Friday, October 31, 2014

ህወሃትና የጦር አበጋዞቹ እሴቶች

ህወሃት የትግሬ ተወካይ ብቻ ሳልሆን ለትግራይ ህዝብ የሚያመልከውን አምላክም ጭምር የምመርጥለት እኔ ነኝ በሚል እብሪት ውስጥ ይገኛል። በዚህ እብሪቱም እየተመራ የምታመልኩትን ልመርጥላችሁ ብሎ አጠቃላይ ሙስሊሙንም ክርስትያኑንም እያመሰው እንደሆነ እያየን ነው። እኔን የማይቀበል እጣ ፈንታው ከመታመስ በላይ የሆነ ወዮታ ነው የሚል ያልተፃፈ አዋጅም አለው። ህወሃት በትግራይ ትከሻ ላይ ተፈናጦ፤ ትግራይን ምርጫ አሳጥቶ እኔን እምኑ መንገዳችሁም ህይወታችሁም እኔ ብቻ ነኝ ብሎ ራሱን የትግራይ ጣዖት አድርጎ ሹሟል። ይሄን ጣዖት አንቀበልም፤ እኛ የራሳችን ሂሊና ያለን እንደ ሰው ማሰብ የምንችል ነን ያሉ ብዙ የኢትዮጵያ ልጆች ባልታወጀው አዋጅ መሠረት አብዮታዊ ፀሎት እየተፀለየላቸው አፈር ለብሰው ቀርተዋል።የህወሃት የእብሪቱ መጀመሪያ “እኔ ያልኩት ካልሆነ ሁሉም ገደል ይግባ” ማለቱ ነው። የትግራይ ተወካይ እኔ ብቻ ነኝ ሌላው ሁሉ የትግራይ ህዝብ ጠላት ነው የሚል እምነቱ የድርጅቱን ሥር የሰደደ መሠሪነትና እብሪት የሚያሳይ ነው።

ብዙ ኢትዮጵያዊያን ህወሃት የቆመው ለትግራይ ህዝብ ነው የሚል ዕምነት አሳድረዋል። ይሄን አስተሳሰብ መቀበል የሚጠቅመው ለህወሃት ብቻ ነው።ህወሃት ለትግራይ ህዝብ ክብርም ፍቅርም ያለው ቡድን አይደለም። ለትግራይ ህዝብ በጎ ምኞት እና ክብር ያለው ቢሆን ኑሮ የትግራይ ህዝብ የወደደውን እንዲመርጥ፤ ያልወደደውን እንዲተው ያልተሸራረፈ ነፃነት እንዲኖረው ያደርግ ነበር። እኛ እንደምናየው ግን የትግራይ ህዝብ የወደደውን ለመምረጥ፤የጠላውን ለመተው እንዲችል ነፃነትያለው ህዝብ አይደለም። የትግራይ ህዝብ ነፃነቱን በነፃነት ሥም ያጣ ህዝብ ሁኗል። ህወሃቶች የትግራይን ህዝብ ነፃነት ሸራርፈው ሸራርፈው ህዝቡን በሙሉ መያዣ አድርገውና ከወገኑ ለይተውት እየገዙት ይገኛሉ። የትግራይም ህዝብ ሳይወድ በግዱ ህወሃቶችን ተሸክሞ መከራው በዝቶ እየተገዛ ይገኛል።

