Tuesday, October 20, 2015

ውሸት ውሎ አድሮ መጋለጡ አይቀርም!!!

ሥልጣንን በጠመንጃ አፈሙዝ ተቆጣጥሮ ያለው የወያኔ አገዛዝ ካለመታከት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ተአምር ሊመስል በሚችል  መንገድ እያሳደኩ ነው እያለ ሲዋሽ አመታት ተቆጥረዋል። በተለይ ምዕራባዊያንን ሲያታልልበት የነበረው የዲሞክራሲ ጭንብል በምርጫ 97 ከተገፈፈበት ወዲህ ላለፉት አስር አመታት ባለ ሁለት አሃዝ እድገት አስመዝግቤያለሁ እያለ እጅ  እጅ እስኪለን ድረስ በባዶ ሜዳ ስለ ልማትና የዕድገት ሲነግረን ሰነበቷል።

ወያኔ በጉልበት በሚያስተዳድራት ኢትዮጵያ የልማትና የእድገት ፕሮፓጋንዳ ስለ ሰበአዊ መብትና ስለዲሞክራሲ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለማፈኛና አፍ ለማዘጊያነት በማገልገል ላይ ይገኛል ። አለማቀፍ የሰባአዊ መብት ተቋማት ስለሰበአዊ መብት ጥሰት ለሚያቀርቡት አቤቱታ ሁሉ የሚሰጠው መልስ “ኢኮኖሚውን እያሳደግን ነው” የሚል ነው። ኢኮኖሚ ማደግ አለማደጉን ትርጉም የሚኖረው ከህዝብ የእለተ ተእለት ኑሮ ጋር ሲያያዝ መሆኑ ሁሉ  ትርጉም አጥቷል። ራበኝ የሚለው ሰው ሁሉ ጠገብኩ ማለቱ ነው ተብሎም ይተረጎማል።

የውሸት ነገር ውሎ አድሮም ቢሆን መጋለጡ አይቀርምና ይኼው በቅርቡ የተከሰተው ድርቅ የወያኔን የውሸት ፕሮፓጋንዳ ክንብንብ ገፎታል። አለም በሙሉ አስር አመት ሙሉ በሁለት አሃዝ ሲያድግ የነበረ ኢኮኖሚ ባለበት ሃገር ውስጥ አንዲት የድርቅ አመት ካለርሃብና ልመና እንዴት መሻገር አቃተው የሚል ጥያቄ በሰፊው በማንሳት ላይ ነው። ወያኔ ለዚህ ጥያቄ መልስ የለውም።  በአለም ዙሪያ ያለው ተመክሮ ሁሉ የሚያሳየው ወያኔ አድጌበታለሁ ብሎ ሲለፍፍ ከኖረው አሃዝ በታች በግማሽ ያደጉ ሃገሮች እንኳ አንድም ጊዜ አንድ የድርቅ ዘመን መሻገር አቅቶአቸው  ሲንገዳገዱና መንግሥታቸው ለልመና ሲሄድ አለመታየቱን ነው።

ኢትዮጵያ ውስጥ ወያኔ የሚያወራውን ያህል ያልሆነ ቢሆንም በአንዳንድ ከተሞች አካባቢ የሚታየው እድገት የተገኘው ከውጭ መንግስታት የገንዘብ ብድር፣ በአለም አቀፍ ተቋማት እርዳታ፣ ስደተኛው ኢትዮጵያዊ በገፍ በሚልከው ገንዘብና ወያኔ ከድሃውና ከነጋዴው ከዝርፊያ ባላነሰ ሁኔታ በሚሰበሰበው ግብርና መዋጮ የተገኘ እንጂ ወያኔ ባስፋፋው ኢንዱስትሪና ልማት እንዲሁም ሀገር ውስጥ በፈጠረው ሀብት አለመሆኑ የሚታወቅ ነው።

የወያኔ ሹማምንትና አገልጋዮች ሀብት በሀብት መሆናቸውን እንደ እድገት ካልቆጠርን በስተቀር  ህዝባችን ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮውን እንኳን መደጎም አልቻለም ።በዝርፊያ ገንዘብ ሹማምንቱና የወያኔ ባለምዋሎች የገነቡትን ፎቅ የሀገር ልማት ነው ካላልን በስተቀር እውነተኛና የህዝብ ህይወት ከመሰረቱ የሚቀይር ልማት አገር ውስጥ አለመካሄዱ ትንሽ ገለጥ ሲያደርጉት የሚታይ ሃቅ ነው። አንድ የድርቅ ወቅት መሻገር አቅቶት ብዙ ሚሊዮኖችን ከረሃብና እልቂት መታደግ ያልቻለ ኢኮኖሚ አስር አመት ሙሉ በሁለት አሃዝ አድጓል ብሎ የሚያምን ሰው ሊኖር አይችልም።

