Thursday, January 18, 2018

ለዲሞክራሲ የሚናካሂደው ትግል በምንም አይነት ጥገናዊ ለውጥ አይደናቀፍም!

የአርበኞች ግንቦት 7 ርዕስ አንቀጽ

የኢትዮጵያ ህዝብ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ከታህሳስ 3 ቀን 2010 ጀምሮ እስከ ታህሳስ 21 ቀን ሲያካሂድ በሰነበተው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ በራሱ በድርጅቱ ውስጥ ተፈጥሮአል ባላቸው ችግሮች እና የአገራችንን ግዜያዊ ሁኔታና የወደፊት አቅጣጫ አስመልክቶ ግምገማ በማድረግ ባለ 8 ነጥብ ውሳኔዎችን አሳልፎ እንደተጠናቀቀ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል ።

ኢህአዴግ አወጣሁ ያለው ይህ መግለጫ በአጭሩ ሲዳሰስ በቅርጹም ሆነ በይዘቱ ብዙ ችግሮች የሚታዩበት ፤ አደናጋሪና ወጥነት የሌለዉ፥ እርስ በርሱ በሚጣረስ ሀሳቦች የታጨቀ ከመሆኑም በላይ አገራችን የገባችበትን መሰረታዊ ችግሮች ያላገናዘበ እና ህዝባችን በተለይ ላለፉት ሶስት አመታት እያነሳቸው ያሉትን መሠረታዊ ጥያቄዎች ከግምት ዉስጥ ያላስገባ ወይም እውቅና ያልሰጠ ፤ የህወሃት የበላይነት የነገሠበትን ሥርዓት ዕድሜ ለማስቀጠል ሲባል ገዢዉ ፓርቲ እስካሁን አከናወንኩ ያላቸውን በጎ እርምጃዎች በመዘርዘር “በአመራሮቹ ድክመት ካልሆነ በቀር ምንም አይነት የፖሊሲም ሆነ የፖለቲካ እምነት ችግር የለብኝም እና ተረጋጉ” የሚል መልዕክት ያስተላለፈበት ሆኖ ተገኝቶአል። እንዲህ አይነት መግለጫ ለማውጣት የህወሃትን የበላይነት ከውስጥ ሆነው አጥብቀው በመታገል ላይ ያሉ የሌሎች አባል ድርጅቶች አመራሮችስ እንዴት ብለው ተስማሙበት የሚል ጥያቄም በማስነሳቱ ምናልባትም ስብሰባው ከተበተነ ቦኋላ እራሱ ህወሃት “አለሁ” ለማለት በግሉ ጽፎና አጽድቆ ያሰራጨው ሊሆን ይችላል የሚልም ግምት አሳድሮአል። የግምቱን ምክንያታዊነት ደግሞ የሚያረጋግጠው መግለጫው ይፋ የሆነው ስብሰባው ተጠናቀቀ ከተባለበት ዓርብ ታህሳስ 21 ቀን ቦኋላ ለ36 ሰዓታት ዘግይቶ መሆኑ ነው። መግለጫው ላይ እንዲህ አይነት ጥርጣሬ በመፈጠሩ የተነሳ በኢህአዴግ 27 አመት የሥልጣን ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የ4ቱም ድርጅቶች ሊቃነመናብርት በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠት ተገደዋል። በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅትም ህብረተሰቡ ውስጥ ጥርጣሬ በፈጠሩት እና መነጋገሪያ በሆኑት ነጥቦች ላይ በሁለት ጎራ የተከፈለ አስተያያት ሲሰጥ ተስተውሎአል።