Wednesday, October 22, 2014

የእንግሊዝ መንግሥት ለኢትዮጵያ ያዘጋጀውን የደኅንነት ማኔጅመንት ፈንድ አቋረጠ

በእንግሊዝ መንግሥት ገንዘብ ለኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች ይሰጥ የነበረው የደኅንነት ማኔጅመንት ፕሮግራም ተቋረጠ:ሪፕሪቭ የተባለ ነፃ የሕግ አገልግሎት የሚሰጥ የእንግሊዝ ኩባንያና ሌሎች የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞች፣ ካለፈው ዓመት አጋማሽ ጀምሮ የእንግሊዝ መንግሥት ይህንን ፕሮግራም እንዲያቋርጥ ግፊት ሲያደርጉ ነበር::
እነዚህ ወገኖች ይህንን ግፊት የጀመሩት የኢትዮጵያ መንግሥት በልማት ምክንያት ዜጐችን ከመኖሪያ አካባቢያቸው ያፈናቅላል በሚል ክስ ነበር:: ይሁን እንጂ የግንቦት ሰባት ጸሐፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በየመንና
በኢትዮጵያ የፀጥታ ኃይሎች፣ ባለፈው ሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ ኤርትራ ለመጓዝ የመን በኢትዮጵያ የፀጥታ ኃይሎች፣ ባለፈው ሐምሌ 1ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ ኤርትራ ለመጓዝ የመንሰንአ አውሮፕላን ማረፊያ በቁጥጥር ሥር ውለው ወዲያውኑ ለኢትዮጵያ መንግሥት ከተላለፉ በኋላ፣ በእንግሊዝ መንግሥት ላይ ጫናው እንዲጠናከር ሲጥሩ ነበር::
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ አሁን ያለውን የኢትዮጵያ መንግሥት በኃይልም ሆነ በተገኘው አማራጭ ለመለወጥ የሚታገለው የግንቦት ሰባት አመራር ይሁኑ እንጂ፣ ዜግነታቸው እንግሊዛዊ መሆኑ ተጨማሪ ግፊት ይፈጥራል ብለውም ነበር::
እሳቸው በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ በእንግሊዝ መንግሥት ላይም ሆነ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ከፍተኛ ግፊት ከሚያደርጉት መካከል፣ መቀመጫውን ለንደን ያደረገው ነፃ የሕግ አገልግሎት የሚሰጠው ተቋም የሆነው ሪፕሪቭና የአውሮፓ ኅብረት የሰብዓዊ መብት ኮሚቴ ይገኙበታል::
የሪፕሪቭ የሕግ ዳይሬክተር ቲኔክ ሀሪስ በነሐሴ ወር ለእንግሊዝ መንግሥት ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር ጀስቲገን ግሪንግ በጻፉት ደብዳቤ፣ ‹‹የእንግሊዝ ዜግነት ያለውን ግለሰብ ላገተውና ቶርቸር በማድረግ ለሚጠረጠረው የኢትዮጵያ መንግሥት ኃላፊዎች ይህንን ፕሮግራም መስጠት ተገቢ ነው ወይ? ተገቢ ነው ብለው ካላመኑ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እስካልተፈቱ ድረስ ምን ዕርምጃ ሊወስዱ እንደሚችሉ ቢያሳውቁን?›› በማለት ጥያቄ አቅርበው ነበር::
የአውሮፓ ኅብረት የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ኮሚቴ ባለፈው መስከረም ወር ባካሄደው ጉባዔው በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እስር ላይ የእንግሊዝ መንግሥት ምንም ዓይነት ጫና አለማሳደሩን በመውቀስ አስፈላጊ ነው የተባለ ውሳኔ በኢትዮጵያ ላይ ለማሳለፍ የሁለት ወራት ጊዜ ቀጠሮ ወስዶ መበታተኑን መዘገባችን ይታወሳል::
ይህ ጫና ባለበት በአሁኑ ወቅት የእንግሊዝ መንግሥት ዲፓርትመንት ፎር ኢንተርናሽናል ዴቨሎፕመንት (ዲኤፍአይዲ) ለኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች ይሰጥ የነበረውን የደኅንነት ማኔጅመንት ፕሮግራም አቋርጧል::
ፕሮግራሙ የተመረጡ የኢትዮጵያ የደኅንነት ኃላፊዎች በእንግሊዝ አገር በደኅንነት ማኔጅመንት የማስትሬት ዲግሪያቸውን እንዲሠሩ የሚያግዝ ነበር::
የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ ወደ 70 ሚሊዮን ፓውንድ ሲሆን፣ ለመጀመሪያው ዙር ፕሮግራም ሁለት ሚሊዮን ፓውንድ ያስፈልግ ነበር::
ለዚህ ዓመት ተይዞ የነበረው የሁለት ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ ለአጠቃላይ ፕሮግራሙ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ::
የዲኤፍአይዲ የኢትዮጵያ ቢሮ ጉዳዩን በተመለከተ ከሪፖርተር በኢሜይል ለቀረበለት ጥያቄ ፕሮግራሙ መቋረጡን አረጋግጧል:: ነገር ግን ምክንያቱ ከአቶ አንዳርጋቸው ጋር ግንኙነት እንደሌለው አስታውቋል::
‹‹ፕሮግራሙ የተቋረጠው የእንግሊዝ መንግሥት ለፕሮግራሙ የሚያወጣውና የሚያገኘው ምላሽ (ኢንቨስትመንት ሪተርን) የሚጣጣሙ ባለመሆናቸው ነው፤›› በማለት በደፈናው መልሷል::