የወያኔ የኢኮኖሚ አሃዝ “መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ” ከሚለው የሀገራችን ግፈኛ አባባል  ብዙም አይለይም። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለህዝብ በሚጠቅም መንገድ የማደጉ ጉዳይ በመጀመሪያ ፍትሐዊ ኢኮኖሚያዊ ሥርአት መገንባትንና ዴሞክራሲ ማስፈንን ይጠይቃል።
በመሆኑም የዛሬው የወያኔ ኢኮኖሚ የዝርፊያ ኢኮኖሚ እንጂ ህዝባዊ ሽታ የለውም። የኢትዮጵያን ህዝብ እዚህና እዚያ በሚብለጨለጩ ያውም በአብዛኛው በብድርና እርዳታ በተገኙ ልማት ተብዬ ነገሮች ለረዥም ጊዜ ማታለል አይቻልም።

ወያኔ በሚሰጠው አሃዝ የሚያድግ ማንኛውም ሀገር የውጭ ስደተኞችን ያስተናግድ እንደሆን እንጂ ወጣቶች ሞትና ህይወትን አማራጭ አድርገው አይሰደዱበትም። ባለ ሁለት አሃዝ አዳጊ ኢኮኖሚ በየትም ሀገር የስደተኞች ምንጭ ሆኖ ታይቶ አይታወቅም በዘረኛው ወያኔ ተገዢዋ ኢትዮጵያ ካልሆነ በስተቀር።

አርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ትንሳኤ ከዘራፊው የወያኔ ሥርዐት መወገድ ጋር በጥብቅ የተሳሰረ መሆኑን ያምናል!  ስለዚህም ህዝባችን ወያኔን ለማስወገድ የተጀመረውን ትግል በነቂስ ለመቀላቀል ዛሬውኑ እንዲነሳና ከጎናችን እንዲሰለፍ የማያቋርጥ ጥሪውን ደግሞ ደጋግሞ ያስተላልፋል።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

Tuesday, October 13, 2015

ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጀርባ – አርበኞች ግንቦት 7

ከሁለት አመት በፊት በቂ ህዝባዊ ምክርና ውይይት ያልተካሄደበት የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ተግባር ላይ ለማዋል የተደረገው ሙከራ በበርካታ የኦሮሞ ተማሪዎች ተቃውሞ እንደገጠመውና በየኮሌጁ በተነሱ ተቃውሞዎች ሳቢያ በርካታ ወጣቶች በወያኔ እንደተገደሉ ብዙዎች በእስር እየማቀቁ እንዳሉ ይታወቃል። ግጭቱ የፈጠረው ቀስል ገና ባላገመ ማግስት በአሁኑ ወቅት የህወሃቱ አባይ ጻሀይ በውድም በግድም ፕላኑ “ይተገበራል” ብሎ በዛተው መሰረት ተግባር ላይ ለማዋል ሰሞኑን ሽር ጉድ ተይዟል።

ከዚህ ማስተር ፕላን በስተጀርባ የተደበቀው የህወሃትና ጀሌዎቹ አላማ በአግባቡ አለመተንተኑ የፕላኑ ተቃዋሚዎች ኦሮሞዎች ብቻ በመሆናቸው ጥያቄው የግዛት ስፋትና ጥበት ወይም ባለቤትነት ጉዳይ መስሎ ይታይ እንጂ ነገሩ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ የሚያስቆጪና ተቃውሞ ሊያስነሳ የሚገባው ደባ ነው። ከህወሃት/ ወያኔ ማስተር ፕላኑ ጀርባ የመሬት ዝርፊያ እቅድ እንዳለው አርበኞች ግንቦት 7 ከእስከ አሁኑ ተመክሮና ባህሪያቸው በግልጽ ማየት ይቻላል ብሎ ያምናል።