ሁላችንም እንደምናውቀው የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የሆኑት 3ቱም ድርጅቶች ህወሃት የራሱን የፖለቲካ አጀንዳ ለማሳካትና ጥቅሙን ለማስጠበቅ በህወሃት የተፈጠሩ ናቸው። በዚህም የተነሳ ድርጅቶቹ እስከ ቅርብ ግዜ ድረስ ከአገርና ከወገን ጥቅም በላይ በአካል ለፈጠራቸው ህወሃት ታማኝ ሆነው ሲያገለግሉ ኖረዋል። ይህ ሃቅ መሆኑ እየታወቀ አንዳንዶች ከዚህ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ በጎ ውጤት በመጠበቅ አገዛዙ እስካሁን በተከተላቸው የተሳሳቱ ፖሊሲዎች እና በፈጸማቸው ህገወጥ ተግባሮች ምክንያት አገራችን ከገባችበት ዘርፈ ብዙ ችግሮች የምትወጣበትንና ከተጋረጠባት የህልውና አደጋ የምትታደግበትን ሥርነቀል እርምጃዎች ለመውሰድ የሚያስችሉ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ብለው ጓጉተው ነበር። ህወሃት/ ኢህአዴግ በእስከዛሬ ተሞክሮው ምንም አይነት ለአገርና ለወገን የሚጠቅም እርምጃዎችን ከራሱ ጠባብ አላማ አስበልጦ እንደማያውቅ እየታወቀ እንዲህ አይነት ጉጉት ያደረባቸው ወገኖች ተስፋ ያደረጉት እንዲያው በድፍኑ አልነበረም። ምክንያቱም መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም በሞት ከተለየ ወዲህ ህወሃት ውስጥ የተፈጠረው የሥልጣን ክፍፍል የህወሃትን የበላይነት ተቀብለው በኖሩ አባል ድርጅቶች በተለይም በኦህዴድና በብአዴን ዘንድ“እንደከዚህ በፊቱ ታዛዥ ሆነን አንኖርም” የሚል አመጽ እና የእኩልነት ጥያቄ ቀስቅሶአል። በሌላ በኩል ደግሞ በአብዛኛው የአገራችን ክፍል የሚኖረው ህዝባችን አገዛዙ አሠልጥኖ ካዘመተበት የአጋዚ ጦር ጋር እየተፋጠጠ ለመብቱና ለክብሩ በማካሄድ ላይ የሚገኘው ሁለገብ ትግል ከግዜ ወደ ጊዜ እየተጠናከረና አድማሱን እያሰፋ እንጂ ወደ ኋላ እየተመለሰ ስላልሆነ በራሱ በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውስጥ በተለያየ የሥልጣን እርከኖች ላይ ባሉ አመራሮች ዘንድ ግንዛቤና ድጋፍ እያገኘ የመጣበት ሁኔታም አለ። ከዚህ በተጨማሪ ህወሃት በገጠመው ንቅዘትና በህዝብ ዘንድ ባጣው ተቀባይነት ምክንያት ከከፍተኛ አመራሩ ጋር ተሻርከው በሃብት ዘረፋ የተሰለፉ ነባር የኦህዴድና የብአዴን አመራሮችን በሙስናና በመልካም አስተዳደር ጉድለት ስም እያባረረ በወታደራዊና የስቪል ደህንነት ተቋሞቹ ውስጥ ተኮትኩተው ያደጉ ወጣት አመራሮችን ወደ ሥልጣን እንዲመጡ ሁኔታዎችን አመቻችታል። በተለይም በኦህዴድ ውስጥ። እነዚህ አዳዲሶቹ አመራሮች ደግሞ እንደቀደሞዎቹ ነባር አመራሮች ህሊናቸውን ሽጠው ለሚከፈላቸው ደመወዝ የሚገዙ አልሆኑም። እንዲያውም እንወክለዋለን የሚሉት ማህበረሰብ የሚያሰማውን የዘመናት ብሶትና የመብት ጥያቄ ከመደገፍ አልፈው ወገናዊነታቸውን በተለያየ መንገድ መግለጽ ጀምረዋል። ከነዚህ ሁሉ ምክንያቶች በመነሳት ህወሃት እንደ እስከዛሬው የኦህዴድንና የብአዴንን ሙሉ ድጋፍና ትብብር ሳያገኝ ብቻውን እየገደለ፤ እያሰረ ፤ እየገረፈና እያፈናቀለ ለመዝለቅ እንደማይችል ሥለሚረዳ አጋጣሚውን በመጠቀም እራሱን ለህዝብ ጥያቄ ለማስገዛት ሥርነቀል ውሳኔ ለማስተላለፍ ይችል የሆናል የሚል ተስፋ ይዘው ነበር።

ብዙዎችን ተስፋ ያስቆረጠው ይህ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች አንዳንዶች ጠብቀውት እንደነበረው ሥርነቀል ለውጥ ለማምጣት አስተዋጽዖ የሚያደርግ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ከማናችንም በላይ ተጠቃሚው እራሱ ህወሃት ይሆን እንደነበር ግልጽ ነው። ምክንያቱም ላለፉት 27 አመታት ሥልጣንን ከለላ በማድረግ በአገር ሃብት ዘረፋ እጅግ የከበሩ፤ የሥልጣን ዕድሜያቸውን ለማራዘም በፈጸሙት አፈና በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን በግፍ ያስጨፈጨፉ ፤ ያሠሩ ፤ ያስገረፉ ፤ ያፈናቀሉና ለስደት የዳረጉ እነርሱ ስለሆኑ አገራችን ውስጥ የሚደረገው ማንኛውም አይነት ሠላማዊ የሥልጣን ሽግግር ይዞት የሚመጣው ብሄራዊ እርቅ በአብዛኛው ተጠቃሚ የሚያደርገው በወንጀል የተጨማለቀውን የህወሃት አመራርን ነበር። ዛሬ የአጋዚ ጦር የሚፈጽምበትን አፈናና ግድያ ተቋቁሞ ነጻነቱን ለማስመለስ በመፋለም ላይ ያለው ህዝባችን በምንም ተዓምር መብቱንና ክብሩን ሳያስመልስ ወደ ቤት እንደማይገባ ከምንግዜውም በላይ ግልጽ ሆኖአል። በህወሃት ገታራነትና ትዕቢት ህዝባችን ለዚህ ትግል የሚከፍለው መስዋዕትነት እየከበደና እየገዘፈ ከሄደ ለህወሃት የእስካሁኑ ወንጀሎች የሚኖረው የይቅርታ ልብ እየተመናመነና እየደነደነ በስተመጨረሻው የሚያስከፍለውም ዕዳ እየከፋ ይሄዳል። ይህ በሞራልም በህግም የተረጋገጠ ነው።