Sunday, October 19, 2014

“እኔ ብቻ” ቢያክሙት የማይሽር የወያኔ በሽታ

ዘረኝነት፤ ጎጠኝነትና ዕብሪት የወያኔ አዲሰ ባህሪያት ሳይሆኑ አስራ ሰባት አመት ጫካ ዉስጥ በቆየባቸዉ አመታትና ዛሬም ከጫካ ወጥቶ አገር እየመራ በቆየባቸዉ ሃያ ሦስት አመታት አብረዉት የኖሩ መታወቂያ ካርዶቹ ናቸዉ። ዘረኝነት፤ አማራ ጥላቻና የትግራይ ሪፓብሊክ ህልም ዋና ዋናዎቹን የወያኔ መሪዎች ደደቢት በረሃ ከገቡ በኋላ በድንገት የለከፋቸዉ በሽታ ሳይሆን ከና ከልጅነታቸዉ ተጠናዉቷቸዉ አብሯቸዉ ያደገ በሽታ ነዉ። ወያኔ ጨካኝ ነዉ፤ ወያኔ ዉሸታም ነዉ፤ወያኔ ከሃዲ ነዉ፤ ወያኔ ለኢትዮጵያ ዳርድንበርና የግዛት አንድነት ደንታ የሌለዉ ባዕድ አካል ነዉ። እነዚህ ሁሉ የወያኔን ማንነትና ምንነት በትክክል የሚገልጹ የወያኔ በሽታዎች ናቸዉ። በዛሬዉ ቆይታችን በልዩ መነጽር አብረን የምንመለከተዉ የወያኔ በሽታ ግን በአይነቱ ከእነዚህ ከላይ ከተጠቀሱት በሽታዎቸ ጋር ተመሳሳይ ቢሆንም በጠባይና በአገላለጽ ግን ለየት ያለ ነዉ።

