነዚህንና አላሙዲንን የመሳሰሉ ደደብ ሀብታሞችንና ቱጃር የባለሥልጣን ነቀዞችን  ቢያስተባብሩ አባይን የሚያስንቅ ስንትና ስንት ግንባታ ሊሠሩ አይችሉም ነበር ወይ? እነሱ እንደልባቸው ለሚምነሸነሹባት ሀገር እኔ ምን ቤት ነኝና የሌለኝን ልስጥ? ይህኛው ግፍ ከሁሉም ግፎች አይበልጥምን? አሁን ኢትዮጵያ በርግጥ የማን ናት? ከትንሽ ጣት ምን ተቆርጦ ይወሰዳል? እነዚህ የመንግሥት ሰዎች ግፍ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አያውቁም ማለት ነው? ጤፍ በኩንታል ከብር 1600 በላይ በሆነበትና የአንድ ወዛደር ወርሃዊ ደሞዝ ከ400 ባልበለጠበት ሁኔታ ምኑን ነው ከምኑ የሚቆርጡት? ምነው እስከዚህን አቅል አሳጣቸው? …

አባይን ተገድቦ ማየት ማንም አይጠላም፡፡ “አሻራውን አባይ ላይ የማያስቀምጥ ኢትዮጵያዊ አይደለም” የሚሉት ፈሊጥ ደግሞ የእውነት መሠረት የሌለውና ጠርዝ የለቀቀ የግድብ ‹ፖሊቲሳይዜሽን› ነው፡፡ ከእውነቱ ፍጹም የራቀ የማጨናበሪያ ፕሮፓጋንዳ ነው፡፡ መቼም ቢሆን አባይ ቢገድብ የሚጠላ ኢትዮጵያዊ ሊኖር አይችልም – መንግሥት ቀርቶ የመንግሥት ጳጳስ ቢያወግዘንም የአባይን መገደብ ሣይሆን የምንቃወመው ጠንጋራ አካሄዱንና የወያኔን ገደብ የለሽ ቱልቱላ ነው፡፡ ለምሳሌ ከፍ ሲል እንደተገለጸው ግድቡ ለሆነ ችግር ማስተንፈሻ ድንገት ጣልቃ ገባ እንጂ ሕዝብ አልመከረበትም፤ የሥራው ኮንትራት አሰጣጥም ብዙ ችግር እንዳለበት፣ ዕቃ አቀራረብና ሌላ ሌላ ሂደት ላይም ወያኔያውያን ባለጠጎችና ሞሰቦን የመሳሰሉ የወያኔው መርዝአቀባይ  ደንገጡር ድርጅቶች ይበልጥ እንዲከብሩበት ተደርጎ እየተካሄደ መሆኑ ከታማኝ የዜና ምንጮች ሰምተናል፤ ታዲያስ? ለምን እንታለላለን? እንጂ በመሠረቱማ ወያኔን መጥላትና የአባይ መገደብ የግድ የሆነ ግንኙነት ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ችግሩ ተደጋግሞ እንደተነገረው ዘረኝነትን በዋነኛነት ጨምሮ ከአባይ በፊት መገደብ ያለባቸው ብዙ ወያኔያዊ የመጥፎ አገዛዝ ጎርፎች መኖራቸው ነው፡፡ እኔ ለምሳሌ ለአባይ ድምቡሎ አላዋጣም፤ ፍላጎቴ ራሱ ዜሮ ነው፡፡ የኔ ሰዎች የያዙት ስለማይመስለኝና ስላልሆኑም እንዲያውም ስለአባይ ወሬው ራሱ ባይነሳብኝ እመርጣለሁ – ወያኔን ብሎ ለኢትዮጵያ አሳቢ ይታያችሁ! አንድስ አንድስ እሚያህል መሬት እየገነደሰ ለባዕድ የሚሸጥ ወያኔ እንዴት ለሀገር ተቆርቁሮ ይህን ታላቅ ፕሮጀክት ሊጀምር ይችላል? እደግመዋለሁ – ግድቡን ግን ጠልቼ አይደለም፡፡ በሌላም በኩል ካየነው እኔን እየራበኝ፣ ኑሮየ የጎሪጥ እያየኝ ነጋ ጠባ እያላገጠብኝ ከኔ ተርፎ ለአባይ ማለት ከጅብ ተርፎ ለውሻ እንደማለት ስለሆነ ላዋጣ ብዬ ልግደርደር ብል እንኳን እንደስድብ ተቆጥሮ “ተው አንተ፣ አቅምህን ዕወቅ፣ ዕረፍ እንጂ፣ አንተን አይመለከትም፤ ምን አለህና! “ ነው ልባል