አርበኞች ግንቦት 7 አገራችን ውስጥ እየተካሄደ ያለው ትግል የዲሞክራሲ ሥርዓት ለማምጣት የሚካሄድ የሞት ሽረት ትግል ስለሆነ ህወሃት በሚያስበው ማንኛውም አይነት የጥገና ለውጥ እንደማይሰናከል አጥብቆ ያምናል።በዚህም ምክንያት ህዝባችን የጀመረው ትግል ግቡን እንዲመታ ያለውን ሃይል በሙሉ አስተባብሮ እስከመጨረሻው በጽናት ይታገላል።

ህወሃት በድል አድራጊነትና በአይነኬነት እስከዛሬ የአገራችንን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ምህዳር በበላይነት ተቆጣጠሮ ለመዝለቅ የቻለው ህዝባችንን በቋንቋና በሃይማኖት የመከፋፈል ሴራው ስለተሳካለት ነበር። ያስኬት ዳግም ላያንሰራራ እየሞተ ነው። የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ “መርህ አልባ ግንኙነት “ በማለት የኮነነው የሁለቱ ትላልቅ ማህበረሰቦች ግንኙነት የህይወት እስትንፋስ ሆኖ ህወሃትን ላለፉት 26 አመታት ሥልጣን ላይ ያቆየውን የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ አፈር ከድሜ አብልቶታል። ህወሃት ምን ያስከትል ይሆን ብሎ ሳያስብ “መርህ አልባ ግንኙነት” ብሎ የኮነነው የአማራና የኦሮሞ ህዝብ ግንኙነት የበለጠ የህዝብ ቁጣ ቀስቅሶበት ከተለመደው አሰራር ውጪ በቡድን ጋዜጣዊ መግለጫ እንዲሰጥ አስገድዶታል። “ ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ ” እንዲሉ መልዕክቱ ዒላማውን ከመታ ቦኋላ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጠ አልተሰጠ ልዩነት የለውም።“እሳትና ጭድ የሆኑት ሁለቱ ማህበረሰቦች መቀራረብ የጀመሩት በኛ ሥራ አለመሥራት ነው” ተብለንስ የለ? በቃል አቀባዩ ጌታቸው ረዳ? ሌላው ማዘናጊያና ጊዜ መግዣ ደግሞ በስብሰባው ውሳኔ ላይ ያልተጻፈና ከጋዜጣዊ መግለጫው የሰማነው የፖለቲካ እስረኞች የመፈታት ዜና ነው።

ወያኔን ማፍረስ አገራችንን ከመፍረስ መታደግ ነው! – የአርበኞች ግንቦት 7 መግለጫ

የወያኔው ጦር በጨለንቆ በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ ባደረሰው የጅምላ ጭፍጨፋና እንዲሁም በምዕራብ ሃረርጌ ሃዊ ጉዲና እና ዳሮ ወረዳዎች ውስጥ በኢትዮጵያ ሶማሊ ወገኖች ላይ በደረሰው እልቂት ንቅናቄያችን አርበኞች ግንቦት7 የተሰማውን ከፍተኛ ሃዘን ለመግለጽ ይወዳል። ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ህይወት ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውና ለዜጎች የህይወት ዋስትናና ነጻነት እውን መሆን ሌት ተቀን የሚታገለው ድርጅታችን፣ እንዲህ አይነት የጅምላ ጭፍጨፋ መርዶዎችን ሰምቶ በዝምታ ለማለፍ የሚያስችለው ትዕግስት የለውም።