የኢትዮጵያ ህዝብ ለአመታት እንዳየዉም ሆነ ሀወሓትን መስረተዉ ለስልጣን ያበቁትና ህወሓት ለእነሱም አልበጅ ብሏቸዉ ጥለዉት የወጡት ግለሰቦች በቃልም በጽሁፍም እንደነገሩን ወያኔ የጫካ ዉስጥ ጠባዩን ዛሬም ያልለቀቀ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ዛሬማ ጭራሽ ብሶበት ያየዉን ነገር ሁሉ ነጥቆ የራሱ ካላደረገዉ ወይም ሙሉ ለሙሉ ካልተቆጣጠረዉ አርፎ የማይተኛ ድርጅት ሆኗል። ብዙዎቻችን የወያኔ ስም በተነሳ ቁጥር ትዝ የሚለን ዘረኝነቱ ነዉ። በእርግጥም ወያኔ ግለሰብንና ግለሰቦችን ወይም የተለያዩ ቡድኖችን በዘር መነጽር ብቻ የሚመለከት ዘረኛ ድርጅት ነዉ። ሆኖም ወያኔንና ወያኔ የፈጠረዉን ዘረኛ ስርዐት ለመደምሰስ የሚደረገዉ ትግል የወያኔን ዘረኛ ገጽታ ብቻ ሳይሆን ሁሉንም የወያኔ ገጽታዎች ማጋለጥና መዋጋት አስፈላጊ ነዉ። ለምሳሌ ወያኔ በፕሮፓጋንዳዉ ይዋጋናል፤ በዲፕሎማሲ ዘርፍ ይዋጋናል፤ በማህበራዊ ሜዲያዉ ዘርፍ ለተሳዳቢዎች ገንዘብ እየከፈለ ይዋጋናል፤ ከዚህ በተጨማሪ በቁጥጥሩ ስር ባደረጋቸዉ ፍርድ ቤቶች፤ ፖሊስ፤ መከላከያና የደህንነት ተቋሞች አማካይነትም ይዋጋናል። አዎ ! ወያኔ በቁጥጥሩ ስር ባደረጋቸዉ ተቋሞች አማካይነት እንቅልፉን ትቶ ቀንና ማታ ይዋጋናል። ዉድ አድማጮቻችን እቺን ወያኔ በቁጥጥሩ ስር ባደረጋቸዉ ተቋሞች አማካይነት ይዋጋናል የምትለዋን አባባል ጠበቅ ያደረግነዉ አለምክንያት አይደለም። ዛሬ ብዙ የምናወራዉ ስለዚሁ “ሁሉን ነገር መቆጣጠር” ስለሚለዉ የወያኔ አባዜ ነዉ።

በወያኔ የበላይነት የተጻፈዉ የኢትዮጵያ ህገ መንግስት – የኢትዮጵያ ብሄር፤ ብሄረሰቦች፤ ህዝቦች የኢትዮጵያ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤቶች ናቸዉ ይላል። ሆኖም የዚህ ሉዓላዊነት መገለጫ በሆነዉ ፓርላማ ዉስጥ 38 መቀመጫዎች ብቻ ያለዉ ህወሓት 509 መቀመጫዎች ያላቸዉን ከትግራይ ዉጭ ያሉትን ሌሎቹን የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች የፖለቲካ ህይወት ሙሉ በሙሉ ይቆጣጠራል። የሚገርመዉ ወያኔ የሚቆጣጠረዉ የኢትዮጵያን ህዝብ የፖለቲካ ህይወት ብቻ አይደለም። የኢትዮጵያን የኤኮኖሚና የማህበራዊ ዘርፎችም ሙሉ በሙሉ በወያኔ ቁጥጥር ስር የወደቁ ናቸዉ። በአጠቃላይ ወያኔ ኢትዮጵያ ዉስጥ በዬትኛዉም ዘርፍ ከላይ እስከታች እሱ የማይቆጣጠረዉ ምንም ነገር እንዲኖር አይፈለግም። ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያ ዉሰጥ በወያኔና በሁለቱ ግዙፍ የአገራችን ሐይማኖቶች መካከል ለአመታት የዘለቀዉ ንትርክ፤ አተካሮና ፍጥጫም የዚሁ የወያኔ ሁሉንም ነገር እኔ ብቻ ካልተቆጣጠርኩት የሚል ክፉ አባዜ ዉጤት ነዉ።

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የሕዝብ ወገንተኝነቱን የሚያሳይበት ወቅት አሁን ነው!