እስከዛሬ ባለን ተመክሮ ከተማውን በማስፋፋት ስምና መሬት የመንግስት ነው የሚለውን ሰበብ በመጠቀም ድሃ ገበሬዎችን በማፈናቀል የተዘረፈውን መሬት ልብ ማለትና ማስታዎስን ያሻል።

በሀገራችን ቅጽበታዊ ሚሊየነር የሆኑት የወያኔ ሹማምንት፣ ዘመዶቻቸውና ባለሟሎቻቸው ዋናው የሃብታቸው ምንጪ ድሆችን በማፈናቀል በገፍ እየዘረፉ የሸጡትና የተቆራመጡት መሬት ነው። የአዲስ አበባ መሬት የወያኔ የወርቅ ማእድን ጉድጓድ ከሆነ ቆይቶል። በየከተማው ዙሪያ ያሉ ምስኪን ገበሬዎች የረባ ካሳ እንኮን ስላላገኙ ከግብርና ወጥተው ወደኩሊነትና የቀን ሰራተኝነት ተበታትነው ቤታቸው ፈርሶ ይገኛል።

የወያኔ መንግስት ይህን ማስተር ፕላን ስራ ላይ ለማዋል የሚስገበገብበት ዋናው ምክንያት የሀገርና ከተማ ልማት ጉዳይ አይደለም። የከተማው መሬት ተዘርፎ በማለቁ ሌላ በገፍ የሚዘረፍ መሬት ለማመቻችት ብቻ ነው። ችግሩ ለምን ፕላን ኖረ፣ አዲስ አበባ በአግባቡ ማደግና መልማት የለባትም የሚል አይደለም። ቁምነገሩ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን በቅጽበት እያፈናቀለና እየደኸዩና ቤተሰብ እየፈረሰ፤ በጥቂት ህገ ወጥ ባለስልጣናት የሚደረገው ሀፍረት የለሽ ዝርፊያ ነው ችግሩ። በመሆኑም ይህን የዝርፊያ ተግባር ብሄረሰብ ሳንለይ ሁላችንም ልንቃወም ይገባል። ይህ ማስተር ፕላን የህግ የበላይነትና ተጠያቂነት በሌለበት ሁኔታ ስራ ላይ በአግባቡ ስራ ላይ መዋል አይችልም። በፕላኑ የተጠቃለለውን ህዝብና አካባቢ ሊጠቅም የማይችል ፕላን ሊሆን የሚችለው የዝርፊያ ፕላን ብቻ ነው።

የወያኔ መንግስት በሰፈራ ሁኔታ ባካሄደው የከተማ ቦታ ዝርፊያ ነው ዛሬ በየመሸታ ቤቱና በየከተማው ዋና ዋና መዝናኛ ቦታዎች ብር እንዳሻቸው የሚነዙ የወያኔ ቱባ ባለሟሎች የተፈጠሩት። ወያኔ ሌላው ቀርቶ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ዘረኝነት በማካሄድ ላይ እንደሚገኝ እናውቃለን።

መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን በማር የተላወሰ መርዛማ ፕሮጀክት አጥብቆ እንዲታገል አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪውን ያቀርባል።

በሀገራችን ጥቂቶች እያረፉ የሚከብሩበት ድሃ ወገኖቻችን ይበልጥ እየደኸዩ የሚሄዱበት ዘመንና ስርአት አለንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲወገድ ወጣቱ አርበኞች ግንቦት 7ን ባለበት ይቀላቀል። ትግላችን እስከመጨረሻው ድል ይቀጥላል።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7

Wednesday, October 7, 2015

ድርጅታችንን እናጠንክር፤ በጽናት እንታገል!

“የአርበኞች ግንቦት 7 አባል በመሆኔ እኮራለሁ” እያሉ በአገዛዙ የይስሙላ ችሎት ሳይቀር በድፍረት የሚናገሩ ወጣቶች ተፈጥረዋል። ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለዲሞክራሲ፣ ለእኩልነትና ለሀገር አንድነት መስዋዕትነት መክፈል የሚያኮራ ተግባር መሆኑ በተግባር የሚያሳዩ ወጣቶች መጥተዋል፤ አሁን በርካቶችም እየመጡ ነው። ወያኔ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በማኅበረሰባችን ውስጥ የዘራው የፍርሀትና የአድርባይነት ስሜት በራሱ በወያኔ የአገዛዝ ዘመን ተወልደው ባደጉ ወጣቶች እየተናደ፤ በምትኩ ሊጠፋ ተቃርቦ የነበረው የአገር ፍቅርና የአርበኝነት ስሜት እያንሰራራ ነው።