የአለም ህዝብ አገራችንን በድህነቷ ይወቃት እንጅ፣ ድህነት ያልበታተነው የህዝብ አንድነትና ፍቅር ያላት አገር መሆኗንም ጠንቅቆ ያውቃል። ይህ በዘመናት የተገነባው ፍቅርና አንድነት የውዷ አገራችን ልዩ መለያ እሴቷ ነው። ይሁን እንጅ ይህ እንቁ እሴት ካለፉት 26 ዓመታት ወዲህ፣ በተለይም ደግሞ በቅርቡ እየተራከሰና ዋጋ እያጣ በመምጣቱ በአገራችን ህልውና፣ በህዝባችን ሰላምና ደህንነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ይዞ መጥቷል። ይህ የአንድነትና የፍቅር ማተባችን እየተበጠሰ ያለው በማንኛውም የውጭ ሃይል ወይም በየትኛውም ድርጅት ሳይሆን፣ ስልጣኑን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮ በሚገኘው የወያኔ ቡድን መሆኑ ስጋታችንን አባብሶታል። በየትኛውም አገር የመንግስት ታሪክ የመንግስት የመጨረሻውና ቀላሉ ስራ የዜጎችን ደህንነትና ህልውና ማስጠበቅ ነው። እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ለዘመናት የተገነባ ፍቅርና አንድነት ባለባቸው አገሮች የሚገዙ መንግስታት፣ የዜጎቻቸውን ደህንነትና ሰላም ማስጠበቅ ካለባቸው ሃላፊነቶች ሁሉ እጅግ ቀላሉ መሆኑን ከታሪክ መማር ይቻላል። ዜጎች ለዘመናት የገነቡትን ፍቅርና አንድነት ከትውልድ ትውልድ እያሸጋገሩ ህልውናቸውንና ደህንነታቸውን አስጠብቀው እንዲጓዙ፣ ፍትሃዊ አስተዳደር መመስረት ግድ ነው። እንደ ጣሊያን የመሳሰሉ የውጭ ወራሪዎች አገራችንን በቅኝ ግዛት ለመያዝ ያልቻሉት ይህን ዘመን የማይሽረውን የአንድነትና የፍቅር ማተብ ለመበጠስ ባለመቻላቸው መሆኑ የሚታወቅ ነው። ወያኔ ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድነት ይነሳብኛል በሚል ፍርሃት፣ ህዝባችንን እርስ በርስ በማጋጨት በየቦታው የዜጎች እልቂት እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑ ፣ በአለም የመንግስታት ታሪክ ልዩ ያደርገዋል። ይህ ህዝብን እርስ በርስ እያጨፋጨፉ ለመግዛት የሚደረግ ሙከራ፣ ዛሬ ሆድን ሞልቶ ለማደር የጠቀመ ቢመስልም፣ የሁዋላ ሁዋላ ግን “መሬት ተከፍታ በዋጠችኝ” የሚያስብል አደጋ በገዢዎች ላይ ይዞ መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ከሊቢያው መሪ ጋዳፊ እና ከየመኑ አህመድ ሳላህ የቅርብ ጊዜ ታሪክ መማር ይቻላል።

በሃዊ ጉዲናና ዳሮ ወረዳዎችም ይሁን በጨለንቆ፣ ከዚያ በፊትም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተካሄዱ እና አሁንም በመካሄድ ላይ ያሉ ጭፍጨፋዎችና ግጭቶች በህዝብ መካከል የሚካሄዱ ሳይሆኑ ወያኔ የስልጣን እድሜውን ለማራዘም ሲል የሚለኩሳቸውና የሚያራግባቸው መሆኑን ህዝባችን የሚያውቀው ሃቅ ቢሆንም፣ ዛሬም ይህን ሃቅ ልናስታውስ እንወዳለን። ወያኔ በስልጣን ላይ እንዲቀጥል እስከፈቀድንለት ድረስ በዘመናት የተገነባው የፍቅርና የአንድነት ማተባችን ተበጣጥሶ አሁን ከሚታዬውም በላይ እጅግ አስከፊ ወደሆነ የእርስ በርስ ጦርነት እንደሚከተን የታወቀ ነው። ስለዚህ ይህን የአገር ጠላት ከስር መሰረቱ ነቅሎ በመጣል የአንድነታችንንና የፍቅር ማተባችንን መልሶ በማሰር የዜጎቻችንን ህልውና እና ደህንነት ማስጠበቅ ከእያንዳንዱ አገር ወዳድ ዜጋ ሁሉ የሚጠበቅ ነው። ወያኔ እያንዳንዷን ቀን በስልጣን ላይ በቆዬ ቁጥር በህዝባችን ላይ የሚደርሰው አደጋም በተመሳሳይ መንገድ እየጨመረ የሚሄድ በመሆኑ ዳር ቆመን የምንመለከትብት ጊዜ እንዳበቃ ማወቅ አለብን።

አርበኞች ግንቦት7 ወያኔ በህዝባችን ላይ ያደረሰውን እልቂት ሲያወግዝ፣ የእልቂቶች ሁሉ ምንጭ የሆነውን የወያኔ አገዛዝ እንድናስወገድ የተለመደ ጥሪውን በማቅረብ ነው።

ድል ለኢዮጵያ ሕዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ለዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