እሚገባ፡፡ ዐይን አይቶ ልብ ይፈርዳል ይባላል፡፡ በቀን አንዴ መቅመስ ያቃተው ሰው፣ የነተበ ሸሚዝና አቧራ የቃመ የሸራ ይሁን የላስቲክ ጫማ ማድረጉ የማይታወቅ ሰው፣ ወር በገባ በአምስተኛውና ስድሰተኛው ቀን ሁሉም የቤት አስቤዛው ተመካክሮ በአንዴ የሚያልቅበትና ኑሮውን በብድርና እልፍ ሲልም በውጭ ሀገራት በሚኖሩ ዘመዶቹ መጠነኛ የበጀት ድጋፍ ተሰናባቹን ወር ከአዲሱ ወር ለማገጣጠም የሚፍጨረጨር ሰው፣ ልብሱ እላዩ ላይ አልቆ – ከአንሶላ ጋር ተቆራርጦ – ከሶፋና አዳዲስ የቤት ዕቃዎች ግዢና ጥገና ጋር እስከወዲያኛው ተፋትቶ፣ … በደመ ነፍስ ብቻ (ጌታ) ናስቲለው የሚኖር ሰው የግድብ ወሬ አይገባውም – እንዲገባው መጠበቅ ራሱ ቂልነትና ለተቀማጭ ሰማይ ቅርቡን የሚያስተርት ፌዝና ቀልድ ነገር ይመስለኛል፡፡ ይህ ግድብና የግድብ ቱሪናፋ የቅንጦት ወሬና እውነትም ለቡትለካ እንዲያመች ለወያኔ ዕድሜ ማራዘሚያነት ተለክቶ የተሰፋ መለስ ዜናዊያዊ የማጭበርበሪያ ካባ ነው – ካባ አሰፋፍ እንደሱ እንደመለስ የሚሆን ደግሞ በዓለም የለም፤ ማገብት፣ ተሓት፣ ተሓህት፣ ሕወሓት፣ማሌሊት፣ ኢማሌኃ፣ ኢዴመአን፣ ኢሕዲን፣ ብኣዴን፣ ደኢሕዴግ፣ ኦሕዴድ፣ ብዙ ንቅናቄዎች፣ ብዙ ዴዶች … ስልቻ ቀልቀሎ፣ ቀልቀሎ ስልቻ …ይህ ሁሉ ካባ ወያኔ ላይ የሚጠለቅና በአብዛኛው በኢንጂኔር መለስ ዜናዊ የተሰፋ ነውና ነበርም – አማርኛውም ጠፋኝ ልጄ፡፡ በዚህ በአባይ ግድብ የውሸት ካባ ደግሞ ኢትዮጵያዊነት አይለካም – መለካት ካለበት እንግዲያውስ ይህን ወያኔያዊ ቅራቅንቦና የነፃነት ትግልን የማደናቀፊያ ሥልት ተከትሎ ራሱ በመወናበድ ሌሎችን የሚያወናብድ ቀፎ ዜጋ ነው – በቃ ቀፎ፡፡ አናቱን በመዶሻ እየወቀጡት እግሩን ሲያኩት መታለሉ የማይገባው ዝንጉ ካለ ቀፎ ብቻ ሣይሆን ድንጋይ ራስም ሆዳምም ደንቆሮም ነው፡፡ ለእኔ ሀገርና መሪ ሲኖረኝ ሁሉም ይደርሳል፡፡ ዝንጀሮ “ቀድሞ የመቀመጫየን” እንዳለችው  ሀገራዊ ነፃነት ሣይኖረኝ አንድ ሺህ ግድብና አንድ ሌላ ሺህ ባቡር ከነሃዲዱ ቢኖረኝ ምንም አይፈይድልኝም፡፡ ጣሊያን በአምስት ዓመት የሠራቸው የልማት አውታሮች ጥቅማቸው እንዳለ ሆኖ ቅኝ ገዢውን ግን ወደ መልአክነት አልለወጡትም፤ በአፓርታይድ ዘመን ደቡብ አፍሪካ ውስጥ የታዩና ሀገሪቷን ከበለጸጉ የዓለም ሀገሮች ተርታ ያስሰለፉ የዕድገትና ልማት እመርታዎች የአፓርታይድን ሥርዓት ከመገርሰስ ካለማዳናቸውም በላይ ሥርዓቱን ከዓለም አቀፍ ውግዘትና መነጠል አውጥተው ለጽድቅና ለበረከት አላበቁትም፡፡ ኦ!ኦ! አሁንስ በቃኝ እባክህን፡፡ ዕንቅልፌ እያዳፋኝ ነው፡፡ እነዚያ እርጉም ትናንሽ ወያኔዎችም ግብዣየን መቀበል አለመቀበላቸውን ላረጋግጥና ጋደም ልበል፡፡ ከቅብዥር ነፃ የሆነ እውነተኛ ዕንቅልፍ ባይኖርም ዐረፍ ማለቱ አይከፋም፡፡ እነዚህ ነቀዝ ወያኔዎች እያሉ በቅጡ መተኛትም እኮ ቀረ፡፡ 11፡30 ሌሊት (ንጋት?)፡፡ 24/7/2006ዓ.ም