ዘረኛውና ፋሽስታዊው የህወሓት አገዛዝ የኢትዮጵያን መከላከያ ሠራዊት በዘርና በፓለቲካ ወገንተኝነት በመከፋፈል ሹመቱና ጥቅማ ጥቅሙን ለራሱ ወገን፣ ችግሩንና መከራዉን ግን ለሌላው ኢትዮጵያዊ ያደለ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም መሠረት ሳይማሩና ሳይሰለጥኑ የጄኔራልነት ማዕረጎችን በሙሉ ሰብስበው የወሰዱት የህወሓት አባላት መሆናቸው የአደባባይ ሚስጢር ነው።

በወያኔ መዳፍ ውስጥ እየተሰቃየች ባለችው ኢትዮጵያችን ውስጥ በዘርም ይሁን በፓለቲካ አመለካከት ከህወሓት የተለዩ ኢትዮጵያዊያን ቢማሩም ቢሰለጥኑም ለከፍተኛ አመራርነት እንደማይበቁ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ያየነው ነው። አገዛዙ ቅራኔ ውስጥ በገባባቸው ቦታ ሁሉ እየዘመቱ ሕይወታቸውን እየገበሩ ያሉት ግን በመካከለኛና ዝቅተኛ ማዕረጎች ያሉ ኢትዮጵያዊያን መኮንኖችና ብዙሃኑ የሠራዊቱ አባላት የሆኑ ወታደሮችናቸው። ብዙሃኑ የሠራዊት ክፍል አለቆቹን ከመጠበቅ ባለፈ ድምጹን ከፍ አድርጎ ለመናገር እንኳን የማይፈቀድለት ሎሌ ተደርጓል።

ለኢትዮጵያዊ ወታደር ለህወሓት ሎሌ ከመሆን በላይ የሞት ሞት የለም። ብዙሃኑ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊቱ አባላት በጥቂት የወያኔ ሹማምንት የሚረገጥ መሆኑ የሠራዊቱን አባላት የግል ስብዕና ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ የሠራዊቱን ክብር ይነካል። የሠራዊታችን የህወሓት አገልጋይ መሆን የምንወዳት አገራችን ኢትዮጵያን ያዋርዳል። ይህ ዉርደት በዚህ ሁኔታ መቀጠል የለበትም።

ከእንግዲህ ጄኔራሎችና ሌሎችም የበላይ አዛዦች ሁሉ የአንድ አካባቢ ተወላጆች በሆኑበት ሠራዊት ውስጥ ተስማምቶ መኖር መቀጠል እያንዳንዱን የመከላከያ ሠራዊት አባል ሊያሰፍር ይገባል። የህወሓት ጄኔራሎች ጮማ በውስኪ ሲያወራርዱ፤ በህንፃዎች ግንባታ፣ በባንኮች ንግድ፣ በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ተሰማርተው ቢዝነሳቸውን ሲያጧጥፉ፣ ምስኪኖቹ የሠራዊቱ አባላት በኦጋዴን፣ በአፋር፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በአማራና በሌሎች የአገሪቱ ግዛቶች እየተወረወሩ ወገኖቻቸውን የሚፈጁበት ሥርዓት ማብቃት አለበት። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ብዙሃኑ አባላት ቤተሰቦቻቸው በችጋር እየተቆሉ የአዛዦቻቸው ሀብት ጠባቂ መሆናቸው ማክተም አለበት።

የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት የጭለማ ዘመን ታሪክ እያበቃ መሆኑን የሚጠቁሙ ምልክቶች እየታዩ ነው። መሣሪያዎቻቸውን እንደያዙ የነፃነት ኃይሎችን የሚቀላቀሉ የሠራዊቱ አባላት ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እየጨረመ መጥቷል። ሠራዊቱ ከሕዝብ ጎን እንደሚቆም ውስጥ ውስጡን የሚላኩ መልዕክቶች እየተበራከቱ መጥተዋል። ይህ አበረታች ዜና ነው፤ ግን በቂ አይደለም። ወያኔን ከውስጥም ከውጭም የምናጣድፍበት ጊዜው አሁን ነው። የነፃነት ኃይሎችን መቀላቀያ ጊዜ አሁን ነው፤ በሠራዊቱ ውስጥም በህቡዕ መደራጃ ጊዜ አሁን ነው። ይህን ጊዜ መጠቀም ብልህነት ነው።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ጥቂት የህወሓት ጥጋበኞች በብዙሃኑ የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት ላይ የሚያደርሱት በደል ማብቃት አለበት ይላል። ግንቦት 7፡ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት በሙስና የደለቡት፣ ትዕቢተኛና ጨካኝ መሪዎቻቸው ፍጹም ኢትዮጵያዊ ባህርይ የሌላቸው ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች እንደሆኑ በመረዳት በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ክንዱን እንዲያነሳባቸው ጥሪ ያደርጋል። ከዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያ ሕዝብም የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አንድ ወጥ እንዳልሆነ እና በመካከለኛና ዝቅተኛ ደረጃ ያሉ መኮንኖችና አብዛኞዎቹ ወታደሮች የሕዝብ ወገን መሆናቸውን እንዲገነዘብ ያሳስባል። “አብረን ነው ዘረኛውና ፋሽስቱን ወያኔን ከኢትዮጵያ ጫንቃ ላይ አውርደን የምንጥለው” ስንል አብዛኛው የመከላከያ ሠራዊታችን ኢትዮጵያዊ ወገናችን እንደሆነ እና በወደፊቷ ኢትዮጵያ ግንባታ ውስጥም ጉልህ ሚና እንዲጫወት የምንፈልግ መሆኑን ግልጽ ማድረግ እንሻለን። የመከላከያ ሠራዊቱም የሕዝብ ወገንተኝነቱ በተግባር እንዲያሳይ ጥሪ እናደርጋለን። የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት የሕዝብ አካል ነው፤ የሕዝብ ወገናዊነቱ በተግባር የሚያሳይበት ትክክለኛ ጊዜ ደግሞ አሁን ነው እንላለን።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!



Saturday, October 11, 2014

ወያኔ ሲያስር አሜን….ሲገድልም (በኤፍሬም ማዴቦ)

ብዕር የያዘ ማንም ሰዉ በዘመናችን ደግሞ የኮምፒተር መክተቢያ ፊቱ ላይ የደቀነ ሁሉ ከሱ ዉጭ ያለዉን ማንንም ሰዉ “ሌባ”፤ “ባንዳ” ወይም “ከሃዲ” እያለ እንዳሰኘዉ መጻፍ ይችላል። በተለይ በእንደኛ አይነቱ ሀላፊነትም ተጠያቂነትም በሌለበት ህብረተሰብ ዉስጥ ደግሞ የጓደኛዉ ሀሳብ ያልተስማማዉ ሁሉ እየተነሳ የገዛ ጓደኛዉን ባንዳና ከሃዲ አድርጎ ስለሚስለዉ የላይ የላዩን ብቻ ለሚመለከት ሰዉ አገራችን በባንዳና በአገር ወዳድ መሳ ለመሳ ለሁለት የተከፈለች ትመስላለች። እግዝአብሄር ይመሰገን እዉነቱ ግን ከዚህ እጅግ በጣም የተለየ ነዉ። ርዕሴን የጀመርኩት አሜን ብዬ ነዉና እስኪ አንባቢዉ አንተም አሜን በል። ባንዳነትና ከሃዲነት ኃብታምና በእድገት ወደፊት የገፉ አገሮችን እየዘለለ ደሃና ኋላ ቀር አገሮችን ብቻ የሚጠናወት ተራ በሽታ አይደለም። ብዙዎቻችን አምባገነን መሪዎቻችንን ሸሽተን የተጠለልንባት አገር አሜሪካ እነ ሄንሪ ቤስትንና ጆን ብራዉንን የመሳሰሉ ከሃዲዎችን እንዳበቀለች ሁሉ ኢትዮጵያችንም ትናንት እነ ኃ/ሥላሤ ጉግሳን ዛሬ ደግሞ የኃ/ሥላሤ ጉግሳ የልጅ ልጆች የሆኑትን እነ መለስ ዜናዊን፤ አባይ ፀሐዬንና ሰብሃት ነጋን የመሳሰሉ የለየላቸዉ ከሀዲዎችን አፍርታለች። በነገራችን ላይ ሙስሊሙ በዱአዉ፤ ክርስቲያኑ በፀሎት፤ ጠቢብ በጥበቡ ፤ፀሐፊ በምናቡ የባንዳዉንና የከሃዲዉን ብዛት ለመቀነስ ካልተባበሩ በቀር “ወላድ በድባብ ትሂድ” ብለን ባንመርቃቸዉም የባንዳ አባትና አናት አስካሉ ድረስ ባንዳም መወለዱ አይቀርም።