ቅንነት፣ ሀቀኝነት እና ጽናት ከተጣሉበት ጉድጓድ አቧራቸውን አራግፈው እየተነሱ ነው። በማኅበረሰባች ውስጥ ትልቅ የስነልቦና አብዮት እየተካሄደ ነው።

ከስነልቦና ለውጡ ጋርም በተግባር የአገር አድን ሠራዊትን የመቀላቀል ፍላጎት ያላቸው ወጣቶች ቁጥር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ ነው። ወጣቶች የአገራቸው ባለቤት መሆናቸው ተገንዝበው የፓለቲካ ሥርዓት ለውጥ ለማምጣት በቁርጠኝነት መነሳታቸው ተስፋ ሰጪ ነገር ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 በዚህ የለውጥ ወቅት ውስጥ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ አጽንዖት ልንሰጣቸው ስለሚገቡ የድርጅትና የሥነሥርዓት (ዲሲፕሊን) አስፈላጊነት ላይ የጋራ ግንዛቤ መያዝና በተግባርም መተርጎም አስፈላጊ ነው ብሎ ያምናል።

ወጣቶች ትግሉን ለመቀላቀል መሻታቸው መልካም ነገር ነው። ሆኖም ግን በድንገት ብድግ ብለው መንገድ ከመጀመር ይልቅ ከሚያምኗቸው ወዳጆቻቸው ጋር የመሠረቱት፤ ከአርበኞች ግንቦት 7 ጋርም ትስስር የፈጠረ ስብስብ አካል ሆነው መቆየታቸው እጅግ አስፈላጊ ነው።
በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ ሆኖ የሚስጢር ድርጅት ማዋቀር አስቸጋሪ መሆኑ የማያጠራጥር ቢሆንም የማይቻል ነገር ግን አይደለም። ወጣቶቻችን በአምባገነን ሥርዓት ውስጥም ሆነው በዲሲፕሊን የታነፀ ድርጅት የመፍጠርን ክህሎት መላበስ ይገባቸዋል። ይህንን ማድረግ ስንችል ነው የህወሓትን ፀረ-አገርና ፀረ-ትውልድ ተግባር ማክሸፍ የምንችለው። ትግሉን በሁሉም የኢትዮጵያ ግዛቶች ማቀጣጠል የምንችለው በየአካባቢው የተደራጀ የለውጥ ኃይል ሲኖረን ነው። ስለሆነም የምስጢር የተደራጀ አካል በየመኖሪያና የሥራ አካባቢዎቻችን ሁሉ እንዲኖር ማድረግ ከአጣዳፊ ሥራዎቻችን አንዱ እናድርገው።

ሁለተኛው ነጥብ ሥነሥርዓትን የሚመለከት ነው። ሥነሥርዓት ከሌለ ድርጅት የለም። የህወሓት አገዛዝ ያሳደረብን ጎጂ የባህል ተጽዕኖ ከባድ በመሆኑ ራሳችንን በሥነሥርዓት ለማነጽ መልፋት ይጠበቅብናል። አገራችንና ራሳችንን ከህወሓት አገዛዝ ነፃ አውጥተን የተሻለ ሥርዓት ማምጣት የምንችለው ራሳችን፣ ድርጅታችን እና ተግባሮቻችን ለሥነሥርዓት ተገዢ ስናደርግ ነው። የነፃነት ታጋዮች ራሳቸውን ለሥነ ሥርዓት ያስገዙ መሆን ይኖርባቸዋል። አስተሳሰባችን ራሱ ሥነ ሥርዓት የያዘ ሊሆን ይገባዋል። እንደዚሁም ሁሉ ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት የታነጹ ሊሆኑ ይገባል።

የንቅናቄዓችንን መዋቅር በመላው አገራችን ከዘረጋን፤ ራሳችንን፣ አስተሳሰቦቻችንና ተግባሮቻችን በሥነሥርዓት ከመራን፤ ቅንነት፣ ሀቀኝነትና ጽናት ከተላበስን ድላችን ቅርብ እና አስተማማኝ ነው። ለውጥን የሚናፍቅ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራት ይተግብር።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!