ጋጠ ወጡ ማን ነው?

የህወሃት ጉጅሌና ሎሌዎቹ መቼም ራሳቸውን የሚያይ አይንም መስታዎትም ያላቸው አይመስሉም። ሀፍረትና ይሉኝታ የሚባሉ ነገሮች በአጠገባቸው የዘሩ የማይመስሉት ለዚህ ሳይሆን ይቀራል። ምናልባትም ብልግና፣ ጭካኔ፣ ግፍ፣ አውሪያዊ ስብእና፣ ወገን ካለህግ መግደልና ማዋረድ፣ የህዝብ ሃብት በጠራራ ጸሃይ መዝረፍ ለእነሱ የተፈቀደና የተሰጠ ጸጋ አድርገው ሳይቆጥሩት ይቀራሉ?

ባለፈው ሳምንት በዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የሰለጠነና የዳበረ ስርዓት አከባበር በሰፈነበት ከተማ ውስጥ ባልታጠቁ ሰላማዊ ተቃዋሚዎች ላይ ሲተኩሱና ሲያስተኩሱ በመዋላቸው ለደረሰባቸው ትዝብት የነውረኝነት ሀፍረት እንደማፈር ሰላማዊዎቹንና በሰላማዊ መንገድ እስከ ሲቪላዊ አልታዘዝም ባይነት መብት ያላቸውን ጠንቅቀው አወቀው የተንቀሳቀሱትን ዜጎች ጋጠ ወጥና ባለጌዎች ናቸው ሲሉ ተደምጠዋል። ትንሽ ሲቀዠብርባቸው ደግሞ ኦባማ ስላነጋገረን የቀኑ ተቃዋሚዎች፣ ይህ አልበቃ ሲል ደግሞ የሻእቢያ ተላላኪዎች ሲሉም ተደምጠዋል። ከአውሬነት ብዙ ያልተለዩት ደጋፊዎቻቸው ተኩሱን ሲያንጣጣ የነበረው የቀድሞ የስዩም መስፍን የግል አሽከርና ሹፌር የነበረው ወዲ ወይኒ ግደይ ስለተባረረ ንዴታቸውን ከአደባባይ እንኳን መደበቅ አልቻሉም። እናስ እዚህ ውስጥ ጋጠወጡ ማነው? ሀገሩን የሚያስተዳድርበትን አራዊታዊና ህግ አልባ ስርአት በሰለጠነ ህዝብ ሀገር በአደባባይ ለኤግዚብሽን የሚያቀርብ መደዴ ወይስ እስከ ሲቪል እምቢተኝነት ድረስ ሊደርስ የሚችል መብታቸውን ጥንቅቀው የሚያውቁና በግፍ ስርአት ለሚኖረው ወገናቸው ድምጽ ያሰሙ የህዝብ ልጆች?

በዘሩ ታማኝነት ተመርጦ ከስዩም መስፍን ሾፌርነት ውጪ ቅንጣት የዲፕሎማሲ እውቀት የሌለውን ደንቆሮ የዲፕሎማት ማእረግና ሽጉጥ አስታጥቆ ዋሽንግተን ከሚልክ መንግስት በላይ ጋጠወጥና አጉራ ዘለል ከየት ይገኛል።

እውነቱ ግን ወዲህ ነው ያለው። ቢያንስ በነጻው አለምየሚኖሩ የኢትዮጵያ ልጆች በሀገራቸውና በወገናቸው ላይ በሚደርሰው ስቃይ ውርደትና ግፍ ተንገፍግፈዋል። የወያኔ ሹማምንት ግፋቸውን እንዲያቆሙ ያሰሩዋቸውን እንዲፈቱና ሀገር ዝርፊያ እስኪያቆሙ ድረስ በገቡበት እየገባ ቁም ስቅላቸውን ማሳየትና ጋጠወጥና የነውረኛ ስርአት አገልጋዮች መሆናቸውን ማጋለጡን ይገፉበታል። በሰሩት ወንጀል አለምአቀፍ ፍርድቤቶች መድረክ ላይ እየጎተተ የሚያቀርብበት ጊዜም ሩቅ አይደለም።

የወጋ ይርሳ እንደሆነ እንጂ የተወጋ አይረሳም። አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሰላማዊ ተቃዋሚውን ድርጅት አባል በብረት ሶዶማዊ ምግባር የፈጸሙትን ጋጠ ወጥ የወያኔ ተላላኪዎች ማን ይረሳል። በየቤቱና በየጎዳናው በዱላ የሚቀጠቀጡትና ደማቸውን ሲጎርፍ ያየናቸው አዛውንት ሙስሊም ወገኖቻችን ደም እንዴት እንረሳለን። ሬሳቸው እንኳን ክብር አጥቶ የጋጠወጥ ወያኔ መጫወቻ የሆኑትን የኦጋዴን ወገኖቻችንን ማን ይረሳል። ጋምቤላ ጫካ ውስጥ እንደደኑ ተጨፍጭፈው የተቆለሉትን አኙዋኮች ማን ይረሳል። ከየኖሩበት ቦታ በግፍ እየተፈናቀሉ የሚንከራተቱትን እና የሚሞቱትን አማሮች ማን ይረሳል። በቆራጥነት ብቻ በሰላም መንገድ እንታገላለን ብለው በተነሱ ወህኒ የተወረወሩትን የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች የታሰሩትንና የተሰደዱትን ጋዜጠኞችና ጦማሪዎች የምንረሳቸው ስንሞት ብቻ ነው። ከየጎረቤት ሀገሩ እየታፈኑ የሚሰቃዩትን እነ አንዳርጋቸውን እና ሌሎች የሞቱትን ማን ይረሳል።

ህዝባችንን ወደ ሰላማዊ አመጽም ሆነ ወታደራዊ አመጽ እየገፋው ያለው ይህ የወያኔ ባህሪ ነው።

ግንቦት 7 ከዚህ አራዊታዊ ስርአት ጋር ሆናችሁ በተለያየ ምክንያት በህዝባችሁ ስቃይ ላይ የምትተባበሩ ወገኖች ሁሉ በአገኛችሁት አጋጣሚ ከእዚህ እኩይ ስርአት ተግባራት ራሳችሁን እንድታወጡ፣ ከቻላችሁ በውስጥም ሆናችሁ ወገናችሁን ሳትበድሉ ትግሉን እንድትቀላቀሉ ይመክራል።

መላው ህዝባችን በያለህበት ራስህን በራስህ እያደራጀህ የእምቢተኝነት እንቅስቃሴዎችን ጀምር። በመላው አለም ዙሪያ ተሰደህ የምትኖር ኢትዮጵያዊ ሁሉ ለወገንህ ለራስህም ትንሳኤ ተነስ!!

ትግላችን የመጨረሻውን መጀመሪያ እየተያያዘ ነው። የትልቅ ሀገርና ትልቅ ህዝብ ባለቤቶች ስለሆንን ከወያኔ ወሮበላ ጉጅሌ በበለጠ የሚገባን ህዝብ ነን!!